2022-10-07 22:52:44
+++ "ያልተሞቁ ትንንሽ ፀሐዮች" +++
ሕፃናት በአካል መጠን አንሰው ቢታዩም በልባችን ውስጥ የሚይዙት ስፍራ ግን እጅግ በጣም ሰፊ ነው፡፡ ቃል ከአፋቸው ሳያወጡ በፊታቸው ብቻ በሚያሳዩን ፈገግታ ሕይወታችን ላይ ደስታን መዝራት ይችላሉ፡፡ ከዓይናቸው የምትወርደው አንዲት የእንባ ዘለላ ደግሞ ስሜታችንን በኃዘን ምስቅልቅሉን የማውጣት ኃይል አላት፡፡ ሕፃናት ለዚህች ቀዝቃዛ ዓለም የተሰጡ ፀሐዮች ናቸው፡፡ ታዲያ እነዚህ ትንንሽ ፀሐዮች ገና ከመውጣታቸው ብዙም ሳንሞቃቸው መልሰው ሊጠልቁ፣ የልጅነት ቡረቃዎቻቸውን ሳንጠግብ ፈጥነው ሊያንቀላፉ ይችላሉ፡፡ ይህ ሲሆን ኃዘኑ ከባድ ነው፡፡
ከአዋቂ ይልቅ የሕፃን ልጅ ሞት ኃዘን ይጠብቃል። በቤተሰብ ውስጥ ከሁሉም መጨረሻ ይሞታል ተብሎ የሚጠበቀው የቤቱ ሕፃን በመሆኑ ልጁ ከወላጆቹ ቀድሞ ሲሞት እጅግ አስደንጋጭ ይሆናል። ወላጆቹ ከልጃቸው ጋር በነበራቸው ያለፈ ግንኙነት ብቻ ሳይሆን፣ እርሱ ላይ የጣሉት የወደ ፊት ተስፋና ሕልማቸው ሁሉ ከንቱ እንደ ቀረ አስበው አንጀታቸው በኃዘን እሳት ይነዳል፡፡ በተለይ ሟቹ ሕፃን ለወላጆቹ አንድ ወይም ብቸኛ ከሆነ በቤተሰቡ ላይ የሚደርስባቸው የኃዘን ስብራት በቃል የማይገለጽ ጥልቅ ነው። ከአገኛቸውም የውስጥ ሕመም እና የልብ መታወክ የተነሣ ቶሎ ለመጽናናት ይቸገራሉ። ከአብራካቸው ወጥቶ ወደዚህ ዓለም የመጣው ሕፃን እንደ ሌሎቹ ሰዎች ሟች እንደ ሆነ ቢያውቁም እንኳን ሞቱ ግን ጨርሶ የማይታመን ይሆንባቸዋል፡፡
በወዳጁ በአልዓዛር ሞት መንፈሱ ታውኮ ያለቀሰ የክርስቶስ አካሉ የሆነችው ቤተ ክርስቲያን ይህ ዓይነቱ ኃዘን ለገጠማቸው ቤተሰብ "አታልቅሱ" ብላ አታስተምርም። ለሰውነት የማይስማማውን ሕግ ጠብቁ ብላ በልጆቿ ላይ ጨካኝ አትሆንባቸውም። የቤተ ክርስቲያን መምህር የሆነው ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ በአንድ ወቅት :- "በልጆቻችሁ ሞት አታልቅሱ ብዬ አላስተማርኩም። እንደዚህ ተናግሬ እንደሆን የማይቻለውን ነገር እላለሁ። እኔ ልክ እንደ እናንተ ከአንዲት እናት የተወለድኩ መዋቲ ፍጥረት ነኝ። ባሕሪያችሁንም ስለምጋራ በሰው ያለውን ስቃይ እረዳለሁ። የአባቶችን ኃዘን የእናቶችን ማቃሰት አያለሁ። ... በሕሊናቸውም የልጃቸውን ልማዶች፣ የሰውነት እንቅስቃሴዎቹን እና ንግግሮቹን እያስታወሱ እንዴት እንደሚሆኑ አውቃለሁ" ሲል ተናግሮ ነበር።
