2021-11-06 18:53:56
የመድኃኔዓለም ወዳጅ - መብዓ ጽዮን
(ዲ/ን ሕሊና በለጠ)
መድኃኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ራሱን አሳልፎ በመስጠት ለዓለም መድኃኒት የሆነው መጋቢት 27 በዕለተ ዓርብ መኾኑ የታወቀ ነው፡፡ (ይህም ዕለት የስቅለት በዓል ነው፡፡ መጋቢት 27 ጥንተ ስቅለት ነው፡፡ መጋቢት 29 ደግሞ ጌታ የተነሣበት በመሆኑ ጥንተ ትንሣኤ ነው፡፡) በዚህም የተነሣ ምንም እንኳን ዓመታዊው ዋናው በዓል መጋቢት 27 ቢሆንም ወር በገባ በ27 መድኃኔዓለምን እንዘክራለን፡፡
ጥቅምት 27 ዓመታዊ በዓል ሆኖ የሚከበርበት ምክንያት ሁለት እንደ ኾነ ትውፊታችን ይመሰክራል። (የመጽሐፍ ምንጩን ያገኘ ቢጠቁመኝ አመስጋኝ ነኝ)።
የመጀመሪያው ምክንያት መጋቢት 27 ዐቢይ ጾም ከሚውልባቸው ቀናት አንዱ በመሆኑና በዐቢይ ጾም ደግሞ ዐበይት በዓላትን በድምቀት ለማክበር ወቅቱ የማይፈቅድ ስለ ሆነ ከአባ መብዓ ጽዮን መታሰቢያ በዓል ጋር በጥቅምት 27 እንዲከበር አባቶች ቀኖና በመሥራታቸው ነው፡፡
ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የመድኃኔዓለምና የኪዳነምሕረት ወዳጅ አባ መብዓ ጽዮን የሚታሰቡበት ዕለት ጥቅምት 27 በመኾኑ ነው፡፡
አባ መብዓ ጽዮን ማን ናቸው?
አባ መብዓ ጽዮን አባታቸው ሀብተ ጽዮን እናታቸው ጽዮን ትኩና ይባላሉ፡፡ በንጹሕ ጋብቻ ተወስነው በፍቅር እየኖሩ ዘወትር እግዚአብሔርን ልጅ እንዲሰጣቸው ይለምኑት ነበርና ደም ግባቱ ያማረ መልኩም ብሩህ የሆነ ሁለመናው ንጹሕ የሆነ ልጅን ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ደስ ተሰኝተው አስቀድመው እንደ ተሳሉት ስሙን መብዓ ጽዮን አሉት፡፡
ትንሽም ባደገ ጊዜ አንድ ካህን እሱ ወዳለበት ሀገር በእንግድነት መጣ፤ የሕፃኑም አባት ተቀብሎ ቤቱ አሳደረው፡፡
ለዚህም እንግዳ ከተወደደ ልጇ ጋር የእመቤታችን ሥዕል ነበረችው፤ ሲተኛም ይህቺን ሥዕል በራስጌው አኖራት፣ ማለዳም ተነሥቶ ሥዕሊቱን ረስቶ ሔደ፡፡
እንግዳው ረስቷት የሔደውን ሥዕል ሕፃኑ መብዓ ጽዮን አገኛት፣ዐቀፋት፣ ሳማትም፣ ደስም ተሰኘባት፤ ለሌላ ሰውም አልሰጥም አለ፣ በአንገቱም አሠራት፡፡ አባቱም ይሄን አይቶ ይህችን ሥዕል እንዳላቆያት የእኔ አይደለችም፣ለባለቤቱ እንዳልሰጥ ያለበትን አላውቅ ብሎ ተጨነቀ፡፡
