2022-04-26 22:39:24
ለመሸፋፈን ብንለፋ አልሸፈን ያለን ነውር ዛሬም ራሱን ገልጧል
ኢና ሊላሂ ወኢና ኢለይሂ ራጂዑን! የሞቱትን ለጀነት፣ ለቆሰሉት ፈጣን ፈውስ፣ ንብረታቸውን ላጡ የተሻለ ካሳ ከአላህ እማፀናለሁ
መተባበርና መተዛዘን በሚጠበቅባቸው ግዚያትና ቦታዎች ማጥቃት ቀላል የሆነላቸው ድንገተኛ ክስተት ሆኖ አይደለም
በቀላሉ ሊቆም የሚችልን ችግር እንደሰደድ እሳት ያስፋፉት ከአቅም በላይ ሆኖ አይደለም፣
በመቃብር ስፍራ ላይ ያስጀመሩትን ጥቃት ወደመኖሪያ ቤት፣ የንግድ ማእከላትና መሳጂዶች ያዛመቱት ድንገት ከጃቸው ወጥቶ አይደለም
ትንሽ መስለው ሰፊውን ህዝብ የሚያውኩት ክፋታቸው በቁጥራቸው ብቻ የሚገለፅ ሆኖ አይደለም
ብዙዎቹ ነገሮች ሁሌ ለመስጠት እንደምንሞክረው ቀና መላምት፣ ለህዝቦች አብሮነት እንደምንለፋው አልሳካ ያሉት ለመሸፋፈን የምንጥረው ነውር ራሱን ደግሞ ደጋግሞ እየገለጠ ነው።
ይህንን ነውር የጎንደር ህዝብ ለአንዴና ለመጨረሻ ግዜ ሊጠየፈው ይገባል። ከውስጡ የበቀሉ የነውረኛ ሥብስቦችን ነቅሎ ለመጣል የሚከፈለውን ዋጋ ሁሉ ቢከፍል ለጎንደር ህዝብ የቆየ ሰላማዊነትና ለነገዋ ጎንደር እፎይታ እጅግ የሚገባ አንገብጋቢ ስራ ነው። የአካባቢው ባለስልጣናትና የክልሉ መንግስት አካባቢውን እና ክልሉን እረፍት የለሽ ሁከት ውስጥ እየከተቱ ክልሉን የነውረኞች መሸሸጊያ እንደሆነ የሚሰሩትን ሳያቃልል እና ምንም ምክንያት ሳይደረድር ሊያስቆምና ሊቀጣ ይገባል። አመራሩ የሚወስደው የማያዳግም እርምጃ ለሰላሙ ብቻ ሳይሆን ነውረኞች በአመራሩ ውስጥ ሰርገው አለመግባታቸውን ማስተማመኛ የሚሰጥ ነው።
ነውረኞች የመጨረሻ ግባቸው የህዝባችን ቋንቋ እና ምግባር በነሱ ደረጃ ወርዶ የነሱ ህግ ገዢ እንዲሆን ነው የሚሹት። ትንሽ ቢሆኑም በነውራቸው ብዙውን ሊበክሉ እንደሚችሉ በማመን ወደሜዳቸው ነው ሊጠሩን የሚመኙት፣ እረፍታቸው የሚመነጨው አለመረጋጋት በመፍጠር ስለሆነ ከሰከነ መንፈሳዊነትና ከተረጋጋ አውድ እንድንወጣ ነው የሚለፉት
ለነርሱ የምንደረድረው የይሆናል ምክንያት አልቆብን ግልፁን መናገር ብንጀምርም ያስነሱትን የነውር መንገድ በጎንደርም ሆነ በተቀረው አካባቢ እንዲሰፍን ግን ፈፅሞ አንፈቅድላቸውም። የተቀረውን አካባቢ ሰላም እንዲጠበቅ እየሰራን እነርሱን ነቅሎ ለመጣል ከጎንደር ህዝብና የሀገር ሽማግሌዎች፣ ከአካባቢው አመራሮች፣ ከክልሉና ከፌዴራል መንግስት ጋር በትብብር እንሰራለን። እንደምናሸንፋቸውም ሙሉ እምነት አለን!
ኡስታዝ አቡበክር አህመድ
ሚያዝያ 18/2014
5.7K views19:39