2022-03-18 12:08:59
+++ የማይነጋው ሌሊት +++
...እስቲ ለአንድ አፍታ ወደዚያ የጨለማ ሸንጎ ስለእኛ ተይዞ በአይሁድ መካከል ብቻውን የቆመውን ደቀመዛሙርቱ ትተውት የሸሹትን ጌታ ተከትለን በዓይነ ኅሊናችን እንግባ! ቤተ ክርስቲያችን አንጀት በሚያላውስ ውብ ዜማ :
‹‹ዐገቱኒ ከለባት ብዙኃን ፤
ወአኀዙኒ ማኅበሮሙ ለእኩያን ፤
ዐገቱኒ ከለባት ብዙኃን››
እያለች በስቅለቱ የምታዜምለት ‹‹ብዙ ውሾች ከበቡኝ ፤ የክፉዎችም ጉባኤ ያዘኝ›› ብሎ በዳዊት አንደበት የተናገረውን ክርስቶስ በውሾች አይሁድ ተከብቦ በክፉዎች ሊቃነ ካህናት ተይዞ እናየው ዘንድ በዓይነ ኅሊናችን ወደ ቀያፋ ቤት ሸንጎ ጌታችንን ተከትለን እንግባ፡፡ (መዝ. ፳፪፥፲፮)
ቅዱስ ኤፍሬም እንዲህ ይላል :-
‹‹ሁሉን የፈጠረው ጌታ ዛሬ በቀያፋ ፊት እንደ ክፉ ወንጀለኛ እየተመረመረ ነው፡፡ ከባሪያዎቹ አንዱም በጥፊ መታው፡፡ ጌታ ቆሞ ባሪያው ሊፈርድበት ተቀመጠ ፤ በክፋት የተሞላው ቁጭ ብሎ በንጹሑ ላይ ፈረደበት፡፡
እነዚህን ነገሮች ባሰብኩ ጊዜ ልቤ በፍርሃት ይንቀጠቀጣል! ሰማያትም ይንቀጠቀጣሉ ፤ የምድርም መሠረት ይናወጻል፡፡ መላእክትና ሊቃነ መላእክት በፍርሃት ይጨነቃሉ፡፡ ሚካኤልና ገብርኤል በክንፎቻቸው ፊታቸውን ይሸፍናሉ፡፡ ባሪያ ጌታውን በጥፊ ሲመታ ባዩ ጊዜ ኪሩቤል ከዙፋኑ ሥር ይሸሸጋሉ ፤ ሱራፌልም ክንፎቻቸውን ያማታሉ!››
ጌታችን በአይሁድ ሸንጎ ‹ሞት ይገባዋል!› ተብሎ ያለ ሕግ ከተፈረደበት በኋላ የነበረው ቀሪው የሌሊት ጊዜ የጭንቅ ነበር፡፡ ሊቃነ ካህናቱ ጉባኤውን በሥርዓት አልበተኑትም፡፡ ‹‹በዚያን ጊዜ ተፉበት ፤ ጎሰሙትም ፤ ሎሌዎቹም በጥፊ እየመቱ ወሰዱት ፤ የያዙት ሰዎች ይዘብቱበትና ይደበድቡት ነበር፡፡ ሌላም ብዙ ነገር እየተሳደቡ በእርሱ ላይ ይናገሩ ነበር፡፡ ሌሎችም በጥፊ መትተው ፡- ክርስቶስ ሆይ በጥፊ የመታህ ማን ነው? ትንቢት ተናገርልን አሉት›› (ማቴ. ፳፮፥፷፯‐፷፰ ፣ ማር. ፲፬፥፷፭ ፣ ሉቃ. ፳፪፥፷፫‐፷፭)
ምራቅ መትፋት በአይሁድ ባህል ትልቅ ማዋረድ ነው፡፡ ‹‹አንዲት ሴት ላይ አባትዋ ምራቁን ቢተፋባት እንኳን ለሰባት ቀን ታፍር››ና ከሰው ትለይ ነበር፡፡ (ዘኁ.