2022-08-29 19:18:26
ሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ
ቅዱስ ጊዮርጊስ ታማኝ የክርስቶስ አገልጋይ ነው
ሼር በማድረግ የቅዱሳንን ክብር
እንመስክር
•••
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከክርስቲያን ቤተሰብ የተገኘ ወጣት ነው። በሕይወት ዘመኑ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘ ፣ የወጣትነት ዘመኑን እግዚአብሔር እንዲከብርበት በቅድስና የኖረ ፣ ከባድ የሰማዕትነትን ተጋድሎ በጽናት የፈጸመ ታማኝ የክርስቶስ ጃንደረባ ነው።
•••
ቅዱስ ጊዮርጊስ ፍቅርን ፣ ትህትናን ፣ ሰብአዊ ርኅራኄንና በጎነትን ወላጅ እናቱ ከቅዱሳት መጻሕፍት በሚገባ ታስተምረው ስለነበር ለሰዎች ሁሉ እጅግ መልካምና ቀና አሳቢ ወጣት ሆኖ አደገ። የነበረውን መልካም ባህሪና በጎ አስተሳሰብ ተመልክተውም በሀገሩ ላይ ለሕዝብ ዕንባ ጠባቂነት አድርገው ለሹመት እንዳበቁት የወጣትነት ዘመን ታሪኩ በሰፊው ይገልጻል። ቅዱስ ጊዮርጊስ ገና በወጣትነቱ የክርስቶስ ፍቅር በልቡ የተሳለበት ፣ የመስቀሉ ውለታ በኅሊናው የታተመበት ጠንካራ ክርስቲያን ነበር። በዚህ ዘመን በዘር ፣ በብሔር ተከፋፍለን በዓለም ርኩሰት ውስጥ ለወደቅን ወጣቶች ብዙ ቁም ነገር ሕይወቱ ያስተምረናልና ጽሑፋን በጥንቃቄ እናንብ።
•••
ቅዱስ ጊዮርጊስ በጥንትዋ ካፓዶቂያ በአሁኗ ቱርክ በሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከክርስቲያን ቤተሰቦች ተወለደ።አባቱ በሞት ሲያልፍ እናቱ ቅዱስ ጊዮርጊስን ይዛ ወደ ትውልድ ሀገሯ ወደ ፍልስጠኤም ምድር ተመለሰች። ጊዮርጊስም በዚያው አደገ ኋላም የሮም ወታደር ሆኖ ሳለ ለሕዝብ ዕንባ ጠባቂነት ማዕረግ ተሾመ። በወቅቱ የሮም ግዛት ንጉሥ የነበረው ዲዮቅልጢያኖስ ክርስቲያኖችን ለማሳደድ ከፍተኛ ዘመቻ ጀመረ። በ303 ዓ.ም ቅዱስ ጊዮርጊስ ንጉሡ በክርስቲያኖች ላይ የሚፈጽመውን ማሳደድ እንዲያቆም አጥብቆ ይቃወመ ስለነበር የነበረውን ስልጣን በተቃውሞ ለቀቀ።
•••
እዚህ ላይ ማስተዋል ያለብን ንጉሡ ሮም ታስተዳድራቸው በነበሩ ሀገራት ሁሉ ላይ ክርስቲያኖችን ያስጨንቅ ያነበረው ጣዖት አምላኪ በመሆኑ ነው። በግዛቱ ላይ ታላቅ አምባገነናዊ አዋጅ አውጆም ነበር « አብያተ ክርስቲያን ይትሃጸዋ አብያተ ጣዖታት ይትርሃዋ » « አብያተ ክርስቲያናት ይዘጉ አብያታ ጣዖታት ይከፈቱ » የሚል መመሪያ በየሀገሩ አስተላለፈ ይህንን የተቃወሙ ክርስቲያኖችን ሁሉ ወታደሮች ይዘው በግፍ እያሰቃዩ እንዲገድሏቸው ፣ ሰውነታቸውን ሰም እየለቀለቁ በአደባባይ እንደ ጧፍ እንዲያቀልጧቸው ፣ ከአንበሶች ጋር እያታገሉ ሰባብረው እንዲበሏቸው ያደርግ ነበርና ቅዱስ ጊዮርጊስ ይህንን ክፉ የአጋንንት ሥራ አጥብቆ ተቃወመ።
