Get Mystery Box with random crypto!

#ሼር_ፖስት ይድረስ ለአቶ አዲሱ አረጋ ''''''''''''''''''''''''''''''''''''' | Tadele Tibebu - ታደለ ጥበቡ

#ሼር_ፖስት ይድረስ ለአቶ አዲሱ አረጋ
"""""""""""""""""""""""""""""""""""""""""""""
ሠላም ጤና ይስጥልኝ አቶ አዲሱ አረጋ? ሰሞኑን ሩዋንዳን እንደጎበኘህ፣ በሩዋንዳ የተፈፀመው እልቂት እንዳሳዘነህ፤ በኢትዮጵያ ይህ እንዳይሆን ማስፈራሪያ ጭምር የደረትከውን ጽሁፍ አነበብኩት። ምን ሩዋንዳ አስኬደህ ተወልደህ ባደግህበት ኦሮምያ በሚባለው ክልል የዐማሮች አፅምና የራስ ቅላቸው እንቁፍቱ ገደል፣ ሞሶ ጊዎርጊስ ገደል፣ ጥርሶ ገደል እና ኩርባ ጀርቲ ገደል ውስጥ አለልህ አይደል። ሰብአዊነት ቢሰማ ኖሮ እነዚህን ገደሎች ገብኝተህ፣ ፎቶ ተነስተህ "እንዳይደገም" ብለህ ብትጽፍ ኖሮ ትደነቅ ነበር።

በእነዚህ ገደሎች ኦነግና ኦሕዴድ ተባብረው ዐማሮችን እጃቸው በገመድ እያሰሩ ዐይናቸው በሻሽ እየሸፈኑ ገድለው ጥለዋቸዋል። በአርባ ጉጉ፣ በጉና ወረዳ ሞሶ ጊዎርጊስ ገደል ከ500 ያላነሱ ዐማሮች በሕይዎት እያሉ ወደ ገደሉ ተጥለዋል። በ1985 ዓ.ም. በምዕራብ ሐረርጌ በሀብሩ ወረዳ ገለምሶ በሚገኘው "ጥርሶ ገደል" ብቻ በተደረገው የአስክሬን ለቀማ 16 ኩንታል የሰው ጭንቅላት ተለቅሟል። የተሰበሰበው ዐጽምም በገለምሶ መድኃኒዓለም ቤተ ክርስቲያን ተቀብሯል። ከሩዋንዳው ጋር ልዩነቱ የሩዋዳዎች አፅም ሙዚየም ውስጥ በመስታወት ተቀምጦ መጎብኝቱ የዐማሮች መሬት ውስጥ መቀበሩ ብቻ ነው።

አቶ አዲሱ አረጋ ሩዋንዳ ድረስ መድክም አይጠበቅብህም ነበር። እናተ በምታስተዳድሩት ክልል ከ1982 እስከ 2015 ዓ.ም. ባለው ግዜ ውስጥ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ዐማሮች አልቀዋል። ምሳሌ ለመጥቀስ ያህል ታህሣሥ 29 ቅዳሜ ቀን 1982 ዓ.ም. በአሶሳ ከተማ ከ360 በላይ ዐማራዎች እነሌንጮ ለታ በሚመሩት ኦነግ ተገድለዋል። በ1983 ዓ.ም. ሐምሌ 3 ቀን በጋራ ሙለታ አውራጃ የሚኖሩ ከ95 በላይ የሆኑ ዐማሮች በኦነግ ታጣቂዎች ተገድለዋል። ዶክተር አክሎግ ቢራራ በሽግግሩ ወቅት የተፈጸመውን የግድያ ናሙና እንዲህ መዝግቦታል፣

"በ1983 ዓ.ም. በአርሲ (ዲቡና ጂጋን) 150 ሰላማዊ የዐማራ ተዎላጆች ናችሁ ተብለው ተገድለዋል። በዚሁ አመት በአርባ ጉጉ/ሐረር (ኦነግ ነን) የተባሉ ታጣቂዎች የህወሓት የበላይ አመራር እያወቀ 1000 የዐማራ ተወላጆች ገድለዋል። ብዙ ንብረት አውድመዋል፤ አቃጥለዋል። በ1984 ዓ.ም፤ በዲኖ/ሃረር 140 የ0ማራ ተወላጆች ናችሁ ተብለው ተገድለዋል። በ1998 ዓ.ም.፤ በጅማ/ኦሮምያ ክልል 50 ክርስትያኖች፤ በሃይማኖታቸው ምክንያት ብቻ ተገድለዋል።"(ድርጂታዊ ምዝበራ፣ 115-116)

