Get Mystery Box with random crypto!

የመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች ነን? እንዴት? የእግዚአብሔር ልጆችስ ነን? እንዴት? ክፍል አንድ የመ | ናዝራዊ Tube

የመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች ነን? እንዴት? የእግዚአብሔር ልጆችስ ነን? እንዴት?
ክፍል አንድ

የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነት ጥቅስ በ2ጴጥ. 1፥4 የሚገኘው ነው። ስለ ክፉ ምኞት በዓለም ካለው ጥፋት አምልጣችሁ ከመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች በተስፋ ቃል እንድትሆኑ፥ በእነዚያ ክብርና በጎነት የተከበረና እጅግ ታላቅ የሆነ ተስፋን ሰጠን። 2ጴጥ. 1፥4

መጀመሪያ ያልሆንነውን ነገር እናስተውል።

1. እኛ መለኮት አይደለንም። መለኮት አንድ ብቻ ነው። እኛ አማልክት አይደለንም። እኛ በምድር ላይ ውር ውር የምንል ትንንሽ እግዚአብሔሮች አይደለንም። መዝ. 82፥6 ላይ የሚገኘው፥ እኔ ግን፦ አማልክት ናችሁ፥ ሁላችሁም የልዑል ልጆች ናችሁ፤ የሚለው ቃል ስለ አምላክ ሳይሆን ስለ ሰዎች እንደሚናገር ቀጥሎ ቁጥር 7 ላይ ያለው፥ ነገር ግን እንደ ሰው ትሞታላችሁ፥ ከአለቆችም እንደ አንዱ ትወድቃላችሁ አልሁ። የሚለው ቃል ይመሰክራል። አምላክ አይሞትምና እነዚህ ከሞቱ ቃሉ ስለ መለኮት አለመናገሩ መሆኑን እናውቃለን። ጌታም በዮሐ. 10፥34 ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፦ እኔ፦ አማልክት ናችሁ አልሁ ተብሎ በሕጋችሁ የተጻፈ አይደለምን? ብሎ ሲጠቅስ ያንኑ አሳብ መግለጡ ነው። ቃሉ ኃያላን፥ ክቡራን ማለት ነው። ‘እነዚያ እንኳ እንደዚያ ከተባሉ፥ እኔ ከአብ የመጣሁት ያንን ብል ተገቢ ነው።’ ማለቱ ነው።

2. እኛ በፍጥረታችን የመለኮት ባሕርይ የለንም። ስንፈጠር ሰዎች ነን እንጂ አማልክት ወይም መናፍስት አይደለንም። ሕይወት ያለን፥ የሕይወት እስትንፋስ እፍ የተባለብን፥ ሕያዋን ወይም ከተፈጠርንባት ቅጽበት ጀምሮ ዘላለማውያን የሆንን ሰዎች ነን። ይህ ስለ አዳምም ስለ እኛም፥ ወይም በአዳም በኩል ስለ እኛም ነው።

3. የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነት በምንም መልክ የክርስቶስ እኩዮች ወይም አቻዎች አያደርገንም። ክርስቶስ እግዚአብሔር ነው፤ ወይም ከሥላሴ አካላት አንዱ ነው። እኛ ግን ፍጡራን እና ፍጡራን ብቻ ነን።

4. የኛ ልጅነት ከክርስቶስ ልጅነት በሁሉ ረገድ፥ በመልኩም፥ በዓይነቱም፥ በደረጃውም የተለየ ልጅነት ነው። ግን ልጅነት ነው። እኛ ልጆች የተደረግን ልጆች ነን። ጌታ፥ ‘አባቴና አባታችሁ’ ሲል ይህንን ያሳያል። ‘አባታችን’ አላለም። “‘አባቴና አባታችሁ’ ሲል ያው አባት አንድ መሆኑን መናገሩ ነው፤ አይደል?” ሊባል ይቻላል። ልክ ነው፤ አባት አንድ ነው፤ አባትነቱ ግን የተለያየ ነው። ‘አባታችን ሆይ’ ብለን እንጸልይ የል?’ ሊባል ይቻላል። አዎን፤ ግን፥ ‘ብላችሁ ጸልዩ’ ነው ያለው። እዚያው ያንን ባስተማረበት ክፍል ውስጥ፥ ‘የሰማዩ አባታችሁ’ እያለም አስተምሯል፤ ‘የሰማዩ አባታችን’ አላለም። ለአይሁድ አባታችን እያለ ሳይሆን አባቴ እያለ መናገሩ ምን ማለቱ እንደሆነ፥ በግልጽ ራሱን ከአብ ጋር ማስተካከሉ እንደሆነ ገብቷቸዋል። ሊወግሩት የቃጡት አሳልፈውም የሰጡት ስለዚህ ነው። ይሁን እንጂ ልጆች ሆነናል፤ በመደረግ።

5. እኛ ከፍጥረታችን ወይም በተፈጥሮአችን የአዳም፥ የወደቀው አዳም ልጆች ነን። በእነዚህም ልጆች መካከል እኛ ሁላችን ደግሞ፥ የሥጋችንንና የልቡናችንን ፈቃድ እያደረግን፥ በሥጋችን ምኞት በፊት እንኖር ነበርን እንደ ሌሎቹም ደግሞ ከፍጥረታችን የቁጣ ልጆች ነበርን። ኤፌ. 2፥3። እነዚያ ‘የአብርሃም ልጆች ነን’ እያሉ ለሚኩራሩት የአብርሃም ሳይሆን የዲያብሎስ ልጆች መሆናቸውን በግልጽ ነበር የነገራቸው፤ ዮሐ. 8፥39-44።

ቀጥሎ የሆንነውን እንመልከት። . . .

ይቀጥላል።

ዘላለም መንግሥቱ
@nazrawi_tube