2022-08-27 07:07:36
.
Shaday DEVOTION ⒺⓅⒽⒾⓈⒾⒶⓃⓈ
(
ቀን #17)
ጸጋ ተሰጥቶናል።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።
የኤፌሶ 4:7-16
"ነገር ግን ክርስቶስ በወሰነው መጠን ለእያንዳንዳችን ጸጋ ተሰጥቶናል። ስለዚህም እንዲህ ይላል፤ “ወደ ላይ በወጣ ጊዜ፣ ምርኮ ማረከ፤ ለሰዎችም ስጦታን ሰጠ።” ታዲያ፣ “ወደ ላይ ወጣ” ማለት ደግሞ ወደ ምድር ታችኛው ክፍል ወረደ ማለት ካልሆነ በቀር ምን ማለት ነው? ወደ ታች የወረደውም፣ መላውን ፍጥረተ ዓለም ይሞላ ዘንድ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው እርሱ ራሱ ነው። አንዳንዶቹ ሐዋርያት፣ አንዳንዶቹ ነቢያት፣ አንዳንዶቹም ወንጌል ሰባኪዎች፣ ሌሎቹ ደግሞ እረኞችና አስተማሪዎች ይሆኑ ዘንድ የሰጠ እርሱ ነው፤ ይኸውም የክርስቶስ አካል ይገነባ ዘንድ፣ ቅዱሳንን ለአገልግሎት ሥራ ለማዘጋጀት ሲሆን፣ ይህም የሚሆነው፣ ሁላችንም የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ ወደሚገኘው አንድነት በመምጣትና ሙሉ ሰው በመሆን፣ በክርስቶስ ወዳለው ፍጹምነት ደረጃ እስከምንደርስ ነው። ከእንግዲህ በማዕበል ወደ ፊትና ወደ ኋላ እየተነዳን፣ በልዩ ልዩ ዐይነት የትምህርት ነፋስ፣ በሰዎችም ረቂቅ ተንኰልና ማታለል ወዲያና ወዲህ እየተንገዋለልን ሕፃናት አንሆንም። ይልቁንም እውነትን በፍቅር እየተናገርን፣ ራስ ወደ ሆነው ወደ እርሱ በነገር ሁሉ እናድጋለን፤ እርሱም ክርስቶስ ነው፤ ከእርሱም የተነሣ፣ አካል ሁሉ በሚያገናኘው ጅማት እየተያያዘና እየተጋጠመ፣ እያንዳንዱ ክፍል የራሱን ሥራ እያከናወነ በፍቅር ያድጋል፤ ራሱንም ያንጻል።"
።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።
ማንኛውም ሰው ሲወለድ ከአንዳች ልዩ ተሰጥኦ ጋር እንደሚወለድ፤ እግዚአብሔር በክርስቶስ ኢየሱስ አምኖ ዳግም ለተወለደ ሰው ቢያንስ አንድ የጸጋ ስጦታን ሰጥቷል ። ይህም የጸጋው ባለቤት የሆነው፤ ክርስቶስ በወሰነው መጠን እንጂ በእኛ ፍላጎት ልክ አለመሆኑንና ስጦታው ለቤተክርስቲያን እንደተሰጠ ሐዋርያው ጳውሎስ ያስረዳናል።
ይህ ክፍል ስለ ስጦታዎች ከሚናገሩ አራቱ የአዲስ ኪዳን ምንባባት መካከል አንዱ ሲሆን የተጠቀሱትም ስጦታዎች፦ ሐዋርያት፣ ነቢያት፣ ወንጌል ሰባኪዎች፣ አስተማሪዎች እና መጋቢዎች ናቸው።
ሐዋርያት፦ የቃሉ ትርጉም "የተላከ" ማለት ሲሆን የአገልግሎቱ ዓላማ የትንሣኤው ምስክር መሆን እና የቤተክርስቲያንን መሠረት መጣል ነበር (ሐዋ 1:15-22 ፤ ኤፌ 2:20)። ለዚህም በአካለ ስጋ ከሞት የተነሳውን ኢየሱስን ማየት የግድ ነበር (1ቆሮ 9:1-2)።
