2022-08-29 10:01:15
+++ የኢየሱስን ልብስ ከላዩ ላይ ገፈፉት ±++
በወንጌል የምናውቃቸው ጌታችን የለበሳቸው ልብሶች አራት ሲሆኑ ሦስቱ ከዕለተ ዓርብ በኋላ የለበሳቸው ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ከመያዙ በፊት ለብሶት የነበረው የራሱ ልብስ ነው ፣ ሁለተኛው ሄሮድስ ለመዘበት ያለበሰው የጌጥ ልብስ ነው ፤ ሦስተኛው ወታደሮቹ ያለበሱት ቀይ ልብስ (ከለሜዳ) ነው ፤ አራተኛው ከትንሣኤው በኋላ ሲገለጥ ለብሶ የታየውና ከየት እንደመጣ የሚያጠያይቀው ነጭ ልብስ ነው፡፡ ጌታችንን መስቀል አሸክመው ከጎልጎታ ኮረብታ ካደረሱት በኋላ ለብሷት የኖራትን ልብሱን ገፈፉት፡፡
‹‹ልብሶቹን ወስደው ለእያንዳንዱ ጭፍራ አንድ ክፍል በአራት አከፋፈሉት ፤ እጀ ጠባቡም ከላይ ጀምሮ ወጥ ሆኖ የተሠራ ነበር እንጂ የተሠፋ አልነበረም፡፡ ስለዚህ እርስ በእርሳቸው ፡- ለማን እንዲሆን በእርሱ ዕጣ እንጣጣልበት እንጂ አንቅደደው ተባባሉ፡፡ ይህም ፡- ልብሴን እርስ በእርሳቸው ተከፋፈሉ ፤ በቀሚሴም ላይ ዕጣ ተጣጣሉ የሚለው የመጽሐፍ ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው›› (ዮሐ. ፲፱፥፳፫‐፳፬ መዝ.፳፩፥፲፰)
የጌታችንን ልብስ የገፈፉት ዕርቃኑን ለመስቀል ሲሆን ልብሱን የተከፋፈሉት ደግሞ ሌላ የሚወደው ሰው መጥቶ ልብሱን እንዳይወስደው ነበር፡፡ አብረውት የተሰቀሉትን ወንበዴዎች ልብሶች እንዲህ እንዳደረጉ አልተጻፈም ፤ ይህም ትንቢት የተነገረለት እርሱ ስለሆነና የሚረዳው የሌለ ያማረ ልብስ የማይለብስ ደሃ ነው ብለው በእርሱ ለመሳለቅ እንዲመቻቸው ነበር፡፡
የጌታችን ልብስ ግን እነርሱ እንዳዩት ተራ ልብስ አልነበረም፡፡ ወታደሮቹ አላወቁም እንጂ ከላዩ ገፍፈው በእጃቸው የያዙት ልብስ በታቦር ተራራ እንደ ብርሃን ነጭ የሆነውን ልብሱን ነበር፡፡ (ማቴ. ፲፯፥፪) ይህ ልብስ ከዓሥራ ሁለት ዓመት ጀምሮ ደም ይፈስሳት የነበረችውና ገንዘብዋን ከስራ ልትድን ያልቻለችው ሴት ‹‹የዳሰስሁት እንደሆነ እድናለሁ›› ያለችው ልብስ ነው፡፡ ይህ ልብስ የዚህችን ሴት የደምዋን ምንጭ ያደረቀላት ልብስ ነው፡፡ ጌታችን ሴቲቱን ከፈወሳት በኋላ ‹‹አንድ ሰው ዳስሶኛል ኃይል ከእኔ እንደ ወጣ አውቃለሁ›› ብሎ የተናገረበት ስለዚህ ልብስ ነበር፡፡ (ሉቃ. ፰፥፵፫‐፵፮) ስለዚህ ልብስ ‹‹በገባበት ስፍራ ሁሉ መንደርም ከተማም ገጠርም ቢሆን በገበያ ድውዮችን ያኖሩ ነበር ፤ የልብሱንም ጫፍ እንኳን ሊዳስሱ ይለምኑት ነበር ፤ የዳሰሱትም ሁሉ ዳኑ›› ተብሎ ተጽፎአል፡፡ (ማር. ፮፥፶፮)
