2022-08-31 17:30:41
የአውሮፓ ወንዶች የማይገረዙት፤ ኢትዮጵያን ጨምሮ በአፍሪካ የሚገረዙት ለምንድን ነው?
የወንድ ልጅ ግርዛት በአውሮፓ አገራት ውስጥ የተለመደ አይደለም።
በአፍሪካ እና በአሜሪካ እንዲሁም የእስልምና እምነት በሚከተሉ አገራት ውስጥ ደግሞ የወንድ ልጅ ግርዛት ከባሕልና ከእምነት ጋር የተቆራኘ ነው።
ለምሳሌ በጋዛ ሰርጥ ያሉ 99.9 በመቶ ወንዶች ተገርዘዋል። በሞሮኮና በአፍጋኒስታንም እንዲሁ ከ99 በመቶ በላይ ወንዶች የተገረዙ ናቸው።
ዎርልድ ፖፑሌሽን ሪቪው የተሰኘው ገፅ እንደሚጠቁመው በኢትዮጵያ ከ92 በመቶ በላይ ወንዶች የተገረዙ ናቸው። በኤርትራ ደግሞ ቁጥሩ ከ97 በመቶ በላይ ነው።
በተቃራኒው በአውሮፓ እና በደቡብ አሜሪካ አገራት የወንድ ልጅ ግርዛት በመቶኛ ሲሰላ ከዜሮ በታች ነው።
ግርዛት ከወንድ ልጅ ብልት ላይ ሸለፈት አሊያም በእንግሊዝኛ ፍርስኪን የተሰኘው ቆዳ የሚለይበት ዘዴ ነው።
ለመሆኑ ይህ የሆነበት ምክንያት እና የግርዛት ጥቅሙ ምንድነው? ጉዳትስ ይኖረው ይሆን?
ዶክተር በዕደ ለማ በአዳማ አጠቃላይ ሆስፒታል የሽንት ቧንቧ እንዲሁም የወንዶች የመራቢያ አካላት ስፔሻሊስት [ዩሮሎጂስት] ናቸው።
የግርዛት ጥቅሙ ምን ይሆን? ዶክተር በዕደ እንዲመልሱ ያቀረብንላቸው ጥያቄ ነው።
"ምንድነው ጥቅሙ? በተለይ ንፅሕናን በሚገባ መጠበቅ በማይችል ማኅበረሰብ ውስጥ የተገረዙ ወንዶች እስከ ካንሰር ድረስ ከሚያደርስ ‘ኢንፌክሽን’ ለመከላከል ሊጠቅማቸው ይችላል።"
ዋናው የግርዛት ጥቅሙ ይህ ነው ይላሉ ዶክተሩ። በተለይ ከሸለፈት ጋር በተያያዘ ለሚመጡ በሽታዎች ግርዛት አንዱ መከላከያ ነው።
ዶክተር በዕደ ግርዛት በምዕራቡ ዓለም ብዙ ተቀባይነት የሌለው ከሃይማኖት እና ከባሕል ተፅዕኖ ወጣ ያለ በመሆኑ እንደሆነ ያስረዳሉ።
ቫቲካን ከዓለም አገራት በጣም ዝቅተኛው የተገረዙ ወንዶች ያሉባት እንደሆነች መረጃዎች ያሳያሉ።
በሕክምናው ዓለም እንደምሳሌ በምትነሳው ደቡብ አሜሪካዊቷ ኩባ የወንድ ልጅ ግርዛት ከመቶኛ ሲታይ 0.10 ነው።
በፖርቹጋል 0.6%፣ በጃፓን 9%፣ ፈረንሳይ 14%፣ በዩናይትድ ኪንግደም ደግሞ 20 በመቶ ነው።
በዚህ የአገራት ደረጃ ምደባ ላይ ብዙ የተገረዙ ወንዶች ያሉባቸው ሰፊ እስልምና እምነት ተከታይ የሚገኝባቸው አገራት ናቸው።
ከዚያ ባለፈ እንደ ኤርትራ እና ናይጄሪያ እንዲሁም ኢትዮጵያን የመሳሰሉ የአፍሪካ አገራት ከ90 በመቶ በላይ ወንዶች የተገረዙባቸው ናቸው።
አውሮፓውያን አገራት ምንም እንኳ የክርስትና እምነት ቢከተሉም ግርዛት ሃይማኖታዊ ግዴታ ተደርጎ አይወሰድም ይላሉ ዶክተር በዕደ።
"በሃይማኖትም በሳይንስም ድጋፍ ስሌለው ብዙዎቹ አይገረዙም። እንዲያውም አንዳንድ ቦታዎች ግርዛት ክልክል ነው።"
ምንጭ ቢቢሲ
212 views14:30