2022-03-21 16:59:50
በምሥራቅ ሸዋ ቡልቡላ ከተማ በሚሊሻ ምርቃት ላይ በደረሰ የቦንብ ፍንዳታ ቢያንስ አራት ሰዎች ሞቱ
በአዳሚ ቱሉ ጂዶ ኮምቦልቻ ቡልቡላ ከተማ ከ200 በላይ የሚሊሻ አባላት በተመረቁበት ወቅት በደረሰ የቦንብ ፍንዳታ የ12 ዓመት ታዳጊን ጨምሮ የአራት ሰዎች ሕይወት ማለፉን የወረዳው አስተዳዳሪ አስታውቀዋል።
ፍንዳታው የተከሰተው የምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ተጠናቅቆ የመንግሥት ባለሥልጣናት ከመድረኩ ከተሸኙ በኋላ ሕዝቡና የሚሊሻ አባላት በደስታ እየጨፈሩ እያለ መሆኑን ነው የተናገሩት።
ከሞቱን ውጭም 35 የሚሆኑ ደግሞ መቁሰላቸውን ባለሥልጣኑ ገልፀዋል።
አቶ ሙሐመድ አክለውም ፍንዳታውን በማድረስ የተጠረጠሩ ሦስት ሰዎች በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተደረገ ነው ብለዋል።
ከምረቃ ፕሮግራሙ በፊት አነስተኛ ፕሮግራሞች እንደነበሩ ያስታወሱት ኃላፊው፣ ዋናው የምረቃ ፕሮግራም ከመጀመሩ በፊት ጥብቅ ፍተሻ እንደነበር በመግለጽ፣ የቦንብ ፍንዳታው የደረሰው ተቀብሮ ይሆን ተወርውሮ እየተጣራ ነው ብለዋል።
በፍንዳታው ጉዳት ደርሶባቸው የሕክምና እርዳታ ያገኙ ተጎጂዎች አብዛኛዎቹ ወደ ቤታቸው መመለሳቸውን ገልፀው፣ ስድስት ሰዎች ግን እስካሁን ድረስ የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው መሆኑን ኃላፊው ተናግረዋል።
"ይህንን ቦንብ ያፈነዳው ጠላት" ነው ሲሉ የገለፁት ባለሥልጣኑ ፍንዳታውን ያደረሰው ማን እነደሆነ እየተጣራ መሆኑን ተናግረዋል። ለቦንብ ፍንዳታው እስካሁን ድረስ ኃላፊነቱን የወሰደ አካል የለም።
በዚህ ቦንብ ፍንዳታ ሕይወታቸው ያለፈ ሰዎች በትናንትናው ዕለት የቀብር ሥነ ስርዓታቸው መፈፀሙን ተናግረዋል ሲል የዘገበው ቢቢሲ ነው።
464 viewsJOHN , 13:59