ምንም ሕፃናትን በሥጋ የማጣት ሕመሙ ከባድ ቢሆንም ወላጆቻቸው ግን ‹‹ተስፋ እንደ ሌላቸው እንደ ሌሎች ደግሞ›› ኃዘን እንዲያበዙ አይፈቀድላቸውም።(1ኛ ተሰ 4፥13) ልጆቻቸው ከዚህ ዓለም ወደ ተሻለው ዘላለማዊ ቤት እንደ ሄዱ በማመን መጽናናት አለባቸው። የሞቱት ልጆቻቸውን መቃብር ሰውራ አታስቀራቸውም። በሰማይም አቀባበል ይደረግላቸዋል። ብዙ ጊዜ ልጆቻቸው በትምህርትም ሆነ በሌሎች ጉዳዮች ከአጠገባቸው ሲርቁ ትልቁ የወላጆች ጭንቀት ባይመቻቸውስ፣ ቢጎሰቁሉስ፣ ፊት ቢነሷቸውስ፣ ክፉ ነገር ቢያገኛቸውስ ... የሚሉት ናቸው። ይሁን እንጂ ከዚህ ዓለም አንቀላፍተው ወደ አምላካቸው ስለ ሄዱት ሕፃናት ግን እንዲህ ብለው ሊያስቡ አይችሉም፡፡ ምክንያቱም ልጆቻቸው ርቀው የሄዱት አመሉን በየሰከንዱ እየቀያየረ ከሚያስቸግር እንግዳ ሰው ዘንድ ሳይሆን፣ በጎነቱ ተሰፍሮ የማያልቅ ቸርነቱ የማይለወጥ ፈጣሪያቸው ጋር ነው። ከእርሱ ጋር ሆነው ማን ያስፈራቸዋል? ማንስ ያስደነግጣቸዋል?!
ሕፃናት የሞቱባቸው ወላጆች ከሚጸጸቱባቸው ምክንያቶች ውስጥ ‹ያለ ጊዜው› መሞታቸውና ልጆቻቸውን አድገው አለማየታቸው ነው፡፡ ይሁን እንጂ የሰውን ሁሉ የዕድሜ ዝርዝር ሰንጠረዥ በእጅ የጨበጡ ይመስል ‹ያለ ጊዜው ነው› እያሉ በድፍረት መናገር አግባብ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ያለ ጊዜው የሚያደርገው ሕይወትም ሞትም የለም፡፡ ነገሩ እኛ በምናስበው ጊዜ ስላልሆነ ‹ያለ ጊዜው›/‹ያልጠበቅነው ነው› ብለን እየተናገርን ካልሆነ በቀር፣ ለእርሱ ሁሉን የሚያከናውንበት ‹‹የሥራ ጊዜ አለው››፡፡(መዝ 119፡126)
"አድጎ ሳላየው" ስለሚለው ጸጸትም፣ እውነት ነው የሕፃናትን እድገት ማየት ደስ ያሰኛል፡፡ ነገር ግን ዋናው ቁም ነገር የልጁ ማደግ ሳይሆን አድጎ የሚኖረው ሰብእና ነው፡፡ የዛሬው ንጹሕ ሕፃን ነገ ሲጎለምስ ቀማኛ እና ደም አፍሳሽ ከሆነ ማደጉ የሚያስቆጭ ይሆናል፡፡ ዛሬ በሕይወት ያሉ ሕፃናት ነገ አድገው ምን ዓይነት ሰዎች እንደሚሆኑ ገና አልታወቀም። "ልጄ በዚሁ በጎነቱ ይቀጥል ይሆን? ወይስ ነገ ከአጉል ሰዎች ጋር ገጥሞ ክፋት ያስተምሩብኝ ይሆን?" የሚለው የብዙ ወላጆች የየቀን ሐሳብ ነው። ሕፃን ልጁ የሞተበት ወላጅ ግን ስለዚህ ነገር አይጨነቅም። የተፈጥሮ ንጽሕናውን ሳያጣ ክፋትን የሚጸየፉ የቅዱሳን ማኅበር ካሉበት፣ የጨለማ ወሬ ከማይወራበት ሰማያዊ እልፍኝ አንድ ጊዜ ገብቶለታልና።
በሕፃናት ልጆች ሞት ከመጠን በላይ ማዘንና በፈጣሪ ላይ መቆጣትን ቅዱሳን አበው በጽኑዕ ያወግዛሉ። በተለይ ቅዱስ ዮሐንስ አፈርቅ በፈጣሪ ላይ የሚደረገው ማጉረምረም "ትልቅ ኃጢአት" እንደ ሆነ ይገልጻል። ድርጊቱም የአምላክን ሥራ ፍጹምነት አለመቀበል በመሆኑ ፈጣሪን ከመስደብ አይተናነስም ይለናል።
