ከሰሞኑ በስፋት የተከሰተው ጉንፋን መሳይ የበሽታ ምልክት ኮቪድ 19 የመሆን እድሉ ከፍተኛ ነው ተባለ
ከሰሞኑ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ጉንፋን መሳይ የበሽታ ምልክት በስፋት መከሰቱንና ይህም የመተንፈሻ አካላትን የሚያጠቃ ጉንፋን መሳይ የበሽታ ምልክት ኮቪድ 19 የመሆን እድሉ ከፍተኛ መሆኑን የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አስታውቋል፡፡
ጉንፋን መሰሉን የበሽታ ምልክት ሁሉ ኮቪድ19 ነው ማለት ባይቻልም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገሪቱ የኮቪድ 19 ስርጭት እየጨመረ መጥቷል፤ የበሽታ ምልክቱ ኮቪድ-19 የመሆን እድሉ ከፍተኛ ስለሆነ ህብረተሰቡ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ጥሪ ቀርቧል፡፡
በተለይ ባለፉት አምስት ተከታታይ ሳምንታት በኢትዮጵያ የኮቪድ-19 ስርጭት የመጨመር አዝማሚያ ማሳየቱን ሲሆን ከ1 በመቶ በታች ወርዶ የነበረው የስርጭት ምጣኔው አሁን ላይ ግን ወደ 4 ነጥብ 5 በመቶ ማሻቀቡን ተነገሯል፡፡
ለአብነትም ባለፉት ሰባት ቀናት ለ11 ሺሕ 920 ሰዎች ምርመራ ተደርጎ በ662ቱ ላይ ኮቪድ-19 መገኘቱ የተገለፀ ሲሆን ህብረተሰቡ ከመያዙ በፊት ለመከላከል የሚያስችሉ ዘዴዎችን መጠቀምና ምልክቱ ሲታይም ፈጥኖ መመርመር እንደሚገባው ተጠቁሟል።(ዋልታ)
@tikvahethmagazine