ከዕለታት በአንዲት ቀንም ከዚያ ካህን ጋር ተገናኘና ሥዕልህን ከእኔ ቤት የተውካት ለምንድን ነው? አሁን በእግዚአብሔር ቸርነት አግኝቼሀለሁና ሥዕልህን ውሰድ አለው፡፡
ያም ሰው ሥዕሏን ማን እንዳገኛት አባትየውን ጠይቆ ሕፃኑ እንዳገኛት፣ ካገኛትም ጀምሮ እጅግ በመውደድ ለማንም አልሰጥም ማለቱን ተረዳ፡፡ አባትየውም ከሕፃኑ በግድ ቀምቼ አመጣታለሁ ሲል ካሕኑ ከለከለው፡፡ “የሥዕሊቱም ባለቤት ወዳለታለች፣ እኔንማ ብትወድ ባልተረሳችኝም ነበር፡፡ ለዚያ ለአገኛት ሕፃን ትሁነው” አለው፡፡
አባቱም በልጁ ላይ ስለ ሆነው ስጦታ አደነቀ፡፡
ሕፃኑ ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስ የዳዊትን መዝሙርና የሕግን መጻሕፍት ሁሉ ያስተምረው ጀመረ፣ዲቁና ተሾመ፡፡
በሥራውም ሁሉ ልበኛና ጥበበኛ የዜማውም መዓዛ የጣፈጠ እንደ ሆነ ባየ ጊዜ ቅኔን ይማር ዘንድ የዮሐንስ ደብር ወደምትሆን ወደ ደብረ ማርያም ወሰደው፡፡ የአንደገባጦንንም አውራጃ ሁሉ የሚገዛ መምህር በዚያ ነበረ፤ መብዓ ጽዮንንም ለሱና ለአንድነቱ መነኮሳት አደራ ሰጠው፡፡
አባ ስምዖንና አባ አዝቂርም ስምህ ማነው ብለው ጠየቁት፣ መብዓ ጽዮን ነው አላቸው፡፡ ከመምህራን ሁሉ እንዲህ ያለ ስምስ አይገባም ስምህ ተክለ ማርያም ይባል እንጂ አንተ ሕፃን ነህና አሉት፡፡ በዚህም የተነሣ ባለ ሁለት ስም ሆነ፡፡ ቅኔንና የጥበብ መጻሕፍት፣ተግሣጽንም ጾምና ጸሎትን ሥዕል መሣልን መጽሐፍ መጻፍን ሁሉ ተማረ፣ በመንፈሳዊ ሥራ ሁሉ ፍጹም ሆነ፡፡
…ከዕለታት በአንድ ቀን አንድ ልጅ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ከተቀበለ በኋላ ከቤተክርስቲያን ወጥቶ ሲሔድ እግሩን ዕንቅፋት ተመታ፣ ደሙም ከመሬት ፈሰሰ፡፡
ዕውቀትን የተመላ ሕፃኑ መብዓ ጽዮን ይህን ዐይቶ ደረቱን መታ፣ ስለሱም ደሜ ይፍሰስ አለ፡፡ እያደነቀም ዕንቅፋት የተመታው ልጅ ከቤቱ እስኪደርስ ከኋላው ተከተለው፡፡
ከሱም ዘንድ ደርሶ ስለመድኃኔዓለም ሥጋና ደም ክብር የደማውን ጣቱን እስኪደርቅ ድረስ ጠባው፡፡ ጓደኞቹም ደሙን ከአፈሩ ጋራ ሲበላ ባዩ ጊዜ የሳቁ አሉ፤ በልቡናቸውም ያደነቁ አሉ፡፡
…ከዕለታት በአንድ ቀን አንድ ልጅ ከቆረበ በኋላ የበላው የጠጣውን ሁሉ አስመለሰው፡፡ ይህ ብፁዓዊ ግን ስለ ጌታችን ስለ መድኃኔዓለም ፍቅር በጻሕል ተቀበለው፡፡
…ከዕለታት በአንድ ቀን አባታችን መብዓ ጽዮን ቁሞ በመትጋት እየጸለየ ሳለ አንድ ሕፃን የወርቅ በትርን ይዞ ከሕፃናት ጋራ ሲጫወት በሩቅ አየ፡፡
