2022-05-07 13:16:02
ቅዱሳት ሥዕላት (Icons) በመጀመሪያዎቹ የክርስትና ክ/ዘመናት [100-400 ክ/ዘመን]
[ክፍል-2]
በጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት ሥዕላትን የመጠቀም እና የማክበር ነገር እንዳልነበር የፕሮቴስታንት ጸሐፊያን ይናገራሉ። ሀንስ ቤልቲንግ የተባለ አንድ የተሃድሶ አቀንቃኝ "በመጀመሪያ የክርስትና ሃይማኖት ሥዕላትን ሙሉ ለሙሉ እንደማይቀበል፣ በተለይም ሥዕላትን ማክበር የተከለከለ እንደሆነ ሁሌም አዕምሮአችን ውስጥ መቀመጥ አለበት" በማለት ይናገራል። [1] ለዚህም በዋናነት ሁለት ምክንያቶችን ይጠቅሳሉ። የመጀመሪያው አይሁድ ፀረ-ሥዕል (Icnophobic) ናቸው የሚል መነሻን የሚያስቀምጥ ነው።[2] ሙግታቸውን በአመክንዮ ስንደረድረው እንዲህ ይቀመጣል።
Premise 1: የሙሴ ሕግ የተሰጠው ለአይሁድ ነው። የሙሴ ሕግ ሥዕላትን እንዳንጠቀም ይከለክላል።
Premise 2: አይሁድ በሙሴ በኩል በተሰጠው ሕግ መሠረት ሥዕላትን አይቀበሉም።.
Premise 3: አብዛኛዎቹ የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ከአይሁድ ወደ ክርስትና የመጡ ነበሩ።
መደምደሚያ (Conclusion): በመጀመሪያዋ ቤተ ክርስቲያን ሥዕል ተቀባይነት አልነበረውም።
ይህ የፕሮቴስታንት ጸሐፊያን ሙግት በመጽሐፍ ቅዱስ፣ በታሪክ እንዲሁም በሥነ-ቁፋሮ ግኝቶች ( archeological Findings) ሲመዘን ውድቅ ነው። በተለይ ከ 20ኛው ክ/ዘመን በኋላ የተገኙ የሥነ-ቁፋሮ ግኝቶች ምስክር ከመሆናቸው በፊት ከላይ የተጠቀሰው የፕሮቴስታንት ጸሐፊያን ሙግት የበረታ ነበር። "የተቀረጸ ምስል ለአንተ አታድርግ" (ዘጸ20:4) የሚለው ሕግን አይሁዳውያን በምን መልኩ ተጠቀሙበት? በመጀመሪያዋ ቤተ ክርስቲያን ዘመን የነበሩ አይሁድ የሥዕል አቀባበል ምን ይመስል ነበር? የሚለው የትኩረት ነጥብ ሆነው ተዳሰዋል።
"የተቀረጸ ምስል ለአንተ አታድርግ" የሚለው ቃል ለእስራኤላውያን የተሰጠው በተደጋጋሚ በጣዖት አምልኮ ይወድቁ ስለ ነበር ነው። እግዚአብሔር በተለያዩ ጊዜዎች ሥዕላት እንዲሳሉ እና እንዲቀረጹ ማዘዙ ይህ ሕግ በቀጥታ የሚመለከተው የአሕዛብን ጣዖታት እንደሆነ የሚያስረዳ ነው። ሥዕለ ኪሩብ በታቦቱ ላይ (ዘጸ25:18)፣ በድንኳኑ መጋረጃ ላይ (ዘጸ26:1)፣ በቤተ መቅደስ ውስጥ (1ነገ6:23)፣ በቤተ መቅደስ ግርግዳዎች ላይ (1ነገ6:29) እንዲሰራ እግዚአብሔር አዟል። እዚህ ላይ የፕሮቴስታንት ጸሐፊያን ሁለት አማራጭ አላቸው። የመጀመሪያው ሥዕለ ኪሩብ ጣዖት ነው ብሎ መደምደም ሲሆን ሁለተኛው አማራጭ ደግሞ በጣዖት እና በሥዕላት መካከል ልዩነት እንዳለ መረዳት ነው። ሥዕለ ኪሩብ በእግዚአብሔር ትዕዘዝ የተሰራ እንደመሆኑ የመጀመሪያው አማራጭ የሚያስኬድ አይደለም። በሰሎሞን ቤተ መቅደስ ውስጥ የኪሩቤል፣ የዘንባባ ዛፍ እና የፈነዳ አበባ ሥዕል ነበር። (1ነገ6:21-29) እሥራኤላውያን ከደዌያቸው የዳኑበት የነሐሱ እባብ የተቀረጸ ምስል ነበር። (ዘኁ27:8-9) ነቢዩ ሕዝቅኤል በጡብ ላይ የእየሩሳሌምን ከተማ እንዲሥል ተነገሮት ነበር። (ሕዝ4:1) የቃል ኪዳኑ ታቦት እራሱ የተቀረጸ ምስል ነው!
