2023-02-20 14:35:26
የልኳንዳ ቤት በር ቡችላ
(በእውቀቱ ስዩም)
ሰፈራችን ባለው፥ የስጋ ቤት በራፍ
የገዛ ገላየን ፥እየጎተትኩኝ ሳልፍ
ሁልጊዜ የማያት ፥ ሚጢጢ ቡቸላ
ከስጋ ቤቱ በር ፥ ፊትለፊት ቁጭ ብላ
ወደ ሱቁ መስኮት ፥ አንገቷን አስግጋ
ትቁለጨለጫለች፥
ጅራቷን ከፍ አርጋ
እንደ ሰላም ሰንደቅ፥ ታውለበልባለች::
ነጋዴው በጠዋት፥ መስኮቱን ይከፍታል
ያቺን ግልገል ውሻ ፥ የጎሪጥ ያያታል
እንዳልተፈጠረች ወድያው ይረሳታል::
ቢላዋ ሰንዝሮ
ጎድን ከዳቢቱ፥ በየገጹ መትሮ
በግራም በኪሎ
ለየበላተኛው ሲያከፋፍል ውሎ
መስኮቱን ይዘጋል
ቀኑም እንደ ወትሮው ይመሻል ይነጋል::
ከዚያ በማግስቱም
ይቺ መከረኛ፤ የሙት ልጅ ቡችላ
የስጋ ትራፊ፤
ያጥንት ርጋፊ
ቢጥልልኝ ብላ
ትጠባበቃለች፤
ከስጋ ቤት በር ላይ ፥ ትቁለጨለጫለች
ያ ስጋ ቸርቻሪ፥ ባይለግሳት አዝኖ
ከሰው ንፍገት በላይ፥ ተስፋዋ መዝኖ
ምጽዋት ይጠብቃል፤ልቧ መቸ ቦዘኖ፤
እኛም እንደዚህ ነን፥
ሰላምን መጠበቅ፥ ከጦረኛ ዘመን
ከንፉግ ሰው ደጃፍ ፥ እንጀራ መለመን
መቸም የማይደክመን ፥
በገፊ መንደር ውስጥ፥ የሚያቅፈን ፍለጋ
እጅ የምንዘረጋ
ሞኝነት ቢመስልም፥ ለሚያየው በሩቁ፥
ተግቶ መጠበቁ
ከጦር ዘመን ሰላም ፤ ከንፉግ ሰው ሲሳይ
አንዳንድ ቀን አለ፥ ተአምር የሚያሳይ
አንዳንድ ቀን፥ አለ ፥ ተፈጥሮ ሚያስለውጥ
ስራት የሚያናውጥ
በዚህ ምክንያት ነው፥
ሰው ልምዶቹን ትቶ ፥ ህልሞቹን የሚያምነው::
65 views11:35