2021-05-11 16:46:21
እምነትቅዱስ መጽሐፋችን
ሰዎችን ሁሉ የሚያድን የእግዚአብሔር ጸጋ እንደተገለጠ ይነግረናል (ቲቶ 2:11)። ይህም ማለት ከሁለት ሺህ ዓመት በፊት በቀራንዮ የፈሰሰው የልጁ ደም ከ7 ቢሊዮን በላይ የሆነውን የአለማችንን ህዝብ ማዳን የሚችልበት አቅም አለው ማለት ነዉ። ይሁን እንጂ፤ በአሁኑ ጊዜ ሁሉም የሰው ዘር መዳን አልቻለም። ለምን?
ማመን ስላልቻለ! በኢየሱስ ላይ እምነት ስለሌለው። እምነት ምንድን ነው?
እምነት ማለት የማይታይን ነገር እንዳለ እርግጠኛ መሆን ነው። በአንዳች ምድራዊ ጥበብ ልታብራራው የማትችለውን ነገር እውነት እንደሆነ ለራስህ የምታረጋግጥበት ሁኔታ እምነት ይባላል። የዕብራውያን መልዕክት 11ኛው ምዕራፍ ስለ እምነት እና የእምነት ምሳሌ ስለሆኑ አባቶች ዘርዘር አድርጎ ያብራራልናል። እምነት ተስፋ የምናደርገውን ነገር እንደተቀበልን የምንቆጥርበት መሣሪያ ነው። አብርሃም የት እንደሚሄድ እንኳን ሳያውቅ በእግዚአብሔር ትዕዛዝ እንደወጣ፤ ሄኖክ በዓይን ያላየውን አምላክ አምኖ አካሄዱን ከእርሱ ጋር እንዳደረገ፤ ስለ ሌሎችም ይናገራል። ሁሉም ታሪኮች እጅግ ማራኪ ቢሆኑም እኔ ግን በግሌ ውስጤን የሚነካው የኖኅ ታሪክ ነው።
እግዚአብሔር በሰው ልጅ ኃጢአት ብዛት ከመከፋቱ የተነሳ በውሃ ጎርፍ ሊያጠፋቸው በወሰነ ጊዜ ኖኅ ግን በእርሱ ፊት ሞገስ አግኝቶ ነበር። በመሆኑም፤ ኖኅ እና ቤተሰቦቹ ከጥፋት የሚሰወሩበትን መርከብ ራሱ ኖኅ እንዲያዘጋጅ እግዚአብሔር አዝዞት ነበር። ነገር ግን ፤ እግዚአብሔር የመርከቡን ዲዛይን ሲሰጠው ለጥፋት ውሃው መምጣት ብዙ ዓመታት ቀርተው ነበር። በወቅቱ ዝናብ አልነበረም፤ ወይም ደግሞ የተለመደው መደበኛ ዝናብ ብቻ ነበር። ኖኅ ግን፤ በታዘዘው መሠረት እንጨት መቁረጡን፤ መጥረቡን፤ መላጉን እና መገጣጠሙን ጀምሯል። ለሚጠይቀው ሁሉ የጥፋት ውሃ ሊመጣ እንደሆነ ሲነግር በሙሉ ልቡ ነበር። በባዶ ቦታ ስለ የጥፋት ውሃ ሲያወራ ሳቅ ያመለጣቸው እንደነበሩ መገመት አይከብድም። ምናልባትም ኖኅ እብደት እየጀማመረው እንዳይሆን ሰግተው ያዘኑለትም አይጠፉም። እርሱ ግን በደረቅ መሬት ላይ ተቀምጦ በእምነት ዓይኑ በጥፋት ውሃ የተጥለቀለቀለችን ምድር ያይ ስለነበር የመርከብ ዝግጅት ሥራውን እያፋጠነ ነበር። ይህ እእንግዲህ እምነት ይባላል።
መጽሐፍ እንደሚናገር ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም። እግዚአብሔር አማኞችን ይወዳል። እንደ ዕብራውያን መልዕክት አንድ ሰው እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት በሁለት ነገር ላይ ጠንካራ እምነት ሊኖረው እንደሚገባ ያስረዳል። 1) እግዚአብሔር እንዳለ 2) ለሚጠይቁትም ነገር መልስ መስጠት እንደሚችል።
አንዳንድ ሰዎች እግዚአብሔርን "እስቲ እውን አንተ ካለህ እንዲህና እንዲያ አድርግና አረጋግጥልኝ" ይሉታል። ይህ እግዚአብሔር መልስ የማይሰጠው ጥያቄ ነው። ቢመልስም በበጎ እና ለበጎ ላይሆን ይችላልና እንዲህ አይነቱ ጥያቄ ለሥጋም ሆነ ለመንፈስ አይበጅም። በነገራችን ላይ፤ እግዚአብሔር አለ። ያንተ ጸሎት ቢመለስም ባይመለስም እርሱ አለ! ይኖራልም። የኛ ጥያቄ መልስ የማግኘት ያለ ማግኘት ጉዳይ የእርሱን ህልውና አያጸናም፤ አይሽርምም።
እግዚአብሔር እንዲሁ የሚያምኑትን ይወዳል። የኢየሱስን ቁስል በእጁ ነክቶ ካመነው ቶማስ ይልቅ ስለ ኢየሱስ ወሬ ሰምቶ ያመነ ሰው በብዙ እጥፍ የሚመሰገነውም ለዚህ ነዉ ። "ሳያዩ የሚያምኑ ብጹዓን ናቸው" ነውና መርሁ።
ጸጋና እምነት በአማኙ ሕይወት ውስጥ የማይነጣጠል፤ የማይነጻጸር ሚና አላቸው። ጸጋ ያለ እምነት በሰው ማንነት ውስጥ ሥራውን ሊሰራ ከቶ አይችልም። በሌላ አገላለጽ፤ ጸጋ ስላለ ብቻ ሰው ያለ እምነት ሊድን አይችልም። እምነት ስላለው ብቻም አይድንም። ሰው የዘላለም ሕይወት እንዲያገኝ እምነቱን በእግዚአብሔር ጸጋ ላይ ማድረግ አለበት (የሰው ልጅ እምነቱ በብዙ ነገር ላይ ሊሆን እንደሚችል ልብ ይሏል)። "ጸጋው በእምነት አድኖአችኋል" አይደል ቃሉ የሚለው (ኤፌ. 2:8)?
ስለዚህ ያላመነ በጸጋው አምኖ ይዳን! በጸጋው ያመነ እምነቱን አጽንቶ ይያዝ!
ጸጋ ብቻ! እምነት ብቻ!
የጸናው የትንቢት ቃል
1.2K views13:46