በዚያን ጊዜ ደም ግባቱ ያማረ የወርቅ በትር በእጁ የተያዘ ይህ ልጅ የማነው የንጉሥ ልጅ ይመስላል ብሎ አሰበ፡፡ እሱ ጌታ መድኅንም መሆኑን ከቃሉ አውቆ ያን በትር ተቀበለው በእጁም ያዘው፡፡ ሕፃኑም መልስልኝ አለው፡፡ አባታችን መብዓ ጽዮንም ለሕፃኑ ሰገደ፣ እኔ ጌታዬ በደለኛ ባርያም ሆኜ ሳለ ከአንተ ጋር እነጋገር ዘንድ አይገባኝም አንተ የሰማይና የምድር ንጉሥ ነህና አለው፡፡
እኔ ካሠለጠንኩህ በኋላ ምን አለብህ አለው፡፡ ከዚህም በኋላ ከሱ ጋር ተቀመጠ እንደ ሕፃናትም ተጫወተ በጀርባውም ታዘለ በእጁም ታቀፈ፡፡
መውደዱንና የዋሕነቱንም ባየ ጊዜ አባታችን መብዓ ጽዮን ሕፃኑን ለመነው፡፡ መድኅን ሆይ መሐላህን አስብ በስምህ ተጠምቀው ወደ ደይን የወረዱትን ነፍሳት ማርልኝ አለው፡፡ መድኃኔዓለምም ቃልህ የጣፈጠ ነው፣ እነሆ አንተ ወደ ሲዖል ውረድ መሸከምም የምትችለውን ያህል ነፍሳትን አውጣ አለው፡፡አባታችን ተክለማርያምም /መብዓ ጽዮንም/ እኔ ደካማና ምስኪን ነኝ ወደ ሲኦል መውረድ በምን እችላለሁ አለው፡፡ ጌታም እኔ እልክሀለሁ ብሎ የወርቅ በትር ሰጠው፣ የዚያን ጊዜ ኃይልን ከመድኃኔዓለም ተቀብሎ ክንፍ እንዳለው በረረ፡፡ ወደ ሲኦልም ገባ፣ ሲኦልም በመድኃኔዓለም ሥልጣን ወዲያና ወዲህ ተከፈለ፡፡ በዚያም የኃጥኣን ነፍሳትን ፍጹም ጩኸትንና ልቅሶን ሰማ፡፡
በዚያን ጊዜ በሲዖል ያሉ ነፍሳት አይተውት በረሩ፡፡ ነፍስ በነፍስ ላይ ፈጽመው እስኪ ከብዱት ድረስ እንደ ንብ ተጫኑ፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር ኃይል አስቻለው፡፡ በፊት እንደ ሆነውም ነፍሳትን ተሸክሞ ወደሱ መጣ፡፡
መድኃኔዓለምም በፍጹም ደስታ ... ይህን ያህል ነፍሳት ማን አውጣ አለህ አለው፤ አባታችን መብዓ ጽዮንም እኔ በምን ኃይሌ አወጣለሁ ባንተ ኃይልና በጸጋህ በፈቃድህም ነው እንጂ አለው፡፡ ጌታዬ መድኃኔዓለም ሆይ እኔ አፈርና ትቢያ ስሆን እንደ ባሕር አሸዋ ቁጥራቸው የማይታወቅ ይህን ያህል ነፍሳትን አወጣ ዘንድ በምን እችላለሁ?
መድኃኔዓለምም እነዚህን ነፍሳት ለአንተ አሥራት ይሁኑህ፣ ደስታ ወዳለበት ገነት አግባቸው አለው፡፡ ከዚህም በኋላ ለዘለዓለም የማይሞት ሕያው ከሱ ተሠወረ፡፡
የአምላካችን የመድኃኔዓለም ቸርነት የአባታችን የመብዓ ጽዮን ምልጃ ከኛ ጋር ይሁን፡፡
አባ መብዓ ጽዮን ደካማ ባርያውን ከመድኃኔዓለም ያማልደኝ ዘንድ ኃይለማርያም ብላችሁ አስቡኝ።
ጥቅምት 27፣ 2010 ዓ.ም.
4.3K views15:53