ሰባት ወንዶች እንዲሁም ሦስት ሴቶች ልጆቹን በቅጽበት ሲያጣ ፈጣሪውን ያላማረረ ጻድቁ ኢዮብን እስኪ ለአፍታ እናስበው፡፡ ልጆቻቸውን ያጡ ወይም የሚያጡ ብዙ ወላጆች ልጆቹ ከመሞታቸው በፊት የመጨረሻ ቃላቸውን የመስማት፣ እጆቻቸውን የማሻሸትና ጥልቅ በሆነ ቤተሰባዊ ፍቅር የመሳም፣ ከሞቱም በኋላ እንደ ሥርዓቱ ዓይኖቻቸውን የመክደን እና አስከሬናቸውን አጥቦ የመገነዝ እድል አላቸው። ጻድቁ ኢዮብ ግን ከእነዚህ ውስጥ አንዱን እንኳን አላገኘም። ልጆቹ በታላቅ ወንድማቸው ቤት ሲበሉና ሲጠጡ ድንገት ዐውሎ ነፋስ ተነሥቶ ቤቱን ደርምሶ ስለ ገደላቸው እነርሱን ተንከባክቦ የማስታመም እድል አላገኘም። ነፍሳቸውም በወጣችበት ደቂቃ ዓይኖቻቸውን አልከደነም፡፡ የሞቱት ድንጋይ ተጭኗቸው ስለሆነና አስከሬናቸውን ለማውጣት በሚደረገው ቁፋሮ ወቅት አንዳንዶቹ ሕዋሳቶቻቸው በጣም ስለሚጎዱ ሙሉ አካላቸውን የመቅበሩ ነገር ያጠራጥራል፡፡ ታዲያ እነዚህ ሁሉ መከራዎች በአንድ ጊዜ ቢደራረቡበትም ጻድቁ ኢዮብ ግን ‹‹እግዚአብሔርን አልሰደበም፣ መላእክትን አልረገመም››። ይልቅ ወደ ምድር ሰግዶ ‹‹እግዚአብሔር ሰጠ፣ እግዚአብሔርም ነሣ፤ የእግዚአብሔር ስም የተባረከ ይሁን›› ብሎ አምላኩን አመሰገነ። ትንሣኤ ባልተሰበከበት፣ የሰው ተስፋ በቀጨጨበት፣ ሞት ጥላውን ባጠላበት በኦሪት ዘመን የነበረ ኢዮብ እነዚያን ሁሉ ልጆች በአንድ ጊዜ አጥቶ እንዲህ ካመሰገነ፣ ስለ ትንሣኤው የተማርንና "የሙታንን መነሣት ተስፉ እናደርጋለን" ብለን የምንጸልይ፣ የኢዮብን ሩብ ያህል እንኳን መከራ ያልደረሰብን እኛ የሐዲስ ኪዳን ምእመናን ምን ያህል አመስጋኞች ልንሆን በተገባን?
ልጆቻቸው በለጋነት እድሜያቸው የሞቱባቸው ወላጆች ‹‹ልጅህን ሠዋልኝ›› ተብሎ ሲጠየቅ ፈጣሪው ላይ ያላጉረመረመ አብርሃምን ሊያስቡ ይገባቸዋል። የገዛ ልጁን በገዛ እጁ መሥዋዕት አድርጎ እንዲያቀርብለት የተጠየቀው አብርሃም በፈጣሪው ላይ አልተቆጣም። "አባት ያደረከኝ የልጄ ገዳይ እንድሆን ነውን? ከዚህ ሁሉ ባትሰጠኝ በተሻለ ነበር" አላለም። "ከይስሐቅ በሚወለዱት ልጆች ዘርህን አበዛለሁ ብለኸኝ አልነበር። ታዲያ ዛፉን ነቅለህ እንዴት ፍሬውን ልትሰጥ ትችላለህ?" እያለም ፈጣሪውን አልተፈታተነም። አብርሃም ልጁ ይስሐቅን የመሥዋዕት እንጨት አሸክሞት ሲሄድ፣ ‹‹የመሥዋዕቱ በግ ግን
99 viewsወሰንየለው ባህሩ, 19:52