2022-08-03 22:38:30
✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞
✞ እንኩዋን ለቅዱሳን ጻድቃን "እንድራኒቆስ ወአትናስያ" እና ለአቡነ "ፊልዾስ ዘደብረ ሊባኖስ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞
† ጻድቃን እንድራኒቆስ ወአትናስያ †
ሁለቱ ቅዱሳን ባል እና ሚስት [ባለትዳር] ናቸው:: የነበረበት ዘመን ፬ [4] ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: እስኪ እግዚአብሔር የቀደሰው ጋብቻ ምን እንደሚመስል እንመልከት::
እንድራኒቆስና አትናስያ በዘመናቸው ከልጅነት ጀምረው ቃለ እግዚአብሔርን የሚሰሙ : ለወላጆቻቸው የሚታዘዙ ነበሩ:: ዘመኑ ደርሶ በሚገባው የተክሊል ሥርዓት ጋብቻቸውን ፈጸሙ:: ፵ [40] ቀን ከተፈጸመ በሁዋላ ከምንም ነገር በፊት ፪ [2] ቱ ቁጭ ብለው ተወያዩ::
የውይይታቸው ርዕስ ደግሞ "ፈጣሪያችን በምን እናስደስተው" የሚል ነበር:: ውይይታቸው የጠናቀቀው በእነዚህ ውሳኔዎች ነው::
፩. ሁልጊዜም እንግዳ መቀበል አለብን::
፪. ነዳያን ከቤታችን ሊጠፉ አይገባም::
፫. ጸሎት : ጾምና ስግደት በቤት ውስጥ አይቁዋረጥም::
፬. አብሮ ለመተኛት መቸኮል የለብንም::
እነርሱ መልካምን አስበዋልና አምላክ የሰጣቸውን ሃብት ሲመጸውቱ ኖሩ:: ከዘመናት የቅድስና ጉዞ በሁዋላ በፈቃደ እግዚአብሔር ፪ [2] ልጆችን አከታትለው ወለዱ:: ወንዱን "ዮሐንስ" : ሴቷን ደግሞ "ማርያም" አሏት::
እነርሱን ከወለዱ በሁዋላ እንደ ገና ሌላ ውሳኔ አሳለፉ:: "ይህንን ላደረገልን ጌታ ከዚህ በሁዋላ አልጋ እንለያለን" ብለው ለ፲፪ [12] ዓመታት በጾምና በጸሎት ተወሰኑ::
ሕጻናቱ ዮሐንስና ማርያም በቅንነት አድገው እድሜአቸው ፲፪ [12] ሲሆን ፪ [2] ቱም በአንድ ቀን ታመው ሞቱ:: ይህ ለአንድ ወላጅ የመጨረሻው አሰቃቂ ፈተና ነው:: ሁሉቱም [እንድራኒቆስና ሚስቱ አትናስያ] ልጆቻቸውን ታቅፈው ወስደው ቀበሩ::
እንድራኒቆስ ከቀብር በሁዋላ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ምርር ብሎ አለቀሰ:: ግን እንዲህ አለ :-
"አምላከ ኢዮብ! አንተ ሰጠኸኝ:: አንተም ነሳኸኝ:: ስምህ ለዘለዓለም ይባረክ" ብሎ ሔደ:: እናት አትናስያ ግን ከሐዘን ብዛት ልቡናዋ ሊሠወር ጥቂት ቀረው::
የልጆቿ መቃብር ላይ ተደፍታ ስታለቅስ ቅዱስ መልአክ ልቡናዋን ወደ ሰማይ አሳረገው:: ልጆቿ ዮሐንስና ማርያም በገነት ውስጥ ከቅዱሳን ጋር ሐሴትን ሲያደርጉም ተመለከተች:: ወዲያው ወደ ቤት ተመልሳ ለባሏ እንድራኒቆስ ያየችውን ነገረችውና ደስ አላቸው::
እዛው ላይ "ለዚህ ውለታው ከነፍሳችን ውጪ የምንሰጠው የለም" ብለው ሊመንኑ ተስማሙ:: እጅግ ሃብታሞች ነበሩና ነዳያንን ሰብስበው : ሃብት ንብረታቸውን : ቤት ርስታቸውን አካፍለው ወደ ገዳመ አስቄጥስ ሔዱ::
እርሷ ከሴቶች ገዳም : እርሱ ደግሞ ከወንዶቹ ገቡ:: ለ፲፪ [12] ዓመታት በፍጹም ተጋድሎ ለፈጣሪያቸው ተገዙ:: በእነዚህ ዘመናት ተያይተው : አንዱ ስለ ሌላው ሰምቶ አያውቅም:: በጸሎት ግን ያለማቁዋረጥ ይተሣሠቡ ነበር::
ከ፲፪ [12] ዓመታት በሁዋላ የፍቅር አምላክ በሁለቱም ልቡና በተመሳሳይ ሰዓት : ተመሳሳይ ሐሳብን አመጣ:: እርሱ ከአበ ምኔቱ [ታላቁ_አባ_ዳንኤል] : እርሷም ከእመ ምኔቷ አስፈቅደው ወደ ኢየሩሳሌም ከቅዱሳት መካናት ለመባረክ ጉዞ ጀመሩ:: በየፊናቸው ጥቂት እንደተጉዋዙ እርስ በርስ ተያዩ::
እርሷ ለየችው:: እርሱ ግን ጭራሽ ሊለያት አልቻለም:: ይህም ጥበበ እግዚአብሔር ነው:: ፪ [2] ቱም እየተጫወቱ : እየጸለዩ በሰላም ተባርከው ወደ ግብጽ ተመለሱ:: በእነዚህ ጊዜያት ቅድስት አትናስያን የሚለያት አልነበረም:: አካሏ በገድል ከመለወጡ ባሻገር የለበሰችው እንደ ወንድ መነኮሳት ነበር::