የተቀረጸ ምሥል ለአንተ አታድርግ ከሚለው ሕግ ጋር ከግብጽ ምድር ያወጣኹህ አምላክህ እግዚአብሔር እኔ ነኝ፣ በላይ በሰማይ ፣ በምድርም በታች፣ በምድርም በታች በውኃ ካሉት የማናቸውም ምሣሌ ለአንተ አታድርግ የሚል ቃል አብሮ ተቀምጧል። በዚህ ቦታ ላይ በመሠረታዊነት ሦስት ቦታዎችን (በሰማይ፣ በምድር፣ በውኃ) የጠቀሰ ሲሆን አብሮ ግብጽንም ያነሳታል። በግብጽ ምድር በነበረው የጣዖት አምልኮ በሰማይ ካሉት Horus (god of the Sky) ፣ Ra ( god of sun) ፣ Khonsu (god of the moon) ፣ Nut (Sky goddess) የሚባሉ ጣዖታት ይመለኩ ነበር። በምድር ካሉት ደግሞ Geb (god of earth) ፣ Aker (god of earth) ይመለኩ ነበር። ከምድር በታች በውኃ ካሉት Bairthy (goddess of the water) ፣ Osiris (god of the water) የሚባሉ ጣዖታት ይመለኩ ነበር። [3] ይህ የግብጾችን የጣዖት አምልኮ አጠቃላይ ሁኔታን የሚገልጽ ነው። ለእስራኤላውያን የተሰጠው የሙሴ ሕግ በግብጽ ምድር የተመለከቷቸውን ጣዖታት እንዳይሰሩ የሚከለክል እንደነበር መገንዘብ ቀላል ነው። ይሄንን እግዚአብሔር በነቢዩ ሕዝቅኤል አድሮ በተናገረው ቃል ማረጋገጥ የሚቻል ነው።
"በዚያ ቀን ከግብጽ ምድር ወዳዘጋጀሁላቸው፥ ወተትና ማር ወደምታፈስሰው፥ የምድርም ሁሉ ጌጥ ወደምትሆን ምድር አወጣቸው ዘንድ ማልሁላቸው፤
እኔም። ከእናንተ እያንዳንዱ የዓይኑን ርኵሰት ይጣል፥ በግብጽም ጣዖታት አትርከሱ፤ እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ነኝ አልኋቸው።" (ሕዝ20:6-7)
በአጠቃላይ ዘጸ20:4 በቀጥታ የግብጽ ጣዖታትን የሚመለከት ቃል እንደሆነ ከላይ በተጠቀሰው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል መረዳት የሚቻል ነው። አይሁድ በዘጸ20:4 ምክንያት ሙሉ ለሙሉ ሥዕላትን ሊቀበሉ የማይችሉ ናቸው የሚለው ሙግትም እውነት ያልሆነ ሀሰት ነው። ሌላኛው የትኩረት ነጥባችን በመጀመሪያዎቹ የክርስትና ክ/ዘመናት አይሁድ ለሥዕላት የነበራቸው አቀባበል እንዴት ነበር? የሚለው ይሆናል።
በመጀመሪያዎች ክ/ዘመናት በአይሁድ እና በክርስቲያኖች ዘንድ ስለ ነበረው ሥርአተ አምልኮ ከሚታዩ ማስረጃዎች መካከል የጥንታዊቷ ዱራ ኢሮፖስ (Dura Europos) ግኝት ታዋቂው ነው። Dura Europos የአይሁድም የክርስቲያኖች ከተማ የነበረች ሲሆን በአሁኗ ሶሪያ ድንበር አካባቢ የምትገኝ ናት። በዚህ ከተማ የተገኙት ማስረጃዎች የፕሮቴስታንት ጸሐፊያንን ብዕር ማጠፍ የቻለ ነው። በ 233 A.D የነበረችው ጥንታዊት ከተማ የአይሁድ ማኅበር (Synagogue) ሕይወትን በግልጽ ታሳያለች። በዚች ጥንታዊት ከተማ ውስጥ የአይሁድ ማኅበር የነቢያት (የሙሴ፣ የዳዊት፣ የሕዝቅኤል፣ የኤልያስ) ሥዕል እንደነበራቸው የተገኙት ማስረጃዎች ያሳያሉ። የይስሐቅ መሥዋዕት፣ የአብርሃም ታሪክ የሚያሳዩ ሥዕላትም በዚው ሥፍራ ይገኛሉ። [4] ይህ ብቻ ሳይሆን የተለያዩ አይሁድ ማኅበራት (Synagogues) ሥዕላትን ይቀበሉ እንደነበር የሚያሳዩ የሥነ-ቁፋሮ ግኝቶች አሁንም ድረስ በመውጣት ላይ መሆናቸውን ማስረጃዎች ያሳያሉ። [5] አይሁድ ሙሉ ለሙሉ ሥዕላትን የማይቀበሉ (Aniconic) ናቸው የሚለው ሙግት ሀሰት መሆኑን እነዚህ ግኝቶች መስክረዋል።
በክፍል-3 ሁለተኛውንና የፕሮቴስታንት ጸሐፊያን የመቃወሚያ ሙግትን በሚመለከት ጽሑፍ ይዤ የምመለስ ይሆናል!
[1] Hans Belting, Likeness and Presence, 1990
[2] John B.Carpenter, Icons and the Eastern Orthodox Claim to Continuity with the Early Church p. 107-108
[3]Orthodoxidation, Icons or Idols? A Faulty Understanding of Exodus 20, 2021
[4] Fine, Steven, Art and Judaism in the Greco-Roman World: toward a New Jewish Archaeology, Cambridge Ch.11
[5] Urman, Dan, and Paul, Ancient Synagogues Historical Analysis and Archaeological Dicovery, Leid, 1998
ስብሐት ለእግዚአብሔር!
784 views10:16