2022-07-18 21:01:30
:::::::::::መንታ መንገድ::::::::::::::
ክፍል ኝ
ፀሀፊ fuad seid
ጁምዓ(አርብ) ጠዋት ሀጅራ ተሰናብታን ወደ ኮምቦልቻ ሄደች። እኔ ሀያት እና ራሄል አራት ሰዓት ላይ ባጃጅ ተኮናትረን ወደ ኤርፖርት ሄድን። ወደ አዲስ አበባ አምስት ሰዓት ላይ ልንበር ትኬት ቆርጠናል። በርግጥ ባለፈዉ ሴሚስተር በሰላም ባስ ነበር የሄድነዉ። መንገዱ ረዥም ስለሆነ እየተጫወትን ቆንጆ ጊዜ አሳልፈናል። ባሁኑ ግን ራሄል የአባይ በረሀ መንገድ ሙቀቱም የመንገዱም አስፈሪነት ስለከበዳት በአዉሮፕላን እንሂድ ስላለች ለሷዉ ብለን ነዉ በአዉሮፕላን ለመሄድ የወሰንነዉ።
.
እኔ ከነሀያት እና ራሄል ተነጥዬ ወደዛ ጭቅጭቅ ወደማያባራበት ቤት ልመለስ መሆኑን ሳስበዉ ሸከከኝ። እዛ ቤት ዉስጥ ከአባቴ በስተቀር ማንም ጉዳዬ አይደለም። እናቴ ደዉላ ዛሬ እንደምመጣ ስነግራት በጣም ነበር ደስ ያላት! ስመለስ መርዝ ምላሷ ዕረፍት ይሰጠኝ ይመስል።
ሀያት አዉሮፕላን ዉስጥ እንደገባን "የቁርጡ ቀን ደረሰልህ!" አለችኝ ወደኔ እየዞረች። ሀያት ከፊት ለፊቴ ነበር የተቀመጠችዉ። እኔና ሪቾ ደሞ አንድ ላይ!
"በየቀኑ ላንገናኝ መሆኑን ሳስበዉ ይቀፈኛል።" አለች ራሄል የሀያትን ንግግር እንዲሁ ተረድታዉ። ሀያት ግን ለኔ የመተጫጨቱ ጊዜ ደረሰ ለማለት ነበር እንደዛ ያለችዉ። አይኖቿ ዉስጥ ትርጉም ነበር።
"አዎ ሪቾ አሁን ከናንተ ጋር መብላት ለምጄ ቤት እንዴት እንደሚበላልኝ እኔንጃ" አልኩ ያሳለፍናቸዉ ጊዜዎች ዉል እያሉብኝ።
"እኔ ራሱ!" አለች ሀያት በረዥሙ እየተነፈሰች።
"አቦ ሀጅራም አለች ኮምቦልቻ ያለችዉ ክረምቱን ሙሉ የማታገኘን እኛ እኮ ሸገር ነን ፈታ በሉ!" አለች ሪቾ ራሷ በጀመረችዉ ጨዋታ ስንተክዝ ደብሯት።
ጓደኝነት ግን ከየትኛዉም ግንኙነት የላቀ አስደሳች ግንኙነት ነዉ። ባላሰበከዉ ሰዓት ወደ ህይወትህ የሚመጡ ሰዎች የህይወትህን አዳፋ ሁሉ አጥርተዉ የማይረሳ ትዝታ ያትሙብሀል። ግን ችግሩ ጓደኝነቱ በተቃራኒ ፆታ መካከል ሲሆን ወደ ፆታዊ ፍቅር የመቀየር እድሉ ከፍተኛ መሆኑ ነዉ። ይኸዉ የኔ ጉዶች ሀጅራ ብቻ ናት እኮ አፈቀርኩህ ያላለችዉ።
.
አዲስ አበባ ደርሰን ከቦሌ አየርመንገድ ስንወጣ ሀዩ እናቷ እና ታናሽ እህቷ መኪናቸዉን ተደግፈዉ ቆመዉ ሲጠብቋት አየቻቸዉ። የሀያት ታናሽ እህት መግፊራ ትባላለች። ስገምት 18 ዓመት ይሆናታል። ልክ እንደ ሀዩ ቀሽት ናት። ሀያት ፈገግ አለችና ሻንጣዋን ጥላ እየሮጠች ሄዳ መግፊራ ላይ ተጠመጠመች። ከዚያም እናቷ እያገላበጡ ሳሟት። ሀያት እና እህቷ በጣም ይዋደዳሉ። ባህርዳር ሆነን ራሱ በየቀኑ ለረዥም ሰዓት ነበር በስልክ የሚያወሩት። ሲያስቀኑ! አሉ እንጂ የእኔ እህቶች መልክ ብቻ የወንድም ፍቅር የማያዉቁ ደነዞች!
