2022-08-20 18:39:40
እዚህ ጋር "ዳዊት" ተብሎ የሚጠራው የእሰይ ልጅ ሳይሆን፥ መሲሁ ነው። ከላይ እንደተነጋገርነው፥ በመጽሐፍ ቅዱስ መሲሁ በብዙ ስሞች ተጠርቷል። ከነዚህ ስሞች መካከል አንዱ "ዳዊት" ነው። እግዚአብሔር ለዳዊት ከሆዱ ፍሬ በዙፋኑ እንደሚያስቀምጥ ስለማለለት (2 ሳሙ 7:12-16 መዝ 132:11) በእርሱ ዙፋን ላይ የሚቀመጠው መሲሁ፥ ዳዊት ተብሎ ተጠርቷል። (ሆሴ 3:5 ኤር 30:9 ሕዝ 34:23-24) ስለዚህ በዚህ ቦታም "ዳዊት" የሚለው እርሱን ነው።
ቀጥሎም፥ እርሱን ለወገኖች አለቃ አድርጌ ሰጥቼዋለሁ ይላል። "አለቃ" ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ "נָגִיד/ናጊድ" ሲሆን፥ በዳን 9:25 ላይ ያለው ራሱ ቃል ነው። ይህ ማለት ሁለቱ ክፍሎች ተያያዥነት አላቸው ማለት ነው። የሚመጣው አለቃው ቅቡዕ፥ ለወገኖች የተሰጠው አለቃው ዳዊት (መሲሁ) ነው። ይህ ከምንም ዳንኤል 9 ስለ ክርስቶስ የሚናገር ትንቢት መሆኑን ያረጋግጣል።
ከዚህም ባሻገር፥ በኢሳ 55:3 ላይ በዳዊት አማካኝነት የዘላለም ቃል ኪዳን ከእነርሱ ጋር እንደሚገባ እግዚአብሔር ይናገራል። ይህ በዳን 9:24 ላይ ካለው ሀሳብ ጋር ይገናኛል። ዘላለማዊ ጽድቅ የሚመጣው በዚህ ዘላለማዊ ቃል ኪዳን አማካኝነት ነውና። እግዚአብሔር ዘላለማዊ ኪዳንን በመሲሁ አማካኝነት ማምጣቱ በብዙ ቦታ የተነገረ ነገር ሲሆን (ኤር 31:31) በዳንኤል 9 የተተነበየው ዘላለማዊ ጽድቅ የዚሁ ኪዳን አካል ነው። ይህ ዳንኤል 9 መሲሐዊ ትንቢት ለመሆኑ ተጨማሪ ማሳያ ነው
"አባቶቻችሁም በኖሩበት ለባሪያዬ ለያዕቆብ በሰጠኋት ምድር ይኖራሉ፤ እነርሱና ልጆቻቸው የልጅ ልጆቻቸውም ለዘላለም ይኖሩባታል፤ ባሪያዬም #ዳዊት ለዘላለም #አለቃ ይሆናቸዋል።"
(ትንቢተ ሕዝቅኤል 37:25)
በዚሁ ስፍራም መሲሁ አለቃ መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር እንመለከታለን። እግዚአብሔር በሚመጣው ዘመን ባሪያው ዳዊት (መሲሁ) ለዘላለም አለቃ እንደሚሆን ይናገራል። በዚህ ስፍራ አለቃ የሚለው የዕብራይስጥ ቃል "נָשִׂיא/ናሲያ" ሲሆን (H5387) በዳን 9:25 ላይ ከተጠቀሰው ቃል ጋር አንድ አይነት ትርጉም ነው ያለው። አዛዥ፥ ገዢ፥ መሪ የሚል ትርጉም ነው ያለው።