•••
ክርስቲያኖች ልብ በሉ ክርስትና እኛ ዘመን የደረሰው አልጋ በአልጋ ሆኖ አይደለም በብዙ መከራና ስቃይ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ዋጋ እየተከፈለበት ነው። የክርስቶስን ጌትነትና አዳኝነት ሳይፈሩና ሳያፍሩ በነገሥታትና በአሕዛብ ፊት ወንጌልን በሰበኩ እውነተኛ አማኞች ታላቅ ተጋድሎ ዛሬ በክብር የምንጠራበት ክርስትና የጨለማውን ዘመን በመንፈስ ቅዱስ ኃይልና ሥልጣን ተሻግሮ በብርሃን ሰረገላ የክብሩን ወንጌል ለእኛ አድርሷል። የቀደሙ ክርስቲያኖች ወንጌልን በአፍ ብቻ ሳይሆን በሕይወታቸው የኖሩ፣ በደሙ የዋጃቸውን ጌታ በደማቸው ያከበሩ ታላቅ የእምነት አርበኞች ናቸው።
•••
ቅዱስ ጊዮርጊስ በክርስቲያኖች ላይ የወጣውን የንጉሡን ትህዛዝ ቀዶ ስለጣለው ይህ ድርጊት ንጉሥ ዲዮቅልጢያኖስ አጅግ አናደደው ጊዮርጊስ እስር ቤት ውስጥ እንዲጣልና በዚያም ከፍተኛ ስቃይ እንዲፈጸምበት አደረገ ፤ ሰማዕቱ ግን እምነቱን ፈጽሞ አልካደም። በታሪክ እንደተመዘገበው ቅዱስ ጊዮርጊስ እጅግ አሰቃቂና አስከፊ በሆነ መንገድ በርካታ ስቃዮችን ተቀብሏል። መርዝ እንዲጠጣ አስገድደውታል ፣ ሁለት የሾለ ብረት ባለው መንኮራኩር መሐል አስገብተው ሰባብረውታል ፣ በትልቅ ድስት ውስጥ የቀለጠ ብረት አፍልተው ጊዮርጊስን እዛ ውስጥ ጨምረው አሰቃይተውታል። ሰማዕቱን ለመግደል ያልሞከሩት ሙከራ አልነበረም ፤ ነገር ግን በድንቅ ተአምር ሌሊት ቁስሉን ክርስቶስ ራሱ ይፈውሰው ነበር። ሰማዕቱ ለጣዖት መስዋዕት እንዲያቀርብ በንጉሡ በተገደደ ጊዜ ቅዱስ ጊዮርጊስ ግን ለሮም ጣዖታት መስዋዕትን ከማቀረብ ይልቅ ሕይወቴ ቢያልፍ እመርጣለሁ ብሎ ተናገረ። ሕዝቡም በእርሱ ላይ የሚሆነውን ለማየት ተሰብስበው ሲመለከቱ ፤ጊዮርጊስ ግን የክርስቲያኖች አምላክ ወደ ሚሆን ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር። እየጸለየም ሳለ ወዲያውኑ እሳት ከሰማይ ወደቀ ፣ ታላቅ የምድር መናወጥም ሆነ ፣ የጣዖት ካህናቱ ፣ ጣዖታቱና የጣዖታቱ መቅደሶቹ ሁሉ ወደሙ። ሆኖም እግዚአብሔር ሰማዕቱ ከዚህ በላይ እንዲሰቃይ አልፈለገምና ስለ እምነቱ ጽናት በሰማዕትነት ክብር እንዲያልፍ ሆነ።
•••
በመጨረሻም ቅዱስ ጊዮርጊስን በዛሬዋ ልዳ ከተማ ጎዳና ላይ እየጎተቱ ወስደው እስዛው በፍልስጠኤም ምድር አንገቱን ሰየፉት። የንጉሡ ዲዮቅልጢያኖስ ሚስት ግን በቅዱስ ጊዮርጊስ የእምነት ጽናት ውስጥዋ እጅግ ተማርኮ ነበርና እርሷዋም በመጨረሻ ክርስቲያን ሆነች። ስለ ክርስትናዋም ብዙ መልካም ተግባራትን ትፈጽም ነበር። ወገኖቼ በጣም እናስተውል ሰው ወንጌል ሲገባው ቅዱሳንን ያከብራል፣ስለ ክርስቶስ ፍቅር ዋጋ ከፍለው