Get Mystery Box with random crypto!

“እኔ ስራ አለኝ እንጂ ሌላ ምን አለኝ” ብሎ የንቀቱን አቅጣጫ ወደ ራሱ መለሰው። አንድ