ነቢያት፦ የትንቢት ዓላማ እና ትኩረት የእግዚአብሔርን ቃልና ፈቃድ በመግለፅ (
በማስተማር)፣ እግዚአብሔርን በመታዘዝ የሚጓዙትን ሰዎች በማበረታታት (
በማጽናናት)፣ የተበላሸ የሕይወት ዘይቤን እየገሰጹ ሰዎችን ወደ ንስሐ በመጥራት (
በማስጠንቀቅ) እና ወደፊት ሊሆን ያለውን በማሳወቅ (
በመተንበይ) የጽድቅ እና የቅድስና ኑሮን ማበረታታት ሲሆን ነቢያትም ለዚህ ዓላማ የተለዩ አገልጋዮች ናቸው።
ወንጌል ሰባኪዎች፦ ሁሉም አማኝ የኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ቢሆንም፣ ወንጌላውያን እግዚአብሔር ለወንጌል ስራ የለያቸው በየሄዱበት ያላመኑትን እየማረኩ ወደ መንግሥቱ የሚያመጡ ሃያላን ናቸው።
አስተማሪዎች እና መጋቢዎች፦ እነዚህ ሁለቱ የእረኝነት አገልግሎት ሀላፊነት ሲሆኑ፤ ዓላማቸው ተማርከው የመጡትን እየመገቡ፣ እየተንከባከቡ እና እያስተማሩ ለመንግሥቱ ማጽናት እና እውነተኛ ደቀመዛሙርት እንዲሆኑ ማሰልጠን ነው።
"በዚህ ዘመን ሐዋርያት እና ነቢያት አሉ?" የሚለው ጥያቄ ብዙ ዘመናት የክርክር ርዕስ የሆነ የነገረ-መለኮት ጥያቄ ነው። የዚህ ጽሁፍ ዓላማ ይህንን ጥያቄ መመለስ ባይሆንም ከዚሁ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ግን ወንጌላውያን አማኞች ለድርድር የማናቀርበውን ሁለት ነገር እናስታውስ፦
አንደኛው የትኛውም አገልጋይ፣ "ነቢይ ነኝ ባይ" ወይም "ሐዋርያ ነኝ ባይ" ልክ የብሉይ ኪዳን ነቢያት እንዲሁም በአዲስ ኪዳን አስራ ሁለቱ የበጉ ሐዋርያት እና ሐዋርያው ጳውሎስ የተቀዳጁትን አይነት "ሥልጣን" እንደሌለው ወይም እንደ መጽሐፍ ቅዱስ የሥልጣን ምንጭ አለመሆኑን ሲሆን፤ ሁለተኛው በዚህም ዘመን እግዚአብሔር ሰዎችን (Missionary) በልዩ ሁኔታ አስታጥቆ ለወንጌል እንደሚለይ እና እነርሱም ወንጌልን ወዳልደረሰበት ሁሉ በመንፈስ ቅዱስ ሀይል ይዘው እንደሚገቡ ነው።
ዋናው ቁምነገር ግን እግዚአብሔር ስጦታዎችን በመንፈሱ አማካይነት በነፃ የሰጠን አካሉ እንዲገነባ፣ ቅዱሳን ክርስቶስን በሚያከብር እና አማኝን በሚጠቅም መንገድ እንድናገለግል፣ ልጁን በማወቅ እና በማመን ወደሚገኘው አንድነት እንድንመጣ፣ ፍጹም ጌታን መስሎ በመኖር በሳል ሰዎች እንድንሆን ነው።
ዛሬ የማሰላስለው የቃሉ እውነት፦ "ክርስቶስ በወሰነው መጠን ለእያንዳንዳችን ጸጋ ተሰጥቶናል"
የዛሬው ፀሎት፦ ጌታችን ሆይ በትምህርት ንፋስ እንዲሁም በሰዎች ረቂቅ ተንኮል እንዳንጠፋ ይልቁንም በነገር ሁሉ ወደ አንተ እንድናድግ ስለሰጠኸን የጸጋ ስጦታ ስምህ ይባረክ!
ነገ እስከምንገናኝ ደህና ሁኑ!!
@Godshaday
467 views04:07