ይህንን ተአምረኛ ልብስ የሮም ወታደሮች ተከፋፍለው በእጃቸው ቢይዙትም ደም ይፈስሳት እንደነበረችው ሴት በእምነት ሆነው አልዳሰሱትምና አንዳች ተአምር አላዩም ፤ ‹‹ምንም ተአምር ከልብሱ አላገኙም ፤ ክርስቶስ የማይነገረውን ኃይሉን ገድቦ ነበርና›› ይላል አፈወርቅ፡፡
ሮማውያን ወታደሮች ጌታችን ልብሱን ገፍፈው በአደባባይ ዕርቃኑን አቆሙት ፤ ምድርን በአበባ የሚያስጌጣትን አምላክ ፤ ሰሎሞን እንኳን በክብሩ ለብሶት የማያውቀውን ልብስ ለሜዳ አበቦች የሚያለብሳቸውን አምላክ ልብሱን ገፍፈው ዕርቃኑን አቆሙት፡፡ ‹‹እንደ ሸላቾች ልብሱን ከላዩ ላይ ሁለት ጊዜ ገፈፉት ፤ እርሱም በሸላቾቹ ፊት ዝም እንደሚል በግ ዝም አለ፡፡ ዕርቃናቸውን ከገነት የወጡትን አዳምና ሔዋንን ለማልበስ ልብሱን ተገፈፈ፡፡ እርሱ በመዋረድ ውስጥ ሆኖ በልብሶቹ ዕርቃናቸውን አለበሰ፡፡ የእርሱ ልብሶች ለተዋረዱት አዳምና ሔዋን እንደሚበቁ ያውቅ ነበርና›› ይላል ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ፡፡
በዚህ ሊቅ ምክንያት እስቲ ለአፍታ አዳምና ሔዋን ከገነት ወደ ወጡባት ቅጽበት እንመለስ፡፡ አዳምና ሔዋን ዕርቃናቸውን ለመሸፈን ቅጠል ባገለደሙ ጊዜ ከገነት ሲወጡ ‹‹እግዚአብሔርም ለአዳምና ሔዋን የቁርበት ልብስን አደረገላቸው አለበሳቸውም›› ይላል፡፡ (ዘፍ. ፫፥፳፩)
እግዚአብሔር ከሌላ ዓይነት ልብስ ይልቅ ስለምን የቆዳ ልብስን ሊያደርግላቸው ወደደ? ብለን ስንጠይቅ ወደ ዕለተ ዓርብ ይመራናል፡፡ እንደሚታወቀው ቁርበት የሚገኘው ከእንስሳ ነው፡፡ አንድ ቁርበት ልብስ እንዲሆን በመጀመሪያ እንስሳው ይታረዳል ፣ ደሙ ይፈስሳል ፤ ቆዳው ይገፈፋል ፣ እንዲደርቅ በእንጨት ላይ ተወጥሮ ይሰጣል ፣ በላዩ ላይ ያለው ነገር እስከሚነጻ ድረስ ይለፋል፡፡ ከዚህ ሁሉ ሒደት በኋላ ልብስ ሊሆን ይችላል፡፡
ይህንን ልብስ በገነት ያለበሳቸው አምላክም የእንስሳ ደሙ እንደሚፈስስ ደሙን አፍስሶ ፣ቆዳው እንደሚገፈፍ ቆዳው አልቆ አጥንቱ እስከሚታይ ተገርፎ ፣ ቆዳ እንደሚወጠር በመስቀል ላይ እንደ ቆዳ ተወጥሮ በዕርቃኑ ዕርቃናችንን ሸፈነልን ፤ እርሱም ለእኛ ልብሳችን ሆነልን፡፡ ‹‹የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋል›› እንዳለ ሐዋርያው (ገላ. ፫፥፳፯)
