2022-06-21 17:30:42
ሰውነታችሁን_ለሰይጣን_ምቹ_አታደርጉ!
ተወዳጆች ሆይ የብዙዎቻችን ሰውነት ለሰይጣን ምቹ ነው፡፡ ለሰይጣን ምቹ ሰውነት ማለት ንስሐ ያልገባ በኃጢአት ግራ የሚጋባ ሰውነት ነው፡፡ ለሰይጣን ምቹ የሆነ ሰውነት ማለት በሐሜት፣ በቧልት፣ በምቀኝነት፣ በክፋት፣ በዝሙት፣ በስኳር፣ በአድመኝነት፣ በዘረኝነት ወዘተ የረከሰ ሰውነት ማለት ነው፡፡
ለሰይጣን ምቹ ሰውነት ማለት ለፈጣሪ የማይንበረከክ፣ ሰማያዊ አምልኮት የማያቀርብ፣ የማይሰግድ፣ የማይጸልይ፣ የማይጾም፣ ቅዱስ ቁርባን የማይቀበል ነው፡፡ የአንዳንዶቻችን ሰውነት ለምጽዋት የተዘረጋ ነው፡፡ ነገር ግን በዝሙት የረከሰ ነው፡፡ ይህ ለሰይጣን ምቹ ነው፡፡ አንዳንዶቻችን ጸሎተኛ ነን፡፡ በጸሎተኝነታችን ልክ እጅግ ሐሜተኛ እና ቅናተኛ ነን፡፡ በዚህም ለሰይጣን ምቹ ነን፡፡
አንዳንዶቻችን እጅግ አማኝ እና ሰርክ ለኪዳን፣ ለቅዳሴ እና ለጉባኤ ከቤተ ክርስትያን የማንርቅ ነን፡፡ ነገር ግን ሲበዛ ቂመኛ እና ይቅርታ የለሾች ጨካኝ ነን፡፡ በዚህም ለሰይጣን ምቹ ነን፡፡ አንዳንዶቻችን ቅዱስ ቁርባን ተቀብለን አንደበታችንን በመዓዛ መለኮት ማጣፈጥ እየቻልን ‹‹እግዚአብሔር ይቅር ይበለኝና›› እያልን አንደበታችን በሐሜት የመረረ ነው፡፡ በዚህም ለሰይጣን ምቹ ነን፡፡
አንዳንዶቻችን በመንፈሳዊ እውቀታችን ሰዎችን መክረን፣ አስተምረን ከኃጢአት መልሰን ለንስሐ እናበቃለን እኛ ግን ተመክረን የማንሰማ፣ ከኃጢአታችን መመለስ ያቀተን፣ ንስሐ የማንገባ ለቅዱስ ቁርባን የማንበቃ ነን፡፡ በዚህ ለሰይጣን ምቹ ነን፡፡
አንዳንዶቻችን የወሲብ ፊልም ማየት፣ ግለ ወሲብ መፈጸም ኃጢአት እንደሆነ ለሰው እንናገራለን እናስተምራለን በዚህም እነዛ ሰዎች ከዚህ ሰይጣናዊ ሱስ ተላቀው ንስሐ ይገባሉ ልማደ ሰይጣንንም ይተዋሉ፤ እኛ ግን ሰው ባላየ እግዚአብሔር ባየ የወሲብ ፊልም እናያለን ግለ ወሲብ እንፈጽማለን፡፡ በዚህም ለሰይጣን እንመቻለን፡፡
አንዳንዶቻችን መጽውቱ ብለን ሰዎች እንዲመጸውቱ፣ ድሆችን እንዲረዱ እናደርጋለን፡፡ የእኛ እጅ ግን በታንክ ፍሬን ተይዟል፣ መመጽወትም እንቢ ብሎናል፡፡ በዚህም ለሰይጣን ምቹ ነን፡፡
አንዳንዶቻችን ሰዎች ሲያማቸው እንዲጸልዩ፣ ጸበል እንዲጠመቁና በዚህም እንደሚድኑ መክረን እነዛ ሰዎች በምክራችን ተጠቅመው ጸልየው ተጠምቀው ይድናሉ፡፡ እኛ ስንታመም ግን እምነት አጥተን በየሆስፒታሉ እንንከራተታለን፡፡ በዚህ ለሰይጣን ምቹ ነን፡፡
ወዳጆቼ በየትኛውም ጉድለታችን ሰይጣን ወደ ሕይወታችን ይገባል፡፡ ሰይጣን ትንሿን ስህተታችንን፣ የኃጢአት ፍላጎታችንን አይቶ ወደ እኛ ጎራ ይልና ትንሿን ስህተት ትልቅ፣ ኃጢአትን ደግሞ ጽድቅ አድርጎ የእሱ መጫወቻ ያደርገናል፡፡
