2023-03-12 01:22:05
( ከሲኦል የተላከ የፍቅር ደብዳቤ )
ሄዋን ሰፈርዋ ስትደርስ ከምሽቱ 3 ሰዓት ሆኖ ነበር፡፡ እጅግ ከምትወዳት ጓደኛዋ ከማኪ ጋር ነበር ያመሹት፡፡ ለሁለት የበሉት እራት በጣም አጥግቧት ስለነበር ቤቷ የቀረበላትን እራት ይቅርብኝ ብላ ለምሽት የምትመርጠውን ሻይ ጠጥታ በቀጥታ ወደ መኝታ ቤቷ ገባች።
እንደ ልማዷ ጸሎት አድርሳ፣ ለእንቅልፍ ራስዋን አመቻቸች። የሄዋን እንቅልፍ ሁል ጊዜ ጣፋጭ ነው። ፀጉሯ ትራስ ከነካ እርሷ የለችም። ወደ ሌላ ዓለም ትሔዳለች! ደግሞ ህልሞች ታልማለች፥ በህልም የምትቀበላቸው መልዕክቶች ደግሞ መሬት ላይ ጠብ አይሉም። ሁሉም ሲፈጸሙ አይታለች። “ዛሬ ህልም አይቼ…” ብላ ከጀመረች ሁሉም ሰው በጉጉት ነው የሚሰማት። በዚህ ሌሊት ያየችው ህልም ግን እጅግ የተለየ ነው።
አንድ ሰው ደብዳቤ ይዞላት ይመጣል በህልሟ። ደብዳቤው የተጻፈው ከታች ከሲኦል ሲሆን የጻፈችላት ደግሞ አብራት ያመሸችው ጓደኛዋ ማኪ ናት። ደብዳቤው አንዲህ ይነበባል።
፡
“ውድ ጓደኛዬ ሂዊዬ! በድንገት ሳላስበው ዛሬ ሌሊት ወደማላውቀው ስፍራ መጣሁ። ሲኦል ነው ብለው ነግረውኛል። የምጽፍልሽ ከዛ ነው። በጣም የሚያስፈራ፣ የሚያስጨንቅ ቦታ ነው። በቅጽበት ከመንገድ ወደዚህ ሲያመጡኝ ለምን ብዬ ጠይቄአለሁ። የሰጡኝም መልስ “ከጠላት አላመለጥሽም፥ የጉብኝትሽን ወራት አላወቅሽም፥ የተከፈለለልሽን አልተረዳሽም!” የሚል ነው። አንቺ ግን ታውቂ ነበር አይደል? ተረድተሽም ነበር አይደል? ግን ለምን አልነገርሽኝም ሂዊ! አንዳንቺ የሚቀርበኝ ጓደኛ ኖሮኝ አያውቀም። ምሥጥረኛዬ አንቺ ነበርሽ! አንድ ቀን እንኳን ሳላገኝሽ ከዋልኩ ቅር ይለኝና ትናፍቂኝ ነበር።
፡
አሁንም በፍቅር ልውቀስሽ ብዬ እንጂ ጠልቼሽ አይደለም። ሂዊዬ! ብዙ ቀን አብረን መዝናኛ ውስጥ ተዝናንተናል። ስለ ብዙ ነገር አውርተናል። መካሪዬ ነበርሽ! ግን ሂዊዬ ልጠይቅሽ። ለምን ስለ ጽድቅ፣ ስለ የዘለዓለም ሕይወት፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን አልነገርሽኝም? ፀጉራችንን ስንሠራ ሁሌም አጠገብ ላጠገብ ሆነን ነበር፤ ለብዙ ሰዓታት እናወራ ነበር። አንቺ ግን ታውቂ ነበር አይደል? የሕይወት መንገድ የሚገኘው እንዴት እንደሆነ? በንስሐ እንደሆነ? እስቲ አሁን እያነባሁ በፍቅር ልጠይቅሽ ሂዊዬ የኔ ቆንጆ ለምን አልነገርሽኝም?