እኔና ሪቾ የራሳችንን እና የሀዩን ሻንጣ እየገፋን የነሀዩ መኪና ጋር ደረስን።
ሀያት እናቷን እና እህቷን አስተዋወቀችን! በስም እንኳ በደንብ ያዉቁናል።
"አክረም እሱ ነዉ" አለች ሀያት ወደ እኔ እየጠቆመች።
"ዋዉ መግፊራ እባላለሁ" አለች እህቷ ፍጥን ብላ። ሀያት ያን ተፍለቅላቂ ሳቋን ለቀቀችዉ። የእህቷ አባባል በጣም ያስቅ ነበር። ሀዩ እንዳፈቀረችኝ ለእህቷ ነግራት እንደነበር ከመግፊራ አኳኋን ተረዳሁ።
"ሴት አይጨብጥም ያልሽኝ እሱን ነዉ? ማሻ አላህ ልጅ እንዲህ ሲያድብ ደስ ይላል!!" አሉ የሀያት እናት።
ሀዩ ጠቅሳኝ ወደ መኪናዉ ገባች። መኪናዉን አስነስተዉ ሲሄዱ መግፊራ እጇን የስንብት አዉለበለበችልን።
.
ቤት እንደገባሁ እህቶቼ መጥተዉ ተጠመጠሙብኝ። ምን ያስመስላሉ?! ከናፈቅኳቸዉ አይደዉሉልኝም ነበር?! እዚ ከአስሩ ጎረምሳ ጋር ከሚጀናጀኑ! ብሽቆች!
እናቴ "አክረሜ የኔ አንበሳ! ለምን የምትደርስበትን ሰዓት አልነገርከንም? በመኪና አመጣህ አልነበረም በኮንትራት ከምትመጣ?!" አለች ሱፍራ እያነጠፈች። ሱፍራ ምግብ ሲቀርብ ምንጣፍ ላይ እንዳይንጠባጠብ ለመከላከል የሚነጠፍ ላስቲክ ነዉ።
ፈገግ ብዬ ዝም አልኩኝ ምንም ማዉራት አልፈለግኩም። ከሁለቱ እህቶቼ ትንሿ ትንሽ ትሻላለች 16 ዓመቷ ነዉ። ኢስራዕ ትባላለች። ትልቋ ደሞ 18 ዓመቷን ልትይዝ ምንም አልቀራትም። መርየም ትባላለች። እማዬ ምግብ አቅርባልኝ ስትወጣ ኢስራዕን ጠራኋት። ልክ አጠገቤ እንደተቀመጠች "ኢስሩ አክስቴ አዚዛ እና ሰሚራ እዚህ መምጣት ያቆሙት ለምንድነዉ?" አልኳት።
ድምጿን ዝቅ አድርጋ "ሁለቴ የመጡ ቀን ማማ ባዶ ቤት ትታቸዉ ወጣች። ከዛ በኋላ መጥተዉ አያዉቁም።" አለችኝ።
ሰዉ እንዴት እድሜዉ ሲጨምር አስተሳሰቡ አብሮ አያድግም? ለሰዉ እኮ እድሜ ራሱ ትምህርት አለዉ። እናቴ ከምወዳቸዉ አክስቶቼ ጋር እንደቆራረጠችን ሳስብ ተናደድኩ። እናቴ መልከኛ ናት ግን ፀባይ አላደላትም። እኔም ቤት ስለማላዘወትርና ሀይማኖታዊ ቡድኖች እንዲሁም የኪነ ጥበብ ማህበሮች ዉስጥ በመሳተፍ ራሴን ስለማጨናንቅ እንጂ የእናቴን ፀባይ እወርስ ነበር።
በመሀል መርየም "በቃ አክረሜ መዉጣቴ ነዉ!" ብላኝ ወጣች። አለባበሷ ይሰቀጥጣል። ቀሚሱ የመቀመጫዋን እንቅስቃሴ በደንብ ነዉ የሚያሳየዉ። ገና ከመምጣቴ መጨቃጨቅ ስላልፈለግኩ ዝም አልኳት። እንዲህ ተኳኩላ የት ልትሄድ እንደምትችል አይጠፋኝም። ጓደኞቼ እኮ ሴቶች ናቸዉ።
.
ትንሽ እንደቆየሁ ኢስራዕን "እስሪ እስኪ ነይ ምርጥ ካፌ ዉሰጂኝ ፒዛ ልጋብዝሽ!" አልኳት ኢስራዕ ፒዛ ነፍሷ ነዉ። እኔ የሰፈራችን ካፌዎች ጠፍተዉኝ ሳይሆን በኢስራዕ እይታ ምርጥ የሚባለዉን ካፌ ለማወቅ ነዉ። በርግጠኝነት ደሞ መርየምን እዛ አገኛታለሁ።
ይቀጥላል..............
ይቀላቀሉን
@joyyeg
@joyyeg
151 viewsHabesha, 18:01