በዚህ ጉዳይ ፕሬዝዳታችሁ የነበረው አባ ዱላ ገመዳ፣ በ1996 ዓ.ም. "የኦሮሞ ሕዝብ ትግል ከዬት ወዴት" ብሎ በጻፈው መጽሐፍ ምስክርነቱን ሰጥቷል። እንዲህ ይላል፤

"ኦነግ ደርግ እንደወደቀ ቀዳሚ ስራ ያደረገው ህዝቦችን በጥላቻ ሰቅዞ መጨፍጨፍ ነበር። ኦነግ በሐረር አካባቢ የነበሩትን አማራ አርሶ አደሮችና ሌሎች ሕዝቦችን ከአከባቢው ለማባረር ባደረገው ዘረኛ እንቅስቃሴ 'የስራ ውጤት' በማስመዝገቡ ወደ አርባ ጉጉ 'አርሲ' መዝለቅ ችሎ ነበር። ኦነግ በአካባቢው ይኖሩ የነበሩትን አርሶ አደሮች በደፈናው ነ*ፍ*ጠ*ኛ በማለት ሰፊ የዘር ማጥፋት እርምጃ ወሰደ።...በአርባ ጉጉ ኦነግ ባደረገው ህዝቦችን የማጋጨት ተግባራዊ አያሌ ... አማሮች አልቀዋል።"
(የኦሮሞ ሕዝብ ትግል፣ 141)

ህዳር 21 ቀን 1993 ዓ.ም. በጊዳ ኪራሞ ወረዳ በተለይም በድብክ ማርያም፣ በሰንቦ፣ በሃሮ፣ በዋስቲ፣ በጅረኛና በመርጋ ቀበሌ የኦሮሚያ ልዩ ኃይልና ፈጥኖ ደራሽ ፖሊስ በጋራ ሆነው በፈፀሙት ጥቃት 1100 የሚሆኑ የብሉይ ዘመን ሕይወትን የሚገፉ ሚስኪን ዐማሮች ሕፃናት፣ አዛውንቶችና ሴቶች አልቀዋል። በምዕራብ ሐረርጌ ብቻ (በገለምሶ፣ አንጫር፣ ዳሮ ለቡ፣ ወፊ፣ ዳንሴ ወዘተ) በመሳሰሉ ቦታዎች ከ10,000-15,000 ዐማሮች አልቀዋል። አሰቦት ገዳም በ1983 ዓ.ም ክረምት ላይ 16 መነኮሳትና አርድእት "ዐማራ ናችሁ" ተብለው እጅና እግራቸው ታስሮ ወደ ገደል ተጥለዋል። በ1999 ዓ.ም የጥቅምት አቦን ለማክበር በበሻሻ በተሰባሰቡ ዐማሮች ዘግናኝ ጨፍጨፋ ተፈጽሟል።

የሩቁን ትተን ባንተ የሥልጣን ዘመን በምዕራብ ወለጋ ዞን ጊምቢ ወረዳ፣ ቶሌ ቀበሌ ሰኔ 11 ቀን 2014 ዓ.ም. በአንድ ቀን ብቻ ከ300 በላይ ዐማሮች ተጨፍጭፈዋል። በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን አሙሩ ወረዳ በምትገኘውን አጋምሳ በተባለች ከተማ ነሀሴ 23 ቀን 2014 ዓ.ም. ከ50 በላይ ዐማሮች ተገድለዋል። በእናተ ቤት ይህ የዘር ማጥፋት ወንጀል አይደለም? ሥልጣን ከያዘችሁ ወዲህ በዚህ አምስት ዓመት በኦሮምያ ክልል ያለቀው ዐማራ የዘር ማጥፋት ወንጀል አይደለም ይሆን?