በሰማዕትነት ያለፉ የእምነት ጀግኖችን እያሰበ ሕይወታቸውን አብነት አድርጎ ይጓዛል፣ለዚህ ነው ቅዱስ ጳውሎስ « የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሯችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ የእምነታቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሏቸው ያለው። » ዕብ 13፥7
•••
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የሰማዕታትን የተጋድሎ ሕይወትና ወንጌልን በሕይወታቸው እንዴት እንደተረጎሙ ትውልዱ በየጊዜው እያሰበ እንዲኖር ቀናት በቅዱሳን ስም ሰይማ ተጋድሎና ታሪካቸውን ስታስተምር መኖሯ ከትክክል በላይ ትክክል ነው። ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እግዚአብሔር ሁሌም በክብር ይጠብቅሽ። ዛሬ አንዳንድ ሰዎች ወንጌል ገብቶናል ፣ እውነት በርቶልናል እያሉ ቅዱሳንን ሲያቃልሉና ሰማዕታትን ሲያብጠለጥሉ ይውላሉ ፤ ነገርግን ስለ ክርስትና አንዲትም መከራ በሕይወታቸው አልተቀበሉም። በግል በሥጋ ድካማቸው የሚመጣባቸውን መከራ ስለ እምነታቸው እንደተቀበሉት አድርገው ይጠመዝዙታል ይሄ በጣም ስህተት ነው። እውነት ወንጌል የበራላችሁ ከሆነ እስቲ እስላም መስኪድ ሄዳችሁ ስበኩ ፣ እስቲ ጠንቋይ ቤት ያሉትን የማምለኪያ መሰዊያዎች ሄዳችሁ አፍርሱ ፣ ፌስቡክ ላይ ተጥደው እየዋሉ ቅዱሳንና ሰማዕታትን የሚነቅፉ ፣ የቤተክርስቲያንን ክብር ለማዋረድ የሚወራጩ ሰዎች መንፈሰ እግዚአብሔር የተለያቸው የአጋንንት መንፈስ በልባቸው ሰልጥኖ ምላሳቸውን የተከራያቸው የጥፋት ልጆች ናቸው እግዚአብሔር ልባቸውን ይፈውስ።
•••
ወገኖቼ የክርስቶስ ፍቅር ሲገባን እንደነ ቅዱስ ጊዮርጊስ እሳትና ስለቱን ሳንፈራ ስለ ወንጌል እንመሰክራለን ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ የአማልክት አምላክ ፣ የጌቶች ጌታ ፣ የነገሥታት ንጉሥ መሆኑን ሳንፈራና ሳናፍር እንመሰክራለን። የሰማዕታት ደም የእምነት ዘር ነው ጥቂት ፈሶ ብዙ ምርኮን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ያስገባል።
•••
የሰማዕቱ በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን
•••
" ...
ጻድቅን በጻድቅ ስም የሚቀበል የፃድቅን ዋጋ ይወስዳል ማንም ከነዚህ ታናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ውኃ ብቻ በደቀ መዛሙርቱ ስም የሚያጠጣ እውነት እላችኃለሁ ዋጋው አይጠፋበትም ... " ( ማቴ.10፥41 )
•••
404 viewsየእኔ ሀብት, 16:18