ወደ ገዳመ_አስቄጥስ ሲደርሱ ጸጋው ተሰጥቶታልና አባ_ዳንኤል ባልና ሚስት መሆናቸውን አወቀ:: "ለምን አብራችሁ አትኖሩም?" አላቸው:: "እኛ ደስ ይለናል" አሉት:: ከዚያ እርሷ እያወቀችው: እርሱ ሳያውቃት ለ፲፪ [12] ዓመታት አብረው በቅድስና ኖሩ::
ከእነዚህ ዘመናት በሁዋላ ግን ሐምሌ ፳፰ [28] ቀን ቅድስት አትናስያ ታመመች:: አባ ዳንኤል ሥጋውን ደሙን አቀብሏትም ዐረፈች:: ሊገንዟት ሲቀርቡ ቅዱስ እንድራኒቆስ መልኩዋን ልብ ቢለው ሚስቱ ናት::
በአንድ ጊዜ ሚስቱንና የሚወደውን ባልንጀራ በማጣቱ አለቀሰ:: እርሷን ቀብረው ወደ በዓቱ ተመልሶ "ጌታ ሆይ! ውሰደኝ?" አለ:: እርሱም ተከትሏት ዐረፈ:: አባ ዳንኤል እርሱንም ቀብሮ ጥዑም ዜናቸውን ጻፈ::
† አባ ፊልዾስ ዘደብረ ሊባኖስ †
ታላቁ ኢትዮዽያዊ ጻድቅ: ሐዋርያና ሰማዕት አቡነ_ፊልዾስ የጻድቁ አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት ደቀ መዝሙር ሲሆኑ የተወለዱት በምድረ ሽዋ በ፩ ሺህ ፪መቶ ፷፮ [1266] ዓ/ም ነው:: ከልጅነታቸው ጀምረው ምሥጢር ተመራማሪና መጻሕፍትን መርማሪ የነበሩት ጻድቁ የመነኑት ገና በ፲፭ [15] ዓመታቸው ነበር::
+በደብረ_ሊባኖስ በአሞክሮ ለ፫ [3] ዓመታት ቆይተው መንኩሰዋል:: ለ፳፪ [22] ዓመታትም የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ደቀ መዝሙር ሆነው አገልግለዋል:: አቡነ ተክለ ሃይማኖት በ፲፻፫፻፮ [1306] ዓ/ም ነሐሴ ፳፬ [24] ቀን ሲያርፉ የተተኩት አባ ኤልሳዕ ቢሆኑም ለ፫ [3] ወራት ቆይተው ዐርፈዋል::
በ1307 ዓ/ም አቡነ ፊልዾስ የደብረ ሊባኖስ አበ ምኔት [እጨጌ] ሁነዋል:: ገዳሙንም ለ፳፰ [28] ዓመታት መርተዋል:: ከዚያም በዘመነ አፄ ዓምደ ጽዮንና በአፄ ሰይፈ አርዕድ ብዙ ስደት: መከራ: እሥራትና ግርፋት ደርሶባቸዋል:: ምክንያቱ ደግሞ እውነትን መናገራቸውና ነገሥታቱን መገሰጻቸው ነበር:: በስደትም ለ፮ [6] ዓመታት ከ፱ [9] ወራት ቆይተዋል::
ሃገሪቱን በስብከተ ወንጌል ካበሩ ፲፪ [12] ቱ_ንቡራነ_እድ አንዱ የሆኑት እጨጌ አባ ፊልዾስ በተወለዱ በ፸፬ [74] ዓመት ከ፱ [9] ወራቸው በ፲፻፫፻፵፩ [1341] ዓ/ም ዐርፈዋል:: የተቀበሩት በደብረ_ዕንቁ ሲሆን ካረፉ በ፻፵ [140] ዓመት አቡነ_መርሐ_ክርስቶስ ዐጽማቸውን አፍልሰዋል::
ከቅዱሳኑ እንድራኒቆስ ወአትናስያ እና ከጻድቁ አቡነ ፊልዾስ በረከትን ይክፈለን::
ሐምሌ ፳፰ [28] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
፩. ቅዱሳን ጻድቃን እንድራኒቆስና አትናስያ
፪. አቡነ ፊልዾስ ጻድቅ [ዘደብረ ሊባኖስ]
ወርኀዊ በዓላት
፩. አማኑኤል ቸር አምላካችን
፪. ቅዱሳን አበው [አብርሃም : ይስሐቅና ያዕቆብ]
፫. ቅድስት ዓመተ ክክርስቶስ
፬. ቅዱስ ቴዎድሮስ ሮማዊ [ሰማዕት]
"ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል:: ከሚስቱም ጋር ይተባበራል:: ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ:: ይህ ምሥጢር ታላቅ ነው:: እኔ ግን ይህን ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተ ክርትስቲያን እላለሁ:: ሆኖም ከእናንተ ደግሞ እያንዳንዱ የገዛ ሚስቱን እንዲህ እንደ ራሱ አድርጐ ይውደዳት:: ሚስቱም ባሏን ትፍራ::" [ኤፌ.፭፥፴፩] (5:31)
† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]
▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬
40 viewsባሕራን, 19:38