Get Mystery Box with random crypto!

የሴቶችን ድንግልና የሚወስደው ማን ነው? ይህን ፅሁፍ ለማዘጋጀት ያነሳሳኝ አብዛኛውን ጊዜ አንዳንድ | Reyan Records

የሴቶችን ድንግልና የሚወስደው ማን ነው?
ይህን ፅሁፍ ለማዘጋጀት ያነሳሳኝ አብዛኛውን ጊዜ አንዳንድ ወደ እስልምና እንጣራለን የሚሉ ሰዎች ህግጋቱን ሁሉ ሴቶች ላይ ጫን አድርገው ወንዶችን ብዙም ሲሉ አይሰማም፡፡
ሰሞኑን አላዋቂዎች ብዙ ሲሳለቁ እና እራሳቸውንም መግለጫ ሰጪ አድርገው ሲያዩ ተመልክተናል፡፡ የሴት ልጅ ድንግልና በብዙ መንገድ ይሄዳል፡፡ ለምሳሌ ሴት ልጆችን በገዛ የቅርብ ቤተሰቦቻቸው እና ዘመዶቻቸው በመደፈር ሁሉ ያጡታል፡፡ ሴት ልጆች ሲደፈሩ ያውም ደፋሪያቸው እየታወቀ “በቃ ዝም በይ” አይነት ማስጠንቀቂያዎች ይሰጧታል፡፡ ድንግልና ያለ ግንኙነትም ሊጠፋ የሚችልበት ሁኔታ እንዳለ ዑለማዎችም ሀኪሞችም ይገልፃሉ። ስለዚህ ድንግልና የሌላት ሁሉ ብልግና ፈፅማለች ማለት ዝቅ ሲል አላዋቂነት ከፍ ሲል ብልግና ነው። በሌሎችም መንገዶች ድንግልና ይሄዳል፡፡
አብዛኛዎቹ ሴቶች ልጅ በነበሩበት ሰኣት በጣም አይን አፋር እና ድንጉጥ ናቸው፡፡ ወንድን መቅረብ አይፈልጉም፡፡ ሴቶቹን ወደ መጥፎ ነገር የሚመሩዋቸው መጥፎ ሴት ጓደኞች እና ምላሳም ወንዶች ናቸው፡፡
መቼም ወንድ ከሌለ ሴቶች በራሳቸው ድንግልናቸውን አጠፉት አይባልም፡፡ አንድ ሴት ልጅ ድንግልናዋን ስታጣ እሷን ብቻ ከመውቀስ በምላሱ አታሎ፣ አጭበርብሮ ድንግልናዋን የወሰደባትን ለምን በደንብ አይኮንኑትም?
አስገራሚው ሴት ልጅ ስትሰራ ከነበረችው መጥፎ ነገር ቶብታለች ሲባል “እሷ እኮ…. ነበረች…. መጠንቀቅ ነው …. ምን ይታወቃል” እና የመሳሰለውን ትንኮሳዎች ይተበተባሉ፡፡
ወንድ ልጅ ግን ለምሳሌ አንዴ በድፍረት 21 ወይንም 22 አመት የሚጠጋው ወንድ ለጓደኞቹ “ከ180 እስከ 200 ሴቶች ጋር ግንኙነት ፈፅሚያለሁ” እንዳላቸው ሲናገሩ ሰምቻለሁ (የአላህ መልክተኛ ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም የእኔ ኡመቶች ወንጀል ይማራል ግልፅ የሚያወጣው ሲቀር ብለዋል፡፡ ወንጀልን እንደቁም ነገር እና ጀብዱ የምታወሩ ሰዎች አላህን ፍሩ)፡፡ ለምሳሌ ይህን ሁሉ ሴት የነካካ ወንድ ቶብቷል ቢባል “አቤት እሱ እኮ ሷሊህ ነው፡፡ አቤት አኽላቁ፡፡ አቤት እሱን ያገኘች” ተብሎ ይለፈፋል፡፡
