2022-08-26 20:33:23
አገራችን ኢትዮጵያ ሰው ሰራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎችን በተለያዩ ጊዜያት እያሰተናገደች እና ለፈተናዎቿም ተመጣጣኝ ምላሾችን እየሰጠች መሻገሯን ትቀጥላለች!
ክብርት ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ፣ የከተማና መሠረተ-ልማት ሚኒስትር
የአደጋ ጊዜ ምላሽ ኮምፖነንት ማስጀመሪያ እና የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ የፌደራልና የክልል ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በአዳማ ከተማ ነሐሴ 20/2014 ዓ.ም በይፋ ተጀምሯል፡፡
መርሃ-ግብሩን በይፋ ያስጀመሩት የከተማና መሠረተ-ልማት ሚኒስትር ክብርት ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ በመክፈቻ ንግግራቸው መንግስት፣ ከተሞች ለሃገር አቀፍ ልማት ያላቸውን ከፍተኛ አስተዋፅኦ በመገንዘብ፣ በቀጣይ 10 ዓመት የፍኖተ ብልጽግና ዕቅዱ ሀገራችንን የአፍሪካ የብልጽግና ተምሳሌት፣ ከተሞቻችንን ደግሞ የምርታማነትና የብልጽግና ማዕከላት ለማድረግ ራዕይ ይዞ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸው የከተማ ልማት ሥራችን ባለ ብዙ ዘርፍ እንቅስቃሴዎችን ያካተተ እንደመሆኑ መጠን የኢንዱስትሪ፣ የገበያ፣ የማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ መሠረተ ልማትና አገልግሎቶችን ከሌሎች ሴክተሮች ጋር በመተባበር በቅንጅት፣ በትስስርና በተመጋጋቢነት በከተሞቻችን ያሉ ዜጎችን የከፋ ድህነት እና ኑሮ ማሻሻል፣ በሰው ሰራሽና በተፈጥሯዊ ሁኔታ በከተሞቻችን ለተፈጠሩ አደጋዎች ምላሽ መስጠት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡ በዚህ የአደጋ ጊዜ ምላሽ አሰጣጥ ኮምፖነንት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ የተገኘን ሁላችንም ለፕሮጀክቱ ስኬታማነት በተባበረ ክንድ አብረን መቆም ይኖርብናል ሲሉም አሳስበዋል፡፡
በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች በደረሱ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ አደጋዎች የተከሰቱ፡- በጦርነት የወደሙ የከተሞቻችንን ተቋማት መልሶ የመገንባት፣ ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ ወገኖችን በዘላቂነት መልሶ የማቋቋም፣ እንዲሁም ከሳዑዲ አረቢያ በበርካታ እንግልትና ጭቆና ውስጥ ኑሯቸውን ለማሻሻል ሲጥሩ የነበሩ ዜጎቻችንን ወደ እናት አገራቸው በመመለስ፣ መልሶ በማቋቋምና ድጋፍ በማድረግ ልንረባረብ ይገባልም ብለዋል፡፡
ከ2009 ዓ.ም ጀምሮ ላለፉት 5 ዓመታት በሃገር አቀፍ ደረጃ በ11 ከተሞች ሲተገበር የቆየው የከተሞች ልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮጀክት በከተሞች የሚስተዋለውን የአደጋ ተጋላጭነት ለመቀነስ ከድህነት ወለል በታች የሚገኙና ለከፋ ድህነት ተጋላጭ የሆኑ የሕብረተሰብ ክፍሎችን በተለይም 60 በመቶ ሴቶችና ህፃናትን ማዕከል በማድረግ የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ስራን በማከናወን ባስገኘው ውጤታማ አፈጻጸም ፕሮጀክቱ ወደ 84 ከተሞች እንዲሰፋ ተደርጓል፡፡
በዛሬው ዕለት በይፋ የተጀመረው መድረክ ፕሮጀክቱ ካቀፋቸው አምስት ኮምፖነንቶች ውስጥ አንዱ የሆነው የከተሞች ልማታዊ ሴፍትኔትና ስራ ፕሮጀክት /UPSNJP/ ለአደጋ ጊዜ ምላሽ Contigenet Emergency Response Component አተገባበርን በይፋ ማስጀመር ሲሆን በዚህ ዙሪያ የፈጻሚና የባለድርሻ አካላትን የግንዛቤ ደረጃ በማሳደግ ኮምፖነንቱን ወደ ተግባር በማስገባት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ እንዲቻል ታስቦ የተዘጋጀ መድረክ ነው፡፡
በመድረኩ ላይ የአደጋ ጊዜ ምላሽ ኮምፖነንት ምንነት፣ የባለድርሻ አካላት ተግባርና ሃላፊነትና ቀጣይ አቅጣጫ፣ በአደጋ ጊዜ ምላሽ ኮምፖነንት የተከናወኑ ተግባራትን፣ በሳዑዲ አረቢያ ተመላሾች መልሶ ማቋቋም የተከናወኑ ተግባራትንና ቀጣይ አቅጣጫዎችን፣ እንዲሁም በአማራ ክልል የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን መልሶ የማቋቋም ተሞክሮን የተመለከቱ ሰነዶች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
በመጨረሻም ክብርት ሚኒስትሯና ክብርት ወ/ሮ አየለች እሼቴ፣ የኢፌዴሪ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ የውይይት መድረኩን በመምራትና አጠቃላይ አስተያየት በመስጠት በተነሱ ጉዳዮች ላይ የጋራ አቅጣጫን አስይዘዋል፡፡
ሪፖርተር፡- ስለሺ ዘገዬ
የካሜራ ባለሙያ፡- ዳዊት ወ/ገብርኤል
682 viewsedited 17:33