አቶ አዲሱ አረጋ እንደነገርከን ሁቹዎች ቱትሲዎችን ላይ የጥላቻ ትርክት ከተሰበከ በኋላ ነው ጥፋት የወረደባቸው። በጣም ትክክል ነህ። ዐማሮችም በአሩሲ፣ በአርባጉጉ፣ በበደኖ፣ በወለጋ፣ በአሰበ ተፈሪ፣ በጉራፈርዳ፣...የተገደሉት "መጤዎች"፣ "ነ*ፍ*ጠ*ኞ" እየተባሉ ነው። ሥልጣን በያዛችሁበት በ2011 እና በ2013 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል በቀጠለው ግድያ (The killing continues) ዐማሮች እንደ እብድ ውሻ ተቀጥቅጠው የተገደሉት "ነ*ፍ*ጠ*ኛ" በሚል ስም ነው። የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ያወጣውን ዝርዝር ሪፖርት ማዬት ብቻ በቂ ነው። ኢሰመኮ ታህሳስ 23 ቀን 2013 ዓ.ም. ይፋ ባደረገው የምርመራ ውጤቱ መሠረት፣ ሜጫና ሚስማር የተመታበት አጣና የያዙ ገዳዮች ጥቃቱን የፈጸሙት "ነ*ፍ*ጠ*ኛ ውጣ፣ የሚኒሊክ ሰፋሪ ካገራችን ውጣ፣ ዐማራ ውጣ፣ ይህ የኦሮሞ ነው አትንካ፣ እሷ/እሱ ዐማራ ወይም ክርስቲያን ሰለሆኑ ንብረቱን አጥፉ" እያሉ እንደነበር በጥናቱ አረጋግጧል። አቶ አዲሱ አረጋ ይህ ከሩዋንዳው በምን ይለያል? እንዲህ ያለውን ከባድ ወንጀል ተሸክመህ ስለሩዋንዳ የዘር ጭፍጨፋ መደስኮር ስላቅ ነው።

የሩዋንዳው ምክትል ፕሬዚዳንት ከቅድመ ዘር ማጥፋቱ በፊት ቱትሲዎችን "በ*ረ*ሮ*ዎች ሀገር የወረሩ ናቸው። እነዚህን ናይባሮንጎ ወንዝ ውስጥ እናስገባቸው" በማለት ተናግሮ ነበር። የክልላችሁ ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ልክ እንደ ሩዋንዳው መሪ መስከረም 21 ቀን 2012 ዓ.ም. በአዲስአበባ ውስጥ በተከበረው የኢሬቻ በዓል ላይ "ነ*ፍ*ጠ*ኞ*ች በሰበሩን ቦታ ላይ ሰብረናቸው በዓላችንን እያከበርን ነው" የሚል አነሣሽ ሞተር በመሆን የሞት ጥሪ ከአስተላለፈ በኋላ ጥቅምት 16 እና 17 ቀን 2012 ዓ.ም. በልዩ ልዩ የኦሮሚያ ዞኖች ዐማራዎች በማንነታቸውና በሃይማኖታቸው የዘር ማጥፋት እና የዘር ማፅዳት ወንጀል ተፈጽሞባቸዋል። አቶ አዲሱ እንዲህ ያለውን አፍንጫህ ስር ያለውን እውነታ ሸሽተት ሩቅ ሀገር ሄደህ ምሳሌ ለመጥቀስ መድከም አልነበረብህም።

የሩዋንዳውን የዘር ፍጀት አነሣስቶ እንዳስፈፀመው
አርቲኤልኤም (RTLM) ሁሉ፣ በዐማራ ሕዝብ ላይ የጅምላ ጭፍጨፋ ቅስቀሳ እያደረገ ያለው የእናተው ኦሮሚያ ሚዲያ ኔትዎርክ (OMN) ነው። የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳ ግድያ ተከትሎ ከጠዋቱ 12፡00 ሰዓት ጀምሮ የተለያዩ ግለሰቦችን በቀጥታ ስርጭት በማስገባት ሲያስተላልፍ የነበረው፣ “ሃጫሉን የገደለው ነ*ፍ*ጠ*ኛ ነው … ከሃጫሉ ሞት የሚጠቀሙ ነ*ፍ*ጠ*ኞ*ች ናቸው፣ ነ*ፍ*ጠ*ኛ ወይም ዐማራ ከዚህ በኋላ በኦሮሚያ ምድር ላይ እንዳይኖር በየቀኑ ለማስወጣት ዝግጅት ላይ ነው፣ ነ*ፍ*ጠ*ኛ ከኦሮሚያ መወገድ አለበት" የሚል የሞት ጥሪ ነበር።