ወታደሮቹ የጌታችንን ልብስ ለአራት ክፍል ተከፋፈሉ፡፡ ቀሚሱ ግን ከላይ ጀምሮ ወጥ ሆኖ የተሠራ ነበርና አንቅደደው ተባብለው ዕጣ ተጣጣሉበት፡፡ እነዚህ ወታደሮች ለቀሚሱ ሳስተው ባለመቅደዳቸው ሳያውቁት ትልቅ ምስክርነት መሰከሩ፡፡ ጌታችን ብዙ መንገላታት ሲደርስበት ባደረው በጨለማው ፍርድ ቤት በአይሁድ ሸንጎ ውስጥ ሊቀ ካህናቱ ቀያፋ ከሕግ ውጪ ልብሱን ቀድዶ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በዚህም ሥራው ሊቀ ካህናት ልብሱ ሊቀደድ እንደማይገባውና ልብሱን መቅደዱም ሊቀ ካህናትነቱ ማለፍዋን የሚያመለክት እንደሆነ በሥፍራው ተመልክተን ነበር፡፡ እነዚህ ወታደሮች የጌታችንን ቀሚስ ባለመቅደዳቸው የሐዲስ ኪዳን ሊቀ ካህናት ክርስቶስ መሆኑንና ልብሱም ፈጽሞ ሊቀደድ እንደማይገባው የሚያሳይ ታላቅ ምሥጢር ተፈጸመ፡፡
ያልተቀደደችውን የመድኃኔ ዓለም ክርስቶስን ቀሚስና ለአራት የተከፋፈለውን ልብሱን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ብዙ አስተምረውበታል፡፡ ‹ከላይ ጀምሮ ወጥ ሆኖ የተሠራ› የሚለው ቃል ክርስቶስ ‹ሰው ብቻ ሳይሆን ከላይ የመጣ መለኮት መሆኑን ያመለክታል› ብሎ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አብራርቶታል፡፡ ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬምም ቀሚስ የተባለ መለኮቱ ሊቀደድ (ከሥጋው ተለይቶ ሊከፈል) አይችልም ፤ ለአራት የተከፈለው ልብሱ ግን አራት ሆና የተጻፈችውና በአራቱም ማዕዘን የምትዳረሰው ወንጌል ምሳሌ ናት ሲል ተርጉሞታል፡፡
ይህ የሊቃውንቱ ትርጓሜ ከእግዚአብሔር መንፈስ የተገኘ መሆኑም በቤተ ክርስቲያን ታሪክም ተረጋግጧል፡፡ ዐሥራ ሰባተኛው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ አርዮስ የተባለውን በኩረ መናፍቃን ካወገዘው በኋላ የተፈጸመው ነገር ይህን ግልጥ አድርጎ ያሳያል፡፡ አርዮስ ከውግዘቱ በኋላ በፓትርያርኩ ላይና በቤተ ክርስቲያኒቷ ላይ ከንጉሥ መክስምያኖስ ጋር ሴራን ተብትቦ ቅዱስ ጴጥሮስን አሳስሮት ነበር፡፡ ከዚያም አርዮስ ፓትርያርኩ ጴጥሮስ ሊገደል እንደሚችል ሲረዳ እንዳወገዘው እንዳይሞት የዋሃን ካህናትን አማላጅ አድርጎ ምሕረት ሊያስለምነው ሞከረ፡፡ ፓትርያርኩም ለአርዮስ አማላጆች ሆነው ለመጡት ካህናት አርዮስን ከውግዘቱ መፍታት እንዳይችል ያደረገውን ራእይ እንዲህ ሲል ነገራቸው፡-
152 views07:01