እግዚአብሔር ለዘላለም መሲሁ የእስራኤል ሕዝብ ገዢ ይሆናል በማለት የተናገረው፥ መሲሁ ዘላለማዊ ዙፋን ስላለው ነው (መዝ 45:6-7 ዳን 7:13-14 ኢሳ 9:6-7) በተጨማሪም መሲሁ ለወገኖች (ለእስራኤል ሕዝብ) አለቃ እንደሚሆን ተነግሯል (ኢሳ 55:4) ስለዚህ በሕዝ 37 አለቃ ይሆናል የተባለው መሲሁ ለመሆኑ ጥርጣሬ የለውም።
በዳን 9:25 ግን የሚመጣው ቅቡዕ፥ አለቃ እንደሆነ ተገልጿል። ይህ በግልፅ እንደሚያሳየው፥ የሚመጣው ቅቡዕ አለቃ በእስራኤል ለዘላለም አለቃ የሚሆነው መሲሁ ነው። ማለትም፥ ዳንኤል 9:24-27 ፍጹም መሲሐዊ ትንቢት ነው ማለት ነው።
በሕዝ 37:25 የምንመለከተው ሀሳብ በሕዝ 34:24 ላይም ተደግሞ እንመለከታለን፦
"እኔም እግዚአብሔር አምላክ እሆናቸዋለሁ ባሪያዬም #ዳዊት በመካከላቸው #አለቃ ይሆናል፤ እኔ እግዚአብሔር ተናግሬአለሁ።"
(ትንቢተ ሕዝቅኤል 34:24)
ልክ እንደ ሕዝቅኤል 37፥ በዚህ ስፍራም መሲሁ "አለቃ" ተብሎ ተጠርቷል። ዳን 9:25 ላይ የተነገረለት ቅቡዕ የተጠራበት ስም ነው። ይህ በይበልጥ፥ ዳን 9:24-27 መሲሃዊ ትንቢት መሆኑን ያሳያል
6) ይቆረጣል
በዳንኤል 9 ስለ ሚመጠው ቅቡዕ ከተነገሩት ሌሎች ነገሮች መካከል፥ እንደሚቆረጥ ነው።
"ከስድሳ ሁለት ጊዜ ሰባትም በኋላ #መሢሕ #ይገደላል፥ በእርሱም ዘንድ ምንም የለም፤ የሚመጣውም አለቃ ሕዝብ ከተማይቱንና መቅደሱን ያጠፋሉ፤ ፍጻሜውም በጐርፍ ይሆናል፥ እስከ መጨረሻም ድረስ ጦርነት ይሆናል፤ ጥፋትም ተቀጥሮአል።"
(ትንቢተ ዳንኤል 9:26)
"ይገደላል" ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል "כָּרַת/ካሬት" ሲሆን (H3772) በቀጥታ ሲተረጎም "መቆረጥ" ማለት ሲሆን፤ መገደልን፥ መሞትን የሚያመለክት ቃል ነው። ቃሉ በመጽሐፍ ቅዱስ መሞትን እና በተለይም በሰው እጅ መገድልን ለማመልከት ጥቅም ላይ ውሏል። ለምሳሌ፦
"ቴማን ሆይ፥ ሰዎች ሁሉ ከዔሳው ተራራ #በመገደል #ይጠፉ ዘንድ ኃያላንህ ይደነግጣሉ።"
(ትንቢተ አብድዩ 1:9)
በዚህ ቦታ እግዚአብሔር በኤዶማዊያን ላይ ስለሚተላለፈው ፍርድ ሲናገር እንመለከታለን። እርሱም፥ ተገድለው እንደሚጠፉ ነው። "ይጠፉ" የሚለው ቃል በዳን 9:24 ላይ "ካሬት" ተብሎ የተተረጎመው ራሱ ቃል ሲሆን፥ በሰው እጅ ተገድሎ መጥፋትን ያመለክታል። ለዚያ ነው "ተገድለው" የሚለው። ሌላ ምሳሌ፦
"ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። እነሆ፥ #ሰይፍ አመጣብሃለሁ፥ ሰውንና እንስሳንም ከአንተ ዘንድ #አጠፋለሁ።"
(ትንቢተ ሕዝቅኤል 29:8)