፲፪፥፲፬) የወንድሙን ቤተሰብ ዋርሳ ሆኖ ማስተዳደር ያልቻለን ሰው ለማዋረድም ሴቲቱ እንድትተፋበት ይደረግ ነበር፡፡ (ዘዳ. ፳፭፥፱) በአይሁድ ዘንድ ብቻ ሳይሆን በእኛም ዘንድ ምራቅ የምንተፋው የሚያስጸይፍ ነገር ስናይ ወይም ክፉ ሽታ ሲሸትተን ነው፡፡ የሰው ፊት ላይ መትፋት ግን የመጨረሻ ንቀትና የጥላቻ መግለጫ ነው፡፡ ትፋትን ለሚቀበለው ሰው ደግሞ ምራቅን በፊቱ ላይ መቀበሉ እጅግ የሚዘገንነው ነገር ነው፡፡ እንኳንስ የሌላን ሰው ምራቅ ቀርቶ የራሳችንንም ምራቅ እንኳን በአፋችን ውስጥ እያለ እንዳልዋጥነው ሁሉ ከአፋችን ከወጣ በኋላ እንጸየፈዋለን፡፡ ሰውነታችንን ቢነካውም በቅጽበት እንታጠባለን እንጂ የራሴ ምራቅ ነው ብለን አንተወውም፡፡
በዚያች ምሽት ግን አንድ ሰው ብቻ ሳይሆን የካህናት አለቆችና የአይሁድ ማኅበር ከነሎሌዎቻቸው በመድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ላይ ተራ በተራ ምራቃቸውን እየተፉ የጥላቻቸውንና የንቀታቸውን ጥግ አሳዩት፡፡
ለመስማት የሚያስጨንቀው በዚህ የጨለማ ሸንጎ ምራቅ ሲተፋበት ያመሸው ጌታ ምራቁን በእጁ ላይ እንትፍ ብሎ የዲዳውን ሰው ምላስ በመዳሰስ አንደበቱን የከፈተለት ጌታ መሆኑ ነው፡፡ (ማር. ፯፥፴፫) እርሱ ዕውር ሆኖ የተወለደን ሰው በቅዱስ ምራቁ ጭቃን ለውሶ በግንባሩ ላይ ዓይን ሠርቶ ወደ ሰሊሆም መጠመቂያ ሔደህ ተጠመቅ ብሎ ዓይኑን አብርቶለት ነበር፡፡ አይሁድ ግን በምራቁ ዓይንን የሚሠጥን ጌታ በዓይኑ ላይ ርኩስ ምራቃቸውን ተፉበት፡፡ (ዮሐ. ፱፥፮)
ጌታችን የዕውሩን ዓይን እንኳን በምራቁ ባበራበት ዕለት በመሬት ላይ አጎንብሶ እንትፍ አለ እንጂ ላድነው ነው ብሎ እንኳን በዕውሩ ፊት ላይ አልተፋበትም፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም እንዲህ ብሏል ፡-
‹‹ለእኛ ፊት ክብርን የሠጠ እንደ አንተ ያለ ማን አለ?
የዕውሩን ዓይን ስታበራ እንኳን አርኣያችንን አክብረህ
ወደ መሬት ተፋህ እንጂ በፊቱ ላይ አልተፋህበትም፡፡
ጌታ ሆይ በእኔ ላይ ግን በፊቴ ላይ እንትፍ በልብኝ ፤
በገዛ ፈቃዴ የዘጋሁትን ዓይኔን ክፈትልኝ››
ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ወተአገሠ ምራቀ ርኩሰ ፤ እንዘ አልቦ ዘአበሰ›› (ምንም የበደለው ሳይኖር ርኩስ ምራቅን ታገሠ) እንዳለው በጌታችን ላይ ያ ሁሉ ምራቅ የተተፋበት አንድም ጥፋት ሳይኖርበት መሆኑ የትዕግሥቱን መጠን ያሳየናል፡፡ ‹‹ጀርባዬን ለገራፊዎች ጉንጬንም ለጠጉር ነጪዎች ሠጠሁ ፤ ፊቴንም ከውርደትና ከትፋት አልመለስሁም›› ተብሎ እንደተነገረለት ጌታችን ያ ሁሉ ምራቅ ሲተፋበት አንድ ጊዜ እንኳን ፊቱን አላሸሸም፡፡ (ኢሳ. ፶፥፮)
