2021-09-25 09:54:43
"ሠርግ አማረኝ"
(absurd wedding)
እንዳልኩሽ አልቀረሁም፡፡
አገባሁ እኮ፡፡
ያውም ላንቺ በገዛሁት ቀለበት፡፡(ዕምነት)
ያውም ላንቺ በገዛሁት ነጭ ሱፍ፡፡(ተስፋ)
ያውም ላንቺ ለጫጉላ በተከራየሁት ቤት፡፡(ፍቅር)
:
:
እና ከመጣሽ ....ሠርግ ልጠራሽ ነበር፡፡
ብቻዬን የደገስኩት፡፡
ብቻዬን ...ሠርግ፡፡
የራሴን ጉልበት ስሜ
ከራሴ ቤት ወጥቼ ራሴ አልቅሼ ራሴን አባብዬ
("ወግ ነው ሲዳሩ ማለቀስ" ብዬ)፡፡
ወግ ላይ ነኝ፡፡
ሰው ይታያሻል አይደለ?
ሲያረግድልኝ፡፡
የኔ ሠርግ ለየት የሚለው ጥቁር በጥቁር ያልለበሰ አለመግባቱ ነው፡፡
(ሞትና ሠርግ አንድ ነው)
የዚህ ሠርግ ልዩ መሆኑ ሙዚቃ የለም፡፡ በቃ የቀጥታ ስርጭት ሙሾ ነው፡፡ ሙሉ ባንድም አለ፡፡
የእናቴ እጅ እና ደረት፡፡ (ሲደቃ)
ይሰማሻል?
እናቴ:- "ለኔ ያርገው"
ሕዝቡ:- "እሰይ"
እናቴ:- "እኔ ልውደቅልህ"
ሕዝቡ:- "እሰይ"
እናቴ:- "ካልገባሁ ከመቃብር"
ሕዝቡ :- "አናስገባም ለቅሶኛ (እናቴን) እደጅ ተኛ፡፡ "
ያው
ከሠርጌ በፊት በላኩልሽ ጽሑፍ
"ብቻሰው ይኑር ብዬሽ የለ"
(ረሳሽው እንዴ)
ሠርጌ ላይ
የሚያለቅሱ
የሚያላቅሱ
የሚያለቃቅሱ
የሞተባቸው ትዝ ያላቸው
"የኔስ ቢሞትብኝ ምን ይውጥኝ?" የሚሉ
አዛኞች
እነ እማማ ድንቁ
እነ እማማ ሰልፌ
አጽናኞች
እነ ዘዉዱ
እነ ነስሓ አባት
አስመሳዮች
በሠርጉ የቀኑ
እነ "የቀድሞ ፍቅረኛ ነን" ባይ
"ቀመሶናል" ባይ
"አናቀውም እንዴ" ባይ
ሁሉም ለሠርጉ የበኩሉን አዋጥቷል፡፡
ሁሉም ገምቷል የቻለውን፡፡
እንዲያውም መዳፌን ላስነበብ ሄጄ የሆነ ቀን ሰውየው እጄን ቢያየው አነሰችበትና፡፡ "ይህ መዳፍ ለመነበብ አልደረሰም" አለኝ፡፡ "እና ዕድሌን እንዴት ልወቅ?" አልኩት
"እጅህ እንዲህ ካነሰ ዕድልህን ገምተው" ያለኝን ትዝ አለሽ፡፡
በቃ እሱ እንደገመተው ሆነ፡፡
የዛሬ....
ግምት ወ ሐሜት
"ትናንት እኮ አይቼው ነበር"
"ስንት ነገር አብረን ልንሰራ ነበር"
"ያው የሴት ጣጣ ነው"
"ሱስ ነው መቼም"
"ያስታውቅ ነበረ፡፡ ስለሞት ያወራ ነበር"
"ሰይጣን ነው"
ሌላም ሌላም....
ትመጫለሽ ሠርጌ ነው
:
:
:
አንገቴን ከገመድ የዳረኩበት ቀን፡፡
* * * * * * * * *
(ነፍስ ይማር አይባልም ራሱን ላልማረ)
➤ከወደዱት በቅንነት ይቀላቀሉን!
@liulzemaryam
@liulzemaryam
@liulzemaryam
76 viewsLiul-ze ማርያም, 06:54