2022-08-30 08:33:39
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ነሐሴ ሃያ አራት በዚህች ታላቅ ዕለት የከበረ ሐዲስ ሐዋርያ የትሩፋትም መምህር የሆነ አባታችን ተክለ ሃይማኖት አረፈ::
የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም ጸጋ ዘአብ የእናቱ ስም እግዚእ ኀርያ ነው::
እሊህም ቅዱሱን ለኢትዮጵያ የሃይማኖት ብርሃንን ላበሩ ካህናት ከወገኖቻቸው የሆኑ ናቸው::
እግዚእ ኀረያም መካን ስለሆነች ልጅን ይሰጣቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እያዘኑ ሲጸልዩ ኖረ::
በዚህም ነገር እያሉ የዳሞት ገዥ ሞተለሚን ሰይጣን አነሣሣው የሸዋን አውራጃዎች እስከ ጅማ እስከ ገዛ ድረስ::
የየሀገሩ መኳንንቶችም በየተራቸው ሚስቶቻቸውን ይሰጡታል:: ከማረከውም ደምግባት ያላቸውን ሴቶች ያገኘ እንደሆነ ቁባቶቹ ያደርጋቸዋል::
በዚያ ወራት ወደ ጽላልሽ ደርሶ ብዙ ክርስቲያኖችን ገደለ ከእርሳቸውም የሚበዙትን ማረከ ጸጋ ዘአብም ከግድያ ፍርሃት የተነሳ ሸሸ::
አንድ ወታደርም ተከተለው እርሱም ወደ ባሕር ተወርውሮ ገባ በእግዚአብሔርም ፈቃድ በባሕሩ ውስጥ ተሸሸገ::
ሚስቱን እግዚእ ኀረያንም ወታደሮቹ ማረኳት ወደ ሞተለሚም አደረሷት በአያትም ጊዜ ውበቷንና ላህይዋን አደነቀ::
በልቡም እጅግ ደስ ብሎት ብዙ ሽልማትን ጌጥን ሰጥቷት በሽልማትና በጌጥ ሁሉ ሸለማት አስጌጣትም የጋብቻ ሥርዓትንም ማዘጋጀት ጀመረ:: ለሠርጉም እንዲሰበሰቡ ወደ መኳንቶቹ ሁሉ ላከ::
እግዚእ ኀርያም ይህን በሰማች ጊዜ ከአረሚ ጋር አንድ ከመሆን ያድናት ዘንድ በብዙ ልቅሶ ወደ እግዚአብሔር ጸሎትን አደረገች::
ያን ጊዜ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በብርሃናዊ ክንፉ ተሸክሞ ከዳሞት አገር ወደ ምድረ ዞረሬ አድርሶ ወዲያውኑ ወደ ቤተ መቅደስ አስገብቶ በሴቶች መቆሚያ አቆማት::
ባሏ ጸጋ ዘአብም ከማዕጠንት ጋራ በወጣ ጊዜ እንደተሸለመች ቁማ አያት አድንቆ በልቡ ይቺ ሴት ምንድ ናት ወደዚህስ ማን አመጣት አለ::
የማዕጠንቱንም ሥራ ጨርሶ ወጣ በጠየቃትና በመረመራት ጊዜ እርሷ ሚስቱ እግዚእ ኀርያ እንደሆነች አገኛት:: እርሷም ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው እግዚአብሔር ያደረገላትን ነገረችው::
ከዚህም በኃላ የእግዚአብሔር መልአክ በአንዲት ሌሊት ተገለጠላቸው::
የዜናው መሰማት በዓለም ሁሉ የሚደርስ የተባረከ ልጅ ይወልዱ ዘንድ እንዳላቸው ነገራቸው አበሠራቸው::
ከጥቂት ቀኖች በኋላ ይህ ቅዱስ ተፀንሶ በታኅሣሥ ወር በሃያ አራት ተወለደ::