ለምን?
አላህ በተከበረው ቁርኣን ላይ
- ዝሙትን በተመለከት ተከልከሉ ሲል ለወንዱም ለሴቱም ነው፡፡
- ዝሙት ከፈፀሙ ያላገቡ ከሆኑ 100 ጅራፉ ይገረፉ ሲል ወንዱንም ሴቷንም ነው፡፡
- ዝሙትን የፈፀሙት ያገቡ ከሆነ በድንጋይ ተቀጥቅጠው ይገደሉ ሲል ወንድንም ሴትንም ነው፡፡
ታድያ ለምን ይሄን ያህል ሁለቱንም የሚመለከተውን ህግ ሴቶች ላይ ብቻ ጫን ማለት አስፈለገ፡፡ እንጨት ለምሳሌ በራሱ አይቀጣጠልም እሳት ሲቀላቀልበት ቢሆን እንጂ፡፡ ስለዚህ ወንድ እና ሴት በፈፀሙት ወንጀል አንዱን ብቻ ጠንከር አድርጎ መውቀሱ በተለይ ከኢስላም ውጭ ያሉ ሰዎች “ኢስላም ሴትን ይበድላል” እንዲሉ የሚያደርጋቸው ይህ ነው፡፡
ፍትሀዊ የሆነ ሀይማኖት ይዘን ፍትህ የሌለ አስመስለን አናቅርበው፡፡ ያለ እውቀት መናገር ሁሌም ጣጣው ከሚታሰበው በላይ ነው፡፡
የቶበቱ ሰዎችን አስመልክቶ ነብዩ (ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም) “ወደ አላህ የተመለሰ ወንጀል እንደሌለበት ነው፡፡” ብለው ሲያበቁ ወደ አላህ የተመለሱ ሰዎችን እያጣጣሉ መናገር መሀይምነትን በይፋ የሚያሳይ ነው፡፡
አስገራሚው ግልፅ ቢድኣና ሺርክን የሚያሰራጩ ግለሰቦች ላይ የሌላቸውን ጥንካሪ እና ድፍረት ወንጀል ላይ የወደቁት ላይ ሲያደርጉት እንመለከታለን፡፡
ወንጀል በድብቅ የሰራ ሰው አይቡ ይደበቅለታል፡፡ ቢድኣን እና ሺርክን በአደባባይ የሚፈፅም ደግሞ በአደባባይ ሙስሊሞች እንዲጠነቀቁት መልስ ይሰጥበታል ይህ ነው ፍትህ እና ሚዛናዊነት፡፡
ዛሬ የቢድኣ ካዝና ለሆኖ ሰዎች ጥብቅና ቆመው እነሱን አናስነካም፡፡ እነሱን የነካ “አይባቸውን እንዳወጣ ነው” ሲሉ ይቆዩና ተደብቀው ወንጀል የሚሰሩ ሰዎችን “ተከታትለን በካሜራ እናጋልጣለን” ብለው ስሜት አምላኪነታቸውን ያሳዩናል፡፡
እንዲህ አይነት መሀይማን ጉዳታቸው እጅጉን የከፋ ነው፡፡

ፅሁፌን ስጨርስ ሴቶችን እንደነ መርየም ድንግልናችሁን ጠብቁ ስንል፣ ወንዶችንም ልክ እንደነ ኡስማን ኢብን አፋን ሁኑ ከዝሙት ራቁ፡፡ ወንድ እና ሴቶች ሆይ! አላህን ፈርታችሁ ቶሎ ተጋቡ፡፡ በኢስላም ትዳር ትልቅ ቦታ አለው፡፡ ከትዳር ያለ አስገዳጅ ሀጃ በመዘግየታችሁ ምንም የምትጨምሩት ነገር የለም፡፡ የምታጡት ነገር ቢብስ እንጂ፡፡
ስለ ትዳር የበሰሉ ሃያእ ያላቸውን ታላቆችን አማክሩ፡፡

ፀሀፊ ሳዳት ከማል