2022-06-23 02:34:05
ⒶⓇⓉⒾⓄⓈ
ⒶⓇⓉⒾⓄⓈ
Artios Devotion
ⒺⓅⒽⒺⓈⒾⒶⓃⓈ
ⒹⒶⓎ #1
የባረከን ይባረክ
የኤፌሶን መልዕክት 1:1-3
====================================
"በእግዚአብሔር ፈቃድ የክርስቶስ ኢየሱስ ሐዋርያ ከሆነው ከጳውሎስ፤ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉ፣ ለታመኑ፣ በኤፌሶን ለሚገኙ ቅዱሳን፤ ከእግዚአብሔር ከአባታችን፣ ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን። በሰማያዊ ስፍራ በመንፈሳዊ በረከት ሁሉ በክርስቶስ የባረከን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ"።
====================================
የደብዳቤው መግቢያ እንደ መሆኑ መጠን በእነዚህ የመጀመሪያዎቹ ቁጥሮች ውስጥ የጻፊውን ማንነት፣ ተደራሲያኑንና የመልዕክቱን ቁልፍ ሃሳብ እናገኛለን።
የዚህ መልዕክት ጸሐፊ ሐዋርያው ጳውሎስ መሆኑን እራሱ በቁ.1 ላይ በግልጽ አስቀምጦታል። ከጥንት ጀምሮ በደብዳቤው ደራሲ ማንነት ላይ ጥያቄ ባይነሳም ሁሉን ነገር ካልተቃወማችሁ የተባሉ ይመስል መቧጨር ልማዳቸው የሆነ አንዳንድ ዘመነኛ የሥነ መለኮት ምሁራን እንደ ለመዱት እርሱ አይደለም ቢሉም ውሃ የሚቋጥር ምክንያት ግን ማቅረብ አልቻሉም።
ጳውሎስ በሌሎች ደብዳቤዎች ሁሉ እንደሚያደርገው እራሱን ሐዋርያ ብሎ ይጠራል። ሐዋሪያ ማለት ቀጥተኛ ትርጉሙ የተላከ ማለት ሲሆን ጳውሎስ ይህን ስያሜ የሚጠቀመው የራሱን ሹመት ለማጉላት ሳይሆን የመልዕክቱን እውነተኛነት፣ ተዓማኒነትና ከጌታ የተቀበለው መሆኑን ለመግጽ ነው።
የመልዕክቱ ተደራሲያን በኤፌሶን የሚገኙ ቅዱሳ፣ በዚያች ከተማ ዙሪያ ለሚኖሩ ወገኖች፣ ደግሞም እስከ ንጥቀት ድረስ በዚህ ምድር ላይ ላሉት ቅዱሳን ሁሉ እንደሆነ የደብዳቤው ይዘት ያመላክታል።
እዚህ ላይ ሳልጠቅሰው ማለፍ የማልፈልገው ጉዳይ ቀደም ብለው በነበሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂዎች ላይ "በኤፌሶን ለሚገኙ ቅዱሳን" የሚል ሐረግ ስለሌለ ይህ መልዕክት በትንሿ ኤስያ አከባቢ ላሉት ቅዱሳን ሁሉ የተላከና እየተዘዋወረ የሚነበብ መልዕክት ነው የሚሉ ወገኖች ብዙ ናቸው። በእኔ ምልከታ ለኤፌሶን የሚል ቀጥተኛ አድራሻ ቢኖረውም ባይኖረውም በመልዕክቱ አስፈላጊነትና ተደራሽነት ላይ አንዳች ተጽዕኖ ይኖረዋል የሚል ግምት የለኝም።
ሐዋሪያው ጳውሎስ ተደራሲያኑን ቅዱሳን ብሎ ነው የሚጠራቸው። ቅዱስ መባል እኛ የሰራነው ገድል ተመዝኖ የሚሰጠን የማዕረግ ደረጃ ሳይሆን በክርስቶስ የቤዛነት ሥራ አምነው በመንፈሱ ታትመው በእውነተኛ ጎዳና ላይ በፀጋው እየተጓዙ የጌታቸውን መመለስ ለሚናፍቁ ሁሉ የተቸረ ስምና የማንነት መገለጫ ሥም መሆኑ ሊታወቅ ይገባል።
በመጨረሻም ለእነዚህ ቅዱሳን ፀጋና ሰላም ይብዛላችሁ ካለ በኋላ የደብዳቤው ማዕከላዊ እውነት ወደ ሆነው በሰማያዊ ስፍራ የተባረክንበትን መንፈሳዊ በረከት በመግለጽ ይቀጥላል።
መንፈሳዊ በረከት ሁሉ ስንል እግዚአብሔር አብ በልጁ ሞት በኩል ለአማኞች ሁሉ የሰጠውን የቤዛነት ሥራ የሚያጠቃልል ንግግር ነው። ሐዋርያው በሚቀጥሉት ቁጥሮችና ምዕራፎች ላይ በድነቱ ፕሮግራም ውስጥ የሥላሴን ድርሻ በሚገባ ይተርካል።
እግዚአብሔር አብ የድነት እቅድ ጠንሳሽ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ የእቅዱ ፈጻሚ፣ መንፈስ ቅዱስ የድነቱ ሥራ በአማኞች ሕይወት ውስጥ በማተም የበረከቱ ተካፋዮች እያደረጉን እንዳለ መገንዘብ ይቻላል።
ጌታች ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ካልመጣ በሚቀጥሉት ቀናት ይህ በረከት እንዴት በዝርዝር እንደ ተገለፀ፤ እንዲሁም በሕይወት እስካለን ድረስ ይህንን በረከት እንዴት በምድር ላይ መግለጽ እንደሚገባን እናያለን።
ዛሬ የማሰላስለው የቃሉ እውነት፦ በመንፈሳዊ በረከት ሁሉ የተባረኩ ሰው ነኝ!
የዛሬው ፀሎቴ፦ "እግዚአብሔር ሆይ በልጅህ በክርስቶስ በኩል በሰማያዊው ስፍራ እኔን የባረክበትን መንፈሳዊ በረከት መረዳት እንድችል አእምሮዬን ክፈትልኝ"
ነገ እስከምንገናኝ ደህና ሁኑ!!
ባይሣ ገመቹ
ሰኔ 10, 2014
ⒶⓇⓉⒾⓄⓈ
ⒶⓇⓉⒾⓄⓈ
ይ ላ ሉን
@artios_media
@artios_media
@artios_media
23 views23:34