2022-07-28 10:40:56
የአላህ ፍትህ እና ፍርድ ...
ነብዩላህ ሙሳ (ዐ.ሰ) በአንድ ወቅት አላህን "ጌታዬ እስቲ ያንተን ፍትህ እና ፍርድ አሳየኝ?" ብለው ጠየቁት።
አላህም፦ "አንተ እኮ ትዕግሥት የለህም እንዴት አድርጌ ላሳይህ" አላቸው።
ሙሳም ..."ባንተ እገዛ ትዕግስት አደርጋለሁ" አሉት።
አላህም... "እንዲህ የሚባል ቦታ ላይ ያለው የውሀ ምንጭ አጠገብ ሂድና ተደብቀህ ዝም ብለህ የሚሆነውን ተከታተል" አላቸው።
ሙሳም ምንጯ አጠገብ በመሄድ እንዲት ዛፍ ላይ ወጥተው የሚሆነውን ለመከታተል ተዘጋጁ።
ከዚያም አንድ ፈረሰኛ ምንጯ ጋ መጣና ፈረሱን አቁሞ ውሀ ከጠጣ በኋላ የያዘው ከረጢት አጠገቡ አስቀምጦ ትንሽ ጋደም አለ።
ከትንሽ እረፍት በኋላ ፈረሰኛው ያስቀመጠውን ከረጢት ረስቶ ጉዞውን ጀመረ። ከደቂቃዎች በኋላ አንድ ልጅ መጥቶ ከምንጩ ውሃ ጠጥቶ ሊሄድ ሲል ያ ፈረሰኛ ረስቶት የሄደውን ከረጢት ያገኝና ከፍቶ ሲያየው 1000 ዲናር አገኘ። ደስ ብሎት ይዞት ሄደ። ይህ ሁሉ ሲሆን ሙሳ (ዐሰ) በደንብ እየተከታተሉ ነው።
ልጁ እንደሄደ አንድ ማየት የተሳነው ሽማግሌ መጣ። ከምንጩ ጠጥቶ ውዱዕ አደርጎ እዚያው ሰግዶ ጋደም አለ። ይህ ሽማግሌ ጋደም እንዳለ ፈረሰኛው ረስቶት የሄደውን ዲናሩን አስታውሶ ሲጋልብ መጣ። ፈረሰኛውም ሽማግሌውን ቀስቅሶ ..."አሁን እዚህ ጋ ውሀ ጠጥቼ 1000 ዲናር የያዘ ከረጢት ረስቼ ሄጃለሁ። ካንተ ሌላ ማንም በዚህ ፍጥነት እዚህ መጥቶ ሊሄድ አይችልምና ንብረቴን ስጠኝ አለው።
ሽማግሌውም ..."ልጄ እኔ እንደምታየኝ ዓይነ ሥውር ነኝ እንዴት አድርጌ ያንተን ገንዘብ እወስዳለሁ?" አለው። ፈረሰኛውም ተናዶ እየዋሸው እንደሆነ በማሰብ ጎራዴውን በማውጣት "ንብረቴን መልስ አይ ካልክ በዚህ ጎራዴ ሆድህን እተረትረዋለሁ" ሲለው... ሽማግሌው ደንግጦ ማልቀስ ጀመረ። ሙሳም (ዐ.ሰ) ይህን ሁሉ በጭንቀት እየተከታተሉ ትዕግስታቸው ተሟጥጦ ጫፍ ደርሶ የአላህን ትዕዛዝ በማስታወስ ባሉበት ፀኑ።
ፈረሰኛውም በያዘው ጎራዴ የሽማግሌውን አንገት ቀንጥሶ ከዚያም ልብሱን ሲፈትሽ ምንም ሊያገኝ ባለመቻሉ ትቶት ሄደ።
ከዚያም አለህ ለሙሳ " አንተ ሙሳ ሆይ! ይህ የኔ ፍትህ እና ፍርድ ነው፡፡" አላቸው።
ሙሳም.... "ጌታዬ ትዕግስቴ ተሟጥጦ አልቋል አንተ ጥበበኛ ነህ እስቲ አስረዳኝ" አሉ።
አላህም.... "እኔ ውስጥ አዋቂ ነኝ አንተ የማታውቀውን አውቃለሁ። የፈረሰኛውን ንብረት የወሰደው ልጅ አባት ፈረሰኛው ዘንድ ተቀጥሮ ይሠራ ነበር። ፈረሰኛውም በጉልበቱ ተመክቶ የላቡን ሳይከፍለው ቀርቶ ነበር። ስለዚህ ልጁ ዛሬ የወሰደው የአባቱን ሀቅ ነው።"
"ዓይነ ሥውሩ ሽማግሌ ደግሞ አይኑ ከመጥፋቱ በፊት የዚያን ፈረሰኛ አባት ገድሎት ስለነበር። ፈረሰኛው የአባቱን ገዳይ እንዲገድል አድርገናል።"
"ሙሳ ሆይ! ለሁሉም ሀቁን አድርሰናል። አንዱ ፍትሐችን ሲሆን አንዱ ደግሞ ፍርዳችን ነው።
★★★★
ቢዘገይም በዚሁ አለም አልያም በመጪው አለም ሁሉም በዳይና ተበዳይ ፍርዱንና ፍትህን ያገኛል።
«አላህንም በደለኞች ከሚሠሩት ግፍ ዘንጊ አድርገህ አታስብ፡፡»
[ኢብራሂም 14:42]
695 views07:40