ከባድ የዘረፋ እና የውንብድና ወንጀል ሲፈፅሙ የነበሩ 14 የሽብር ቡድን አባላት በቁጥጥር ሥር ዋሉ
በአዲስ አበባ እና አካባቢው ተደራጅተው ከባድ ዘረፋ እና ውንብድና በመፈፀም የሕዝብን ሰላም ሲያውኩ የነበሩ 14 የሽብር ቡድን አባላትን ባደረገው ከፍተኛ ኦፕሬሽን በቁጥጥር ሥር ማዋሉን የፀጥታ እና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል ገለጸ።
የከተማው ነዋሪ በስጋት እንዲኖር ከሽብር ቡድኑ ተልዕኮ ተቀብለው የሚንቀሳቀሱ ተላላኪዎችን የመመንጠሩ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ግብረ-ኃይሉ አስታውቋል።
የውስጥ እና የውጭ ጠላቶቻችን ተደራጅተው ከከፈቱብን ዘርፈ-ብዙ ጦርነት አንዱ በከተማ የተሸሽጉ ተላላኪዎችን በመጠቀም በለስ ከቀናቸው በገሃድ፣ ካልሆነላቸውም በድብቅ የነዋሪውን ሰላም በማወክ ኅብረተሰቡ የደህንነት ዋስትና እንዳይሰማው በማድረግ በመንግሥት ላይ ያለውን ዕምነት ማሳጣት ዋነኛ ተልዕኳቸውን ነው።
ምንም እንኳን በተለያዩ ጊዚያት እኩይ ተግባራቸውን ለማሳካት ቢፍጨረጨሩም በኅብረተሰቡ መረጃ ሰጭነትና በፀጥታ ኃይሉ ብርቱ ጥረት በቁጥጥር ሥር እየዋሉ ይገኛል።