በዚያች ምሽት ምራቅ በመትፋትም ብቻ ሳይወሰኑ ጌታችንን ደጋግመው በጥፊ መቱት ፤ ጎሰሙት ቅዱስ ሉቃስ እንደጻፈው ‹‹ሌላም ብዙ ነገር እየተሳደቡ በእርሱ ላይ ይናገሩ ነበር›› እነዚህ ሎሌዎች የሚኖሩት በሊቃነ ካህናቱ ግቢ ቢሆንም በቤተ ክህነት ግቢ ውስጥ መኖራቸው የሥነ ምግባር ብልሹነታቸውን አላረመውም፡፡ የነ ሐናና ቀያፋን ምግባረ ብልሹነት እያዩ እነሱ ከጌቶቻቸው በምንም ሊሻሉ አይችሉምና በማግስቱ ገና ብዙ ግርፋትና ሥቃይ የሚጠብቀውን ‹የሕማም ሰው› ዕረፍት ነስተው ሲደበድቡትና ሲያንገላቱት አደሩ፡፡ ጌታችን ያደረው በቀያፋ ግቢ ምድር ቤት በሚገኘው እስር ቤት ሲሆን እጆቹን ወደ ላይ አሥረው ብዙ ድብደባን አደረሱበት፡፡ ‹‹ዓይኖቹና አፍንጫው የደም ምንጭ ሆኑ››
ወንጌላዊው ‹ሌላ ብዙ ነገር እየተሳደቡ› ብሎ የተወው ‹ከሰደበኝ የደገመኝ› እንዳይሆንበት ነው እንጂ ጌታችንስ በጆሮው ብዙ ስድብን ተቀብሏል፡፡ ‹‹ነፍሴ ስድብንና ኃሳርን ታገሠች ፣ አስተዛዛኝም ተመኘሁ አላገኘሁም የሚያጽናናኝም አጣሁ›› ብሎ በነቢዩ አንደበት እንደተናገረ ጌታችን የማይቆጠር ስድብን ስለ እኛ ተሸክሟል፡፡ (መዝ. ፷፰፥፳)
ለጌታችን መሰደቡ በዚያች ዕለት ብቻ የደረሰበት ነገር አይደለም፡፡ ድርሳነ ማኅየዊ ‹‹ስድቡስ በዕለተ ዓርብ ብቻ አይደለም ፤ ሦስት ዓመት ሙሉ ሰደቡት እንጂ›› ‹‹ጽዕለቱሰ አኮ በዕለተ ዓርብ ባሕቲቱ አላ ጸዐልዎ ሠለስተ ዓመተ›› እንደሚል ጌታችን ምስጋናን ሊሰማበት በሚገባው አምላካዊ ጆሮው ሦስት ዓመት ሙሉ ብዙ ስድብን ስለ እኛ ታግሦ ሰምቷል፡፡ አምላክ እንደመሆኑም በፊቱ የተሳደቡትን ብቻ ሳይሆን በሌላ ቦታ ሆነው የሚሳደቡትንም ስድብ እየሰማ ታግሦአል፡፡
‹‹ሚ መጠነ ዘተወክፈ እግዚእነ ሕማማተ ዘበልሳን እምነ አይሁድ›› ይላል ሌላው ሊቅ ‹‹ጌታችን በአይሁድ አንደበት የሚነገሩ {የንግግር} ሕማማትን ምን ያህል ተቀበለ? የአናጢ ልጅ የሚሉበት ጊዜ አለ ፤ ዕብድ የሚሉበት ጊዜ አለ ፤ ጋኔን ይዞታል የሚሉበት ጊዜ አለ ፤ በደለኛ አሳች የሚሉበትም ጊዜ አለ›› (መዝገበ ሃይማኖት ፩፥፳)
ከዚህ በኋላ ፊቱን አስረው በጥፊ እየመቱ ‹የመታህ ማን ነው ትንቢት ተናገርልን› እያሉ ዘበቱበት፡፡ የነቢያትን አምላክ ‹ነቢይ ከሆንህ ትንቢት ተናገር› አሉት፡፡ ዓይንን የሠራውን ጌታ ዓይኑን ሸፈኑት፡፡ ሁሉን ከሚያውቅ ፈጣሪ ጋር ድብብቆሽ የሚሞክር ሰው ምንኛ ተሞኘ? ነቢዩ ዮናስ መጥቶ ቢነግራቸው ምን አለ? ነገሩን አልን እንጂ ኃጢአት ሰርተን ፈጣሪ የማያየን የሚመስለን ሰዎች ሁላችንም ዓይኑን ካሰሩት ሎሌዎች በምንም አንሻልም፡፡
254 views09:08