2022-07-07 13:39:55
፨
በእንተ ማርቆስ 16:9-20 ፨
ክፍል ፬
ከዚህ በፊት በነበሩት ሶስት ክፍሎች የማርቆስ ወንጌል መደምደሚያ ክፍልን ታሪካዊነት የሚተቹ ሰዎች የሚያቀርቡትን ደካማ ሙግትና እነዚህ አካላት ከሚጠቅሷቸው ጽሑፎችና ምስክሮች ብዙ ዓመታት ቀድመው የኖሩ አባቶች ስለ ክፍሉ ታሪካዊነት የተናገሩትን ምስክርነት አይተናል።
በትችት አቅራቢዎቹ የሚነሱት ዋነኛ "ማስረጃዎች" ታዲያ ኮዴክስ ሳይኔቲከስና ኮዴክስ ቫቲካነስ የተሰኙ ሁለት እደ-ክታባት ናቸው። እነዚህ ቅጂዎች በአንጻራዊነት ጥሩ የሚባል የጽሕፈት ጥራትና እድሜ ስላላቸው የማርቆስ ወንጌል ማገባደጃ ክፍልን አለመያዛቸው የክፍሉን ታሪካዊ አለመሆን ያሳያል የሚለው ሙግት ደጋግመን የምንሰማው ነው። ይህ ድምዳሜ ግን ፈጽሞ ከእውነታ የራቀ መሆኑን መገንዘብ አይከብድም።
በመጀመሪያ እነዚህ ሁለቱ እደ-ክታባት የተጻፉት በአራተኛ ክፍለዘመን አጋማሽ አካባቢ ነው። ከዚህ በፊት እንዳየነው ደግሞ ሄሬኔዎስና ዮስጢኖስን ጨምሮ ሌሎች ብዙ አባቶች የማርቆስ ወንጌልን የመጨረሻ ክፍል እንደሚያውቁ እርግጥ ነው። ታዲያ እነዚህ አባቶች በሙሉ ከሁለቱ ኮዴክሶች ብዙ ዓመታት በፊት መኖራቸውን ልብ ይሏል። ይህ በሆነበት ሁኔታ ሁለቱ ኮዴክሶች ክፍሉን ባይዙ እንኳን የምናወራለት ክፍል ከዚያ የቀደመ እድሜ ስላለው የእደ-ክታባቱ ሙግት የማርቆስ ወንጌል ማገባደጃ ክፍል አለም-አቀፋዊ ተቀባይነት እንዳልነበረው ከማሳየት ውጪ ምንም አያረጋግጥም።
ከዚህ ባለፈ ግን የኮዴክስ ቫቲካነስ ጸሐፊ እንኳን ክፍሉን ያውቀው እንደነበር የሚያሳይ አጻጻፍ ተጠቅሟል። በዚህ እደ-ክታብ ውስጥ ጸሐፊው በምስሉ እንደምትመለከቱት ጽሑፉን በሶስት ረድፎች የገለበጠ ሲሆን የማርቆስ ወንጌል አልቆ የሉቃስ ወንጌልን መጻፍ ሲጀምር ግን አንድ ረድፍ ከግማሽ ክፍት ቦታ በመተው ነበር። ይህ ደግሞ ጸሐፊው በእርግጥም ክፍሉን ያውቀው እንደነበርና የእደ-ክታቡ ባለቤት ልክ መስሎ ከታየው ክፍሉን በራሱ እንዲጽፍበት ምርጫ እየሰጠው እንደሆነ የሚያሳይ ነው። ምንም እንኳን በሌሎች ክፍሎችም ተመሳሳይ ክፍት ቦታዎች ብናገኝም እነዚህ ክፍተቶች ግን የራሳቸው ማብራሪያ ሊቀርብላቸው የሚችሉ ናቸው። ለምሳሌ አንዱ ክፍት ቦታ መጽሐፈ ዕዝራ ካልዕ አልቆ መዝሙረ ዳዊት ሲጀምር የሚገኝ ሲሆን ይህ ክፍተት ግን መጽሐፈ ዕዝራ በሶስት ረድፍ ተጽፎ መዝሙረ ዳዊት ግን በሁለት ረድፍ በመጻፉ ጽሐፊው የአጻጻፍ ቅርጹን ለመለወጥ እንዲያመቸው የግድ ክፍት ቦታ መተው ስላስፈለገው የተፈጠረ ነው። ከዚህ ባለፈ ክፍት ቦታው ከሞላ ጎደል የማርቆስ ወንጌል 16:9-20 ን ለመጻፍ የሚበቃ መሆኑ በራሱ ጸሐፊው ክፍተቱን ለዚሁ ዓላማ እንደተወው የሚያሳይ ነው።
አስቀድመን እንዳልነው ይህ የማርቆስ ወንጌል ክፍል ከማንኛውም እጃችን ላይ ካሉ እደ-ክታባት የቀደመ የአባቶች ምስክርነት ያለው ነው። ካሉን በሺህ የሚቆጠሩ የአዲስ ኪዳን እደ-ክታባት ውስጥ ክፍሉን ያልያዙት እደ-ክታባት ብዛት ሶስት ብቻ መሆኑ ደግሞ ከረጅሙ የማርቆስ ወንጌል ማገባደጃ ይልቅ ቁጥር ስምንት ላይ የሚያልቁ ቅጂዎች እጅግ ያልተለመዱ እንደነበሩ የሚያሳይ ነው። ይህ ደግሞ ለማርቆስ ወንጌል ማገባደጃ ክፍል ከረጅም እድሜ በተጨማሪ አለም-አቀፋዊ ተቀባይነትን የሚሰጥ ነው።
Reference
-Authentic; The Case for Mark 16:9-20 by James snapp Jr.
@Jacobite_apologetics27
264 viewsTinsae, edited 10:39