፡
ምሳ አብረን ስንበላኮ ከ 3 እስከ 4 ሰዓታት ይፈጅብን ነበር። ስለሔድሽባቸው ከተሞችና ስለ አጋጠሙሽ ነገሮች ስታወሪልኝ አፌን ከፍቼ ነበር የምሰማሽ። ግን ሂዊዬ የኔ ጓደኛ የኔ ማር… በመስቀል ላይ ስለተሠራው ሥራ፣ ስለ ቅዱሳን ክብር፣ ስለ ንስሐ ጥቅም ለምን አልነገርሽኝም? አያስፈልጋትም ብለሽ ነው? በየጊዜው ከውጪ ስትመጪ ስጦታ ታመጪልኝ ነበር። ዛሬ እንኳን ይዤው የነበረው ቦርሳ አንቺ የሰጠሸኝ ነው። አንገቴ ላይ የነበረውም ሃብል እንዲሁ። ለእኔ ስጦታ መስጠት ደስታሽ ነበር።
፡
ግን ሂዊዬ! አህቴ! መጸሐፍ ቅዱስ ለምን አልሰጠሸኝም? አልዋሽም! ስለ መንፈሳዊ ነገሮች ከሌሎች ጓደኞቻችን ጋር ሆነን ስታወሩ ሰምቻለሁ። ስለ ታዋቂ ሰባኪዎች፣ ስለ ካህናት፣ ስለ ዘማርያን፣ ስለ ዲያቆናት ስለ ተማራችኋቸው ትምህርቶች ስታወሩ ሰምቼ አውቃለሁ። ግን ለምን ለእኔም በምሥጢራተ ቤተክርስቲያን መሳተፍ፣ መቁረብ እንዳለብኝ አልነገራችሁኝም? ለምን ከሞት እንደሚያድን፣ ከሲኦል እንደሚታደግ አልተረካችሁልኝም? እሺ እል እኮ ነበር! ብታስረዱኝ እስማማኮ ነበር! ዛሬ እንደሆነው ሰይጣን ያለ ዕድሜዬ አይቀጥፈኝም ነበር! በደሙ እሸፈን ነበራ! መላእክቱ ይጠብቁኝ ነበራ! አሁንማ አበቃ! ጊዜው አልፏል አሉኝ። ወደዚህ ስፍራ አመጡኝ፡፡ በጣም ያስፈራል ሂዊዬ! ለማሰረዳት እንኳን ያስቸግራል! ማንም ወደዚህ እንዲመጣ አልፈልግም።
፡
ጓደኛዬ ማሬ! ሂዊዬ ሚስጥረኛዬ! አንቺኮ ልብስሽን ሲነኩብሽ አትወጂም ነበር። እኔ ግን ሌዘር ጃኬትሽን ስለብስብሽ፥ ለዛውም ሳላስፈቅድሽ፥ ስካርብሽንም ለብሼ ስወጣ በነዚያ ትላልቅ ዐይኖችሽ አየት ታደርጊኝና፥ ዝም ትይኝ ነበር። ሽቶሽ ሽቶዬ፣ ጥፍር ቀለምሽ ጥፍር ቀለሜ ያንቺ የሆነውን የኔ ነበር። እንቺ'ኮ የልብ ጓደኛዬ፣ አሰተማሪዬ ነበርሽ። ስለ ብዙ ነገር… ያስተማርሽኝ አንቺው ነሽ። ግን ስለ መንፈሳዊ ሕይወት ለምን አልነገርሽኝም? በእርሱ በአምላካችን በክርስቶስ ኃጢያትሽ እንደተሰረየልሽ፣ የዘላለምን ሕይወት እንደሚያሰጥ ለምን አላወራሸልኝም? ብዙ ቀን ሲኒማ ስንሄድ አንድ ቀን እንኳን ቤተክርስትያን እንሂድ ለምን አላልሽኝም? ልቤ አዘነብሽ! ተቀየምኩሽ ጓደኛዬ ሂዊዬ! ምንም እንኳን ባዝንብሽም ሁሌም ጨክኜ አንቺን ማኩረፍ አልችልም ታውቂ የለ! መልካም ሕይወት ይሁንልሽ! አምላክሽ ያሰብሽውን ሁሉ ያሳካልሽ! ሁል ጊዜ እወድሻለሁ!