በጸጋ ዘአብና በእግዚእ ኀረያ በቤታቸው ታላቅ ደስታ ሆነ ከዘመዶቻቸው ጋራ ደስ አላቸው:: ለክርስትና ጥምቀት ባስገቡት ጊዜ ፍስሐ ጽዮን ብለው ሰየሙት::
ሕፃኑም አደገ ድንቅ ተአምራትንም እያደረገ ዕውቀትንና ኃይልንም ተመልቶ በመንፈስ ቅዱስ ጸና::
ከዚህም በኋላ ዲቁና ይሾም ዘንድ አባ ጌርሎስ ወደ ተባለ ጳጳስ ወሰዱት ::
በዚያ ዘመን በዛጔ መንግሥት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ አባ ቢንያሚ ነበር:: ወደ ጳጳሱ ባደረሱት ጊዜ ይህ ልጅ የተመረጠ ዕቃ ይሆናል ብሎ ትንቢት ተናገረለት::
የዲቁና ሹመትን ተቀብሎ ወደ ሀገሩ ተመለሰ ጎልማሳም በሆነ ጊዜ አራዊትን ሊያድን ወደ ዱር ሔደ::
ቀትር ሲሆንም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መልኩ በሚያምር ጎልማሳ አምሳሎ በቅዱስ ሚካኤል ክንፍ ላይ ተገለጠለትና እንዲህ አለው::
ወዳጄ አትፍራ እንግዲህስ የኃጢአተኞችን ነፍስ ወደ ሕይወት የምታጠምድ ትሆናለህ እንጂ አራዊትን የምታድን አትሆንም ስምህም ተክለ ሃይማኖት ይሁን::
እንደ ኤርሚያስና አጥማቂው ዮሐንስ እኔ ከእናትህ ማኅፀን መርጬ አክብሬሃለውና::
እንሆ በሽተኞችን ትፈውስ ዘንድ ሙታንንም ታሥነሣ ዘንድ ሥልጣንን ሰጠሁህ ርኵሳን አጋንንትንም ከሁሉ ቦታ ታሳድዳቸዋለህ::
ወደ ቤቱም በተመለሰ ጊዜ ገንዘቡን ሁሉ ለድሆችና ለምስኪኖች በተነ:: ዓለሙንም ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጠፋ ለሰው ምን ይጠቅመዋል እያለ ቤቱን እንደተከፈተ ትቶ ምርጒዙን ይዞ በሌሊት ወጣ::
ከዚህም በኋላ ወደ ጳጳስ ሒዶ የቅስና ሹመት ተቀብሎ ለሸዋ አገር ሁሉ ወንጌልን መስበክ ጀመረ::
ዐሥራ ሁለት ሽህ ሦስት መቶ ነፍስ ያህል አጠመቀ:: ለጣዖት የሚሰዉበትን ሁሉ ሻረ:: በውስጡ የሚኖሩ አጋንንትን እስኪሸሹ ድረስ ዐፀዶቻቸውን ሁሉ ቆረጠ::
ሁለተኛም ወደ ዳሞት ምድር ሒዶ ብዙ ሟርተኞችንና አስማተኞችን ጠንቋዮችን አሳመነ::
ከሀዲ ሞተለሚም ብዙ ወራት ተቃወመው:: በጉማሬ ማጥመጃ ውስጥ በመጨመር ብዙ ጊዜ ወደ ገደል ወረወረው::
እርሱ ግን በደኅና ይመላለሳል ደግሞ ሊወጋው ጦር ወረወረ ጦሩም ተመልሶ እጁን ወግቶ ተጠመጠመበት በተሰቃየም ጊዜ አባታችንን ለመነው እርሱም የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አሳምኖ አዳነው የተጠመጠመበትን ጦርም ፈታለት ቀናውን መንገድ የሚያጣምሙ ሟርተኞችንም አጠፋቸው::
ከዚህ በኋላ በክብር ባለቤት ጌታችን ስም ያደረገውን ድንቅ ተአምራቱን አይተው የአገር ሰዎች ሁሉም ከንጉሣቸው ጋራ አመኑ::
የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው:: ቤተ ክርስቲያንም ሠርቶላቸው የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት አስተማራቸው:: በቀናች ሃይማኖትም አጸናቸው ከዚህም ሁሉ ጋራ በጾም በጸሎት በስግደት ሁል ጊዜ ያለ ማቋረጥ ተጠምዶ ይጋደል ነበር::
ዜናውንም ሰምተው ወደርሱ የሚመጡትን የነፍሳቸውን ድኅነት ያስተምራቸዋል የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችን ኢየሱስ በማመንም ያጸናቸዋል::
ከዚህም በኋላ በኤልያስ ሠረገላ ተቀምጦ ወደ አምሐራ ሀገር ሔደ:: በገድል ተጸምዶ ወደ ሚኖር መነኰስ ወደ አባ በጸሎተ ሚካኤል በአንዲት ቀን ደርሶ በዚያ እንደ ባሪያ ሲያገለግል ኖረ::
በአንድነት የሚኖሩ መነኮሳትንም ያገለግላቸው ነበር የሞተውንም እስከማንሳት ድረስ ከደዌያቸው ይፈውሳቸው ነበር::
በዚያም ዐሥራ ሁለት ዓመት ከሆነው በኋላ ሐይቅ በሚባል ቦታ ወደ ሚኖረው ወደ ኢየሱስ ሞዓ የእግዚአብሔር መልአክ እንዳዘዘው ሔደ:: ከእርሱም የምንኩስና ልብስ ቀሚስና ቅናትን ተቀበለ::
ሁለተኛም ወደ ኢየሩሳሌም ሔዶ ከከበሩ ቦታዎችና ከሊቀ ጳጳሳቱ ቡራኬን ተቀበለ::
ከዚያም ወደ ሸዋ ምድር ተመልሶ የአባቱ ወንድም ልጅ የሆነ አባ ዜና ማርቆስን አገኘው በወግዳ በረሀም በአንድነት ኖሩ::
ከዚያም ግራርያ ወደሚባል አገር ሒዶ በኮረብታ መካከል ዋሻ አዘጋጅቶ ተቀመጠ:: በቀንም በሌሊትም ከዚያ አይወጣም ነበር ከጥቂት ቅጠልም በቀር እህልን አይቀምስም መጠጡም ጥቂት ውኃ ነው::
ብዙ ወንዶችና ሴቶች ወደርሱ መጥተው መነኮሳቶች ሆኑ በአንድ ቤት ውስጥ በአንድ መኝታ ላይ ተኝተው ያድራሉ እርስ በእርሳቸውም አይተዋወቁም::
እነርሱም እንደ ሕፃናት ናቸው: በጸሎትና በቅዳሴ ጊዜም በአንድነት ይቆማሉ በዘመኑ ሰይጣን ስለ ታሠረ ወንዱ ሴቷን ሴት እንደሆነች አያውቅም እንዲሁም ሴቷ ወንዱን ወንድ እንደሆነ አታውቅም::
ከዚህ በኋላ መጠጊያ ሠርቶ በፊቱ በኋላም በቀኙ በግራው የተሳሉ ፍላጻዎችን ተከለ ይህንንም ማድረጉ በመደገፍና በመተኛት እንዳያርፍ ነው በዚያም እግሩ ከቅልጥሙ እስቲሰበር ሰባት ዓመት ቆመ::
በዚያም ወራት ምንም የዕንጨት ፍሬ ወይም ቅጠል ሳይቀምስ ውኃም ሳይጠጣው ኖረ::
ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደርሱ መጣ ከእርሱም ጋራ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ደግሞ የከበሩ ነቢያትና ሐዋርያት ሁሉም ሰማዕታትና ጻድቃን የጳጳሳት አለቆች የመላእክት አለቆችም ከሠራዊቶቻቸው ጋራ አሉ::
መድኃኒታችንም እንዲህ አለው ወዳጄ ሆይ አንተ በመከራዬ መሰልከኝ እኔም በመንግሥቴ
522 views05:33