በዚሁ ስፍራም፥ እግዚአብሔር በግብፅ ላይ ስለሚመጣው ፍርድ ሲናገር እንመለከታለን። እርሱም፥ ሰይፍን እንደሚያመጣበትና ሰውንና እንስሳውን እንደሚያጠፋበት ይነግረዋል። አሁንም "አጠፋለሁ" የሚለው የዕብራይስጥ ቃል በዳን 9:25 ላይ ያለው "ካሬት" የሚለው ቃል ነው። በዚህ ቦታ ግብጻውያን በሰይፍ እንደሚገደሉ ለማመልከት ጥቅም ላይ ውሏል። ይህ እንደሚያሳየው፥ ይህ ቃል በሰው እጅ መገደልን ያመለክታል።
በዳን 9 የተነገረለት ቅቡዕ ደግሞ ይቆረጣል ተብሏል። ይህ ማለት ይሞታል፥ በሰው እጅ ይገደላል ማለት ነው።
መጽሐፍ ቅዱስ እንድሚነግረን ደግሞ፥ መሲሁ ለኀጢአታችን ሲል ይሞታል። ይህ በዳን 9 ላይ የተነገረለት ቅቡዑ መሲሁ መሆኑን በሚገባ ያረጋግጣል፦
"ከክፉዎችም ጋር #መቃብሩን አደረጉ፥ ከባለጠጎችም ጋር #በሞቱ ሆኖም ግፍን አላደረገም ነበር፥ በአፉም ተንኮል አልተገንበትም ነበር።"
(ትንቢተ ኢሳይያስ 53:9)
በዚህ ቦታ ላይ እንደምናነበው፥ መሲሁ መቃብሩ ከክፉዎች ጋር ሞቱ ከባለጠጎች ጋር ይሆናል። ማለትም መሲሁ ይሞታል ማለት ነው። ይህ መሲሁ እንደሚሞት የተነገረ ቀጥተኛ ምስክርነት ነው። ስለዚህ በዳን 9:25 የተተነበየለት ቅቡዑ የሚቆረጠው፥ በኢሳ 53:9 ላይ የተተነበየለት መሲህ ስለሆነ ነው። ይህ ዳን 9:24-27 ፍጹም መሲሃዊ ትንቢት ለመሆኑ የማይታበል ማስረጃ ነው።
"በማስጨነቅና በፍርድ ተወሰደ፤ ስለ ሕዝቤ ኃጢአት ተመትቶ ከሕያዋን ምድር እንደ #ተወገደ ከትውልዱ ማን አስተዋለ?"
(ትንቢተ ኢሳይያስ 53:8)
በዚሁ ስፍራም መሲሁ ከሕያዋን ምድር ተመትቶ እንደሚወገድ ተተንብዮ እንመለከታለን። "ተመትቶ" የሚለው የዕብራይስጥ ቃል "גָּזַר/ጋዛር" ሲሆን፥ በዳን 9:25 ላይ ከተጠቀሰው ቃል ጋር አንድ አይነት ትርጉም ነው ያለው። "መቆረጥ" ማለት ሲሆን፤ መሞትን፥ በሰው እጅ መገደልን የሚያመለክት ቃል ነው።
ይህ ራሱ ቃል፥ በመጽሐፍ ቅዱስ በሰው እጅ መገደልን ለማመልከት ጥቅም ላይ ውሏል፦
"ለዘላለም እንደማታስባቸው፥ እንደ #ተገደሉና በመቃብር ውስጥ እንደ ተጣሉ፥ በሙታን ውስጥ እንዳሉ የተጣልሁ ሆንሁ፤ እነርሱም ከእጅህ #ተለዩ።"
(መዝሙረ ዳዊት 88:5)
"ተለዩ" የሚለው ቃል በኢሳ 53:8 ላይ ያለው ራሱ ቃል (ጋዛር) ሲሆን፤ መገደልን፥ መሞትን ለማመልከት ጥቅም ላይ ውሏል። ይህ ክፍል ስለ ተገደሉ ሰዎች የሚናር ክፍል ነውና፥ ቃሉ በሰው እጅ መሞትን ለማመልከት ጥቅም ላይ እንደዋለ እርግጠኛ መሆን እንችላለን።
385 views15:39