ሰይጣን አንዴ በዝሙት ከጣለን ስሜታችን ደግሞ ደጋግሞ ይጥለናል፡፡ ሰይጣን በመርፌ ቀዳዳ ስህተት ይገባና እኛ ግን ከስህተታችን በሰፊው በር መውጣት ያቅተናል፡፡
ዛሬ ሥጋዊ ፍላጎታችን፣ ዓላማችን፣ እውቀታችን፣ ትምህርታችን፣ ርእዮተ ዓለማችን፣ አመለካከታችን በራሱ ለሰይጣን ምቹ ስለሚሆን ልናስተውል እና ልንነቃ ይገባናል፡፡ ዛሬ ከላይ እስከታች፣ ከቤተ ክህነት እስከ ቤተ መንግስት፣ ከዓለማዊው እስከ መንፈሳዊው፣ ከምሁሩ እስከ ፊደል ነውሩ፣ ከወጣቱ እስከ አዛውንቱ ያለነው ሰውነታችን ለሰይጣን ምቹ ስለሆነ ሕይወታችን በፈተና፣ በስቃይ፣ በመንፈሳዊ ባዶነት የተመላ ነው፡፡
እግዚአብሔር ‹‹እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝና፣ ሰውነታችሁን ቀድሱ፣ ቅዱሳንም ሁኑ›› ብሎ አዞናል፡፡
ነገር ግን ሰውነታችንን በኃጢአት አረከስን፣ ሕገ እግዚአብሔርንም አፈረስን፡፡ በዚህም ለሰይጣን ምቹ ሆንን፡፡ ሰይጣን ለራሱ ምቹ በሆነ ሰው እና ሰውነት ላይ እንደፈለገ ይሆናል፣ የፈለገውን ዓላማ ይፈጽማል፣ ለሚፈልገው ዓላማ መጠቀሚያ ያደርገዋል፡፡ /ዘሌ 11÷44/
ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሕያው ቅዱስም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እለምናችኃለሁ›› በማለት የልመና ጥሪ ያቀርብልናል፡፡ /ሮሜ 12÷1/
በእውነት ሰውነታችን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ነው? ሰውነታችን ቅዱስ እና መሥዋዕት ነው? ሰውነት በኃጢአት ሲረክስ ነፍስም ትረክሳለች፡፡
ልብ በሉ ቆሻሻ ነገር ላይ እና ቆሻሻ ስፍራ ላይ ዝንቦች ይሰፍራሉ፡፡ በኃጢአት የቆሸሸ እና የተበላሸ ሰውነት ላይ አጋንንት ይሰፍራሉ፡፡ በቆሻሻ ነገር እና በቆሻሻ ስፍራ ላይ ዝንቦች ለሰው ጎጂ የሆኑ በሽታዎችን ያከማቻሉ፡፡
በኃጢአት በቆሸሸ ሰውነት ላይም አጋንንት መንፈሳዊ ሕይወታችንን የሚያጠለሽ፣ ነፍሳችንን የሚያቆሽሽ ክፉ መርዙን ይረጫል፣ ጎጂ የሆነ ኃጢአትንም ያጠራቅማል፣ የሥጋ እና የነፍስ በሽታ ይሆናል፡፡
እግዚአብሔር በዘሌ 11÷43 ላይ ‹‹በእነርሱ እንዳትረክሱ ሰውነታችሁን አታርክሱ›› ብሎናል ‹‹በእነርሱ እንዳትረክሱ›› ያለው አንድም በሰይጣን ክፉ ምሪት እና ተግባራት ሰውነታችንን፣ ነፍሳችንን እንዳናረክስ ነው፡፡
ስለዚህ ሰውነታችሁን ለንስሐ፣ ለጽድቅ፣ ለጾም፣ ለጸሎት፣ ለስግደት እና ለቅዱስ ቁርባን ምቹ አድርጉ እንጂ በፍጹም ለሰይጣን ምቹ አታድርጉ፡፡
በቀሲስ ሄኖክ ወልደ- ማርያም
286 viewsmihret jiff, 14:30