2022-07-14 00:26:27
† እንኩዋን ለአጋእዝተ ዓለም ሥላሴ እና ለቅዱሳን አበው አብርሃም: አባ ሲኖዳ እና አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ †
† ሥሉስ ቅዱስ †
በአንድነቱ ምንታዌ [ሁለትነት] : በሦስትነቱ ርባዔ [አራትነት] የሌለበት የዘለዓለም አምላክ: የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው:: አብ : ወልድ : መንፈስ ቅዱስ በስም: በአካል: በግብር ሦስትነት: በባሕርይ: በሕልውናና በፈቃድ አንድነት የጸኑ ናቸው:: በዚህ ጊዜ ተገኙ: በዚህ ጊዜ ያልፋሉ አይባሉም:: መጀመሪያም መጨረሻም እነርሱ ናቸውና::
ርሕሩሐን ናቸውና በእናት ሥርዓት " ቅድስት_ሥላሴ " እንላቸዋለን:: የሚጠላቸው [የማያምንባቸውን] አይጠሉም:: የሚወዳቸውን ግን እጽፍ ድርብ ይወዱታል:: በቤቱም መጥተው ያድራሉ::
ከፍጥረታት ወገን ከእመቤታችን ቀጥሎ የአብርሃምን ያህል በሥላሴ ዘንድ የተወደደ ፍጡር የለም:: አባታችን ቅዱስ አብርሃም የደግነት ሁሉ አባት ነውና በኬብሮን በመምሬ ዛፍ ሥር ሥላሴን ተቀብሎ አስተናግዷል:: ሥላሴ አኀዜ ዓለም [ዓለምን በእጁ የያዘ] ነው:: ነገር ግን በፍቅር ለሚሻው በፍቅር ይመጣል::
አባታችን አብርሃም በ፺፱ [99] ዓመቱ: እናታችን ሣራ በ፹፱ [89] ዓመቷ ሥላሴን በድንኩዋናቸው አስተናገዱ:: አብርሃም እግራቸውን አጠበ:: [ወይ መታደል!] በጀርባውም አዘላቸው:: [ድንቅ አባት!] ምሳቸውንም አቀረበላቸው:: እንደሚበሉ ሆኑለት:: በዚያው ዕለትም የይስሐቅን መወለድ አበሠሩት:: ቅድስት ሣራ ሳቀች:: እንደ ዘንድሮ ወገኖቻችን የማሾፍ አይደለም:: ደስታና ጉጉት የፈጠረው እንጂ:: ሥላሴ "ምንት አስሐቃ ለሣራ በባሕቲታ" ብለው ነበርና በዚህም ምክንያት ነው "ይስሐቅ" የተባለው::
ሥላሴን ያስተናገደች ድንኩዋን [ሐይመት] የድንግል እመቤታችን ማርያም ምሳሌ ናት:: በድንግል ላይ አብ ለአጽንኦ: መንፈስ ቅዱስ ለአንጽሖ: ወልድ በተለየ አካሉ ለሥጋዌ በእርሷ ላይ አርፈዋል / አድረዋልና::
† ታላቁ አባ ሲኖዳ †
የባሕታውን ሁሉ አለቃቸው ታላቁ ቅዱስ ሲኖዳ :-
¤ በ፬ [4] ኛው መቶ ክ/ዘመን የተወለደ
¤ በእናቱ ማሕጸን ሳለ መላእክት በሰይፈ እሳት ይጠብቁት የነበረ
¤ የታላቅነት ትንቢት የተነገረለት
¤ ገና ሳይወለድ ሥውራን አበው የሰገዱለት
¤ በሕጻን ሰውነቱ ጾምና ጸሎትን የጀመረ
¤ የልጅነት ቁርስና ምሳውን ለነዳያን ያካፍል የነበረ
¤ በ፱ [9] ዓመቱ ወደ በርሃ የመነነ
¤ የአባ አብጐል ደቀ መዝሙር የሆነ አባት ነው::
ሲመነኩስም በእግዚአብሔር ትእዛዝ የሠለስቱ_ደቂቅ አስኬማ: የኤልያስ ቆብዕ እና የመጥምቁ ዮሐንስ ቅናትን [መታጠቂያ] ከያሉበት መላእክት አምጥተውለት የመነኮሰ
¤ ዓለምን በሙሉ በጸሎቱ ይጠብቅ የነበረ
¤ የግብፅን በርሃ በብርሃን የሞላ
¤ በርካታ ድርሰቶችን የደረሰ
¤ ያለ ማቇረጥ በየቀኑ ከ፻ [100] ዓመታት በላይ ከጌታችን ክርስቶስ ጋር የተነጋገረ
¤ ደመናትን ተጭኖ ይሔድ የነበረና
¤ ያለ ዕረፍት ለ፩፻፲፩ [111] ዓመታት ከ፪ [2] ወራት ፈጣሪውን ያገለገለ አባት ነው::
በዚህም ምክንያት አንድ ቀን ገዳማውያን ሁሉ እየሰሙ እንዲህ የሚል ቃል ከሰማይ መጣ:: "ሲኖዳ ተሠይመ አርሲመትሪዳ "[ሲኖዳ አርሲመትሪዳ ሆኗል:: ማለትም ለባሕታውያን ሁሉ አለቃ ሁኖ ተመርጧል ማለት ነው::]
ቅዱሱ የጌታችንን እግር እያጠበም ይጠጣ ነበር:: በዚህች ዕለት በ፩፻፳ [120] ዓመቱ ጌታችን ወርዶ ሲያሳርገው አቡነ ኪሮስ "ታላቅ ምሰሶ [ታላቅ ዛፍ] ወደቀ" ብለው አልቅሰዋል:: ሲኖዳ ማለት "ደግ ሰው" ማለት ነው::
† አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ †
[GIYORGIS_OF_SEGLA]
ታላቁ ኢትዮዽያዊ ሊቅና ጻድቅ የተወለደው ወሎ ጋስጫ ውስጥ በ1358 ዓ/ም ነው:: ከልጅነቱ ትምሕርት አልገባሕ ቢለውም በልቡናው ግን ቅን እና ታዛዥ ነበር:: መምሕሩ "ትምሕርት አይገባውምና ውሰዱት" ቢላቸው "የእግዚአብሔር ነውና ያገልግላችሁ" ብለው መለሱት:: መገፋቱን የተመለከተ አባ ጊዮርጊስ እመቤታታችንን ከልቡ ይወዳት ነበረና ይማጸናት ገባ::
ቀን ቀን ገዳሙን ሲረዳ: እሕል ሲፈጭና ሲከካ: ላቡንም ሲያፈስ ውሎ ሌሊት ደግሞ ሲጸልይ ያነጋ ነበር:: ድንግል እመቤታችን ጸሎቱን ሰምታለችና ቅዱስ_ዑራኤልን አስከትላ መጣችለት:: በንጹሐት እጆቿ ባርካው ምሥጢርንም ነገረችው:: "ወነገረቶ ሐምስተ ቃላተ" እንዲል:: ጽዋዐ ልቡናን አጠጥታው ተሠወረችው::
ከዚህች ሰዓት ጀምሮ አባ ጊዮርጊስ ፍጹም ተለወጠ:: በጽድቁ ላይ የሊቅነትን ካባ ደረበ:: ቅዱሳት መጻሕፍትን ይተነትናቸው: መናፍቃንንም ምላሽ ያሳጣቸው ገባ:: የተረጐማቸውና ያተታቸውን ሳይጨምር ፵፩ [41] ድርሰቶችን ደረሰ:: [መጽሐፈ ሰዓታት: መጽሐፈ ምሥጢር: አርጋኖን: ኆኅተ ብርሃን: ውዳሴ መስቀል: ወዘተ . . . የእርሱ ድርሰቶች ነበሩ]
ስለ ሃይማኖትም ጠበቃ ነበር:: ስለ ቅድስናውና ውለታው የኢ/ኦ/ተ/ቤ እንዲህ ትጠራዋለች :-
፩. ሊቀ_ሊቃውንት
፪. በላዔ_መጻሕፍት
፫. ዓምደ_ሃይማኖት
፬. ዳግማዊ_ቄርሎስ
፭. ጠቢብ_ወማዕምር
ጻድቁ ሊቅ በተወለደ በ፷ [60] ዓመቱ በ፲፻፬፻፲፰ [1418] ዓ/ም በዚህች ቀን ዐርፏል:: አባ ጊዮርጊስ የተወለደውም ያረፈውም ሐምሌ ፯ [7] ቀን ነው::
የሥላሴ ቸርነት: የአብርሃም ደግነት: የአበው አባ ጊዮርጊስና አባ ሲኖዳ በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን::
ሐምሌ ፯ [7] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
፩. ቅዱሳን አብርሃምና ሣራ [ሥላሴን ያስተናገዱ]
፪. ብሥራተ ልደተ ይስሐቅ
፫. ታላቁ አባ ሲኖዳ [የባሕታውያን ሁሉ አለቃ]
፬. አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ [ሊቀ ሊቃውንት: ኢትዮዽያዊ
የሃይማኖት ምሰሶ]
፭.ቅዱስ አግናጥዮስ ዘአንጾኪያ [ምጥው ለአንበሳ]
፮. አባ መቃቢስ
፯. አባ አግራጥስ
ወርሐዊ በዓላት
፩. አባ ዳንኤል ዘገዳመ ሲሐት
፪. አባ ባውላ ገዳማዊ
፫. ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ
"እግዚአብሔርም ለአብርሃም ተስፋ በሰጠው ጊዜ :- 'በእውነት እየባረክሁ እባርክሃለሁ:: እያበዛሁም አበዛሃለሁ' ብሎ ከእርሱ በሚበልጥ በማንም ሊምል ስላልቻለ በራሱ ማለ:: እንዲሁም እርሱ ከታገሠ በሁዋላ ተስፋውን አገኘ:: " [ዕብ.፮፥፲፫] (6:13)
የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ: የእግዚአብሔርም ፍቅር: የመንፈስ ቅዱስም ሕብረት ከሁላችሁ ጋር ይሁን:: አሜን::" [ቆሮ.፲፫፥፲፬] (13:14)
† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
" ፍቅር ያጌብረኒ ከመ እንግር ዜናሆሙ ለቅዱሳን":: /የቅዱሳንን ዜና [ታሪክ] እንድመሰክር ፍቅር ያስገድደኛል:: አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ /መጽሐፈ ምሥጢር/
[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]
▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬
66 views21:26