፡
ሂዊዬ አንዳንድ ቦታ አልነበብ ካለሽ ቀለሙን ያበላሸው የተንጠባጠበው እንባዬ ነው! ደህና ሁኚልኝ! አክባሪ እህትሽ፣ ጓደኛሽ፣ ሚስጥረኛ ባልንጀራሽ ማኪ ነኝ፤ ከታች… ከሲኦል!”
ሄዋን ከእንቅልፏ በታላቅ ድንጋጤ ነቃች። ህልም ነበር! በህልሟ ያነበበችው የማኪ ደብዳቤ ግን በጣም አስደንግጧታል። ፊቷ ላይ ላብ ችፍ ብሏል እየተንቀጠቀጠች ስልኳን አንስታ ወደማኪ ደወለች። ስልኩ ተነሣ፥ ያነሳችው ግን ማኪ አልነበረችም። እነ ማኪ ቤት ለቅሶ ይሰማል...“ጓደኛዬን ማኪን ፈልጌ ነው” አለቻቸው እየተርበተበተች። ስልኩን ያነሡት እናትም በሲቃ… “አዬ! ማኪንማ የመኪና አደጋ ነጠቀኝ! ጉልበተኛ ሰይጣን ነጠቀኝ! ለማን አቤት ይባላል?” አሏት።
የሄዋን ሞባይል ከእጇ ወደቀ ማኪን? የሚኪና አደጋ? በህልሟ ያነበበችው የማኪ ጥያቄ ይጮህባት ጀመር። "ለምን አልነገርሽኝም?… ለምን?… ጓደኛዬ… ሂዊዬ… እህቴ… ባልንጀራዬ... ለምን አልነገርሽኝም?… ለምን?"
+++ ተፈጸመ +++
ኧህ በእውነት ይህ ታሪክ ለእኛ በስሙ ክርስቶሳውያን ተብለን ለምንጠራ ክርስቲያኖች የእውነት አሳዛኝና አስተማሪ ጹሑፍ ነው።
እስቲ ራሳችንን እንፈትሸው አሁን ባለንበት ዘመን ስንቶቻችን ይኾን ለምንወዳቸው ጓደኞቻችን የእግዚአብሔር መንገድ ስለሐይማኖታችን የምንማማር የምንጠያየቅ የጽድቅን ጎዳና የምንፈልግ። ስለዚህ አንተ ሰው በእውነት የምወደው ጓደኛ ካለህ/ካለሽ ክፋት፣ ምቀኝነት፣ ተንኮል፣ አሽሙር፣ ዘረኝነት፣ ዝሙት፣ ፖለቲካ የውጭ ስፖርት እያወራህ ጊዜህን ከምታጠፋ አሁኑኑ መንፈሳዊ ትምህርቶችን በመማማር ይልመድብን።
ጊዜው የከፋ በመሆኑ ስለመንፈሳዊ ነገር ከሚያወራን ፣ ወደ ቤተክርስቲያን እንሂድ ፣ ሰንበት ት/ቤት እንማር ከሚለን ይልቅ ስለዝሙት ስለጅንጀና የሚያወራንን እንወደው ይሆናል።
ተወዳጆች ሆይ! ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለነፍሳችን የሚሆን መንገድ ያሳየን። አንዳችን ለአንዳችን መንገድ ጠቋሚዎች፣ አሳቢዎች እንሁን። ራሳችንን እንፈትሽ። ልዑል እግዚአብሔር ዕድሜ ለንስሐ ይስጠን አሜን !
537 views22:22