2022-07-11 11:58:41
ደራሲ ፀሐይ መላኩ የሥነ-ጽሑፍ ዝንባሌዋን በተግባር የሞከረችው የሁለተኛ ደረጃ ተማሪ ሆና፣ በሥነ-ጽሑፍ ክበብ ውስጥ ተሳታፊ በነበረችበት ወቅት ነው። በዚያን ጊዜ በምታቀርባቸው የግጥምና ዝርው ጽሑፎች በአስተማሪዎቿ ይሰጣት የነበረው ነጥብና ማበረታታት፣ ለሥነ-ጽሑፍ ያላት ፍቅርና ጥረት ጠንካራ እንዲሆን አድርጓታል።
የቤተ-ክህነት ትምህርት የነበራቸው አባቷ በልጅነቷ መንፈሳዊ የግዕዝና የአማርኛ መጻሕፍትን ከዘመናዊው ትምህርት ጎን ለጎን እንድታነብ ሳያሰልሱ ያበረታቷት ነበር። በዚህም ምክንያት የማንበብ ልምዷ ከዕለት ዕለት ከፍ እንዲልና የኪነ-ጥበብ ዝንባሌዋ እንዲጎለብት በማድረግ በቀጥታ ወደ ሥነ-ጽሑፍ መስመር እንደመራት ታምናለች።
ግንቦት 16 ቀን 1944 ዓ.ም.፣ ከወይዘሮ አዛለች ይገባሃል ፅጌ እና ከአቶ መላኩ ጎላ፣ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ነው የተወለደችው። ፊደል የቆጠረችው በቄስ ትምህርት ቤት ነው።
ፀሐይ መላኩ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቷን አዲስ አበባ በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት፣ መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃን ደብረ ታቦር በአፄ ቴዎድሮስ ትምህርት ቤት፣ ሁለተኛ ደረጃን ጎንደር በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የሙያ ትምህርት ቤት አጠናቅቃለች።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመምህርነት ኮርስ ተከታትላለች። ከዚሁ ዩኒቨርሲቲ በንግድ ሥራ ትምህርት በዲፕሎማ፣ ከዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ደግሞ በእንግሊዘኛ ቋንቋና በሥነ-ጽሑፍ በመጀመሪያ ዲግሪ ተመርቃለች።
ፀሐይ መላኩ ለአንባቢያን ያበረከተቻቸው የሥነ-ጽሑፍ ሥራዎች፦
➢ ቋሳ (ቂም) - በ1982 ዓ.ም.
➢ አንጉዝ (የማይጠፋ ጠባሳ) - በ1984 ዓ.ም.
➢ ቢስ ራሔል - በ1986 ዓ.ም.
➢ እመ ምኔት - በ2002 ዓ.ም.
➢ የንስሐ ሸንጎ - በ2004 ዓ.ም.
➢ የጴጥሮስ ዋዜማ - ታሪካዊ ልቦለድ በ2005 ዓ.ም.
➢ The Drastic Charity (የተባ ትሩፋት) - በ2002 ዓ.ም.
➢ ጀግና እንደ ቴዎድሮስ፣ ቆራጥ እንደ ጴጥሮስ (ግለ ታሪክ) - በ2007 ዓ.ም.
➢ ኮሎኔል ታደሰ ሁንዴ (የሕይወት ታሪካቸውንና ልምዳቸውን የሚተርክ)፤
ረዥም ልቦለድ ድርሰቶቿና የታሪክ ጽሑፎቿ ሲሆኑ፤
➢ የዘመን ቀለማት - የአጫጭር ልቦለዶች መድብል
➢ ዜማ ብዕር ቁጥር 1 - የግጥም መድብል
➢ ዜማ ብዕር ቁጥር 2- የአጫጭር ልቦለዶች መድብል ከሌሌች ደራሲያን ጋር በጋራ ያዘጋጀቻቸውና በመድብል የታተሙ ሥራዎቿ ናቸው።
በተጨማሪም
➢ የስሜት ትኩሳት - ክፍል 1 (የግጥም መድብል) በ2002 ዓ.ም.
➢ የስሜት ትኩሳት - ክፍል 2 (የግጥም መድብል) በ2002 ዓ.ም. ለ40 ዓመታት ያህል ካጠራቀመቻቸው ግጥሞቿ ከፊሉን የያዙ መጽሐፎቿ ናቸው።
ፀሐይ መላኩ ለህትመት ከበቁ ሥራዎቿ ሌላም በልዩ ልዩ ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ በርካታ መጣጥፎችንና የሬድዮ ድራማዎችን በመጻፍም ትታወቃለች።
━━━━━━━━━━━━
ማኅደረ ደራስያን - ቅጽ ፩
በኢትዮጵያ ደራሲያን ማኅበር
https://t.me/Ethiobooks
1.8K viewsተስፋዬ መብራቱ, 08:58