2022-08-27 12:23:16
#ዜና ቤተክርስቲያን
የማኅደረ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን በስብከተ ወንጌል ክፍሉ አዘጋጅነት 1ዓመት ከ5 ወራት ያስተማራቸውን የአካባቢው ወጣቶችና ማኅበራት #ሊያስመርቅ ነው!!
+++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++
(ነሐሴ 20 ቀን 2014 ዓ.ም
አዲስ አበባ-ኢትዮጵያ)
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የማኅደረ ስብሐት ልደታ ለማርያም እና ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ስብከተ ወንጌል ክፍል አዘጋጅነት ለተከታታይ1 ዓመት ከ5 ወራት ያስተማራቸውን 200 የአካባቢው ወጣቶችና
ማኅበራት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት ከ1 ወር በኋላ ሊያስመርቅ መሆኑ ተገልጿል።
ዓመታዊና ወርኃዊ እንዲሁም ሳምንታዊ ጉባኤያትን ከማከናወን ባለፈ የካህናት ንስሐ ልጆች በአንድነት ስብስቦ ትምህርተ ወንጌል በመስጠት፣
ሰ/ት/ቤቱን በማጠናከር ላይ የሚገኘው የደብሩ ስብከተ ወንጌል ክፍል የአካባቢውን ወጣቶችና ማኅበራት ተከታታይ ትምህርት በማስተማር ብዙዎችን ያስደነቀ ተግባር ላይ እንዳለ ብዙዎች ይመሰክራሉ።
በአሁኑ ስዓት የአካባቢውን ወጣቶችና ልዩ ልዩ ማኅበራትን ታሳቢ ተደርጎ ለ1 ዓመት ከ5 ወራት ሲሰጥ የነበረው ተከታታይ ትምህርት መጠናቀቁን ተከትሎ ተመራቂ ተማሪዎቹ የመመረቂያ ጽሁፎቻቸውን ባለሙያዎችና በርካታ ታዳምያን በተገኙበት ማቅረብ ጀምረዋል።
ከበዓለ ጥምቀት መከበር በኋላ በደብሩ በተዘጋጀው የምሥጋና መርሐግብር ላይ ከአካባቢው ወጣቶችና ማኅበራት ጋር በተደረገው ውይይት አጭር ሥልጠና ለመስጠት በማሰብ ከመጋቢት 20-25 ብፁዕ አቡነ ኤርምያስን ጨምሮ ሌሎችም መምህራን የተሳተፉበት የ5 ተከታታይ ቀናት ሥልጠና ተሰጥቷል።
820 ታዳምያን የተሳተፉበት ይህ የአጭር ጊዜ ሥልጠና በፈጠረው መንፈሳዊ መነቃቃት የተነሣ ለ1 ዓመት ከ5 ወራት ኢትዮጵያ የዓለም ብርሃን የሚለውን ስሁት አስተምሮ ጨምሮ 13 የትምህርት ዓይነቶችን በዲ/ቆን ያረጋል አበጋዝ (ዶ/ር)፣ በመ/ር ግርማ ባቱ፣በመ/ር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል፣በመ/ር አብነት አሥራት፣ በመ/ር አባ ጌድዮን (ዶ/ር) እና በመ/ር መታሰቢያ ደምሴ በጥቅሉ በ6 መምህራን ሲሰጥ መቆየቱን ከአስተባባሪዎቹ ለመረዳት ችለናል።
የነገረ ሃይማኖት መግቢያን ጨምሮ አንጻራዊ ትምህርተ መለኮት፣ዕቅበተ እምነት፣ ወጣትነትና መንፈሳዊ ሕይወት፣ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር፣የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓተ አምልኮ እና ኢትዮጵያ የዓለም ብርሃን የሚለው ስሁት አስተምሮን የሚዳስሰው ትምህርት ከተሰጡ የትምህርት ዓይነቶች ተጠቃሾች መሆናቸውም ተገልጿል።
በደብሩ ስብከተ ወንጌል ክፍል ከሚሰጡ ሌሎች መርሐ ግብሮች ባልተናነሰ መልኩ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት በርካታ ተማሪዎችን በመመዝገብ የተጀመረው ትምህርት ከ17 ወራት ቆይታ በኋላ አጠቃላይ የመማር ማስተማር ሂደቱ ተጠናቆ ለምርቃት በመዘጋጀት ላይ የሚገኙት ተማሪዎች በተደራጁበት ቡድን ጥናታዊ ፅሁፋቸውን በደብሩ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ማቅረብ መጀመራቸውን በቦታው ተገኝተን ተመልክተናል።
በጥናት አቅራቢዎቹ እና አማካሪዎቻቸው አማካኝነት ከተመረጡት አንገብጋቢ እና ወቅታዊ የቤተክርስቲያን ርእሰ ጉዳዮች ውስጥ 17 ጥናታዊ ፅሁፎች የተሠሩ ሲሆን 4ቱ ጥናታዊ ፅሁፎች በዛሬው ዕለት ቀርበው በጥናት ባለሙያዎችና በታዳምያኑ ተደምጠዋል፣ በጥናት ዝግጅቱና በአቀራረቡ ዙሪያም የሰላ ሂስ ተሰጥቶባቸዋል።
"አማኞች ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ወደ ሌሎች ቤተእምነቶች የሚሄዱበት ምክንያቶችና መፍትሔዎቻቸው ፣የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ለኢትዮጵያ ያበረከተችው አስተዋጽኦ፣ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓተ ጋብቻ በአማኞች ዘንድ የማይተገበርበት ምክንያቶችና መፍትሔዎቻቸው እንዲሁም ተግባራዊ ክርስትና እንዴትና በምን ይገለጣል?" በዕለቱ የቀረቡ 4 የመመረቂያ ጥናታዊ ፅሁፎች ናቸው።
ቡድናቸውን ወክለው ወ/ት ተስፋነሽ ስሜ ፣የሽወርቅ ፈንታብል ሊያ አምባቸውና ፀጋው ደረጄ በተባሉ 4 ጥናት አቅራቢዎች በቀረቡት ጥናታዊ ፅሁፎቹ ለተነሡት ልዩ ልዩ ርእሰ ጉዳዮች አነሳሽ ናቸው የተባሉ ምክንያቶች፣ ጉዳቱ በቤተክርስቲያኒቱና አማንያኑ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ላይ ያመጣው ውጤትና የመፍትሔ ሐሳቦች ተዳሰዋል።
የደብሩ ስብከተ ወንጌል ኃላፊ ሊቀጉባኤ አምባዬ አባተ በመርሐ ግብሩ ባደረጉት ንግግር ጥናት አቅራቢዎቹን አበረታተው ለ1 ዓመት ከ5 ወራት ሲሰጥ የቆየውተከታታይ ትምህርት በየአደባባይ በዓላቱ እየተገኙ ምንጣፍ ከማንጠፍ፣ የበዓሉን ድባብ የሚያጎሉ ክንውኖችን ከማከናወን ባሻገር ሕይወታዊ ለውጥ የማይታይባቸውን ወጣቶች ለማነፅና በዙሪያችን ያለው የመንጋ ንጥቂለመመከት ነው ሲሉ የተጀመረበትን ምክንያት አስረድተዋል።
ስብከተ ወንጌል ክፍሉ በዓመታዊ ዕቅዱ ከያዛቸው ቋሚ የአገልግሎት ክንውኖች በተጨማሪ በልዩ ትኩረትና እንቅስቃሴ ለአካባቢው ወጣቶችና ማኅበራት እየተሰጠ የቆየውን ተከታታይ ትምህርት ከመፍቀድ ጀምሮ በልዩ ልዩ መንገዶች ሲደግፍ ለነበረው የደብሩ ሰ/ጉ/ጽ/ቤት፣በሙያቸው ያገለገሉ መምህራንና ሌሎችም በጎ አድራጊ ኦርቶዶክሳዊ ምዕመናን ምሥጋናቸውን አቅርበዋል።
ስብከተ ወንጌል ኃላፊው አክለውም በዚህ መልኩ ተምረው የጨረሱትን ደቀ መዛሙርት በደብሩ መንፈሳዊ መዋቅር ውስጥ በማቀፍ በበጎ ፈቃደኝነት የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱን እንዲደግፉ፣ ባሉበት አካባቢና በሚሰሩበት የሥራ ቦታ ስለቤተክርስቲያንና ስለቃሉ ምስክሮችና አቃብያን እንዲሆኑ የተቻለው ሁሉ እንደሚደረግ ገልጸው የሂደቱን ቀጣይነትም አረጋግጠዋል።
መርሐ ግብሩን አስመልክቶ ካነጋገርናቸው ተሳታፊዎች መካከል በማኅደረ ስብሐት ልደታ ለማርያምና ደብረ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ስብከተ ወንጌል ክፍል እየተሠራ ያለው ሰው ተኮር እንቅስቃሴ በሌሎች ገዳማትና አድባራትም በትኩረት ሊሠራ እንደሚገባ ሐሳባቸውን አካፍለውናል።
ደብሩ በዕለቱ ከቀረቡት 4 የመመረቂያ ጥናታዊ ፅሁፎች በተጨማሪ ቀሪዎቹ 14 ጥናታዊ ፅሁፎች በሂደት ቀርበው ከተጠናቀቁ በኋላ #መስከረም 29 ቀን 2015 ዓ.ም ለማስመረቅ ማቀዱን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
በመርሐ ግብሩም የቅድስት ሥላሴ ዩንቨርስቲ የመሠረተ ዕምነት ፋክሊቲ ዲን መ/ር አብነት አሥራትን ጨምሮ ተጋባዥ እንግዶች፣ የደብሩ ልዩ ልዩ የሥራ ኃላፊዎችና አገልጋዮች እንዲሁም በርካታ የጥናቱ ታዳምያናን ተገኝተዋል።
በመ/ር ሽፈራው እንደሻው
ምንጭ :- አዲስ አበባ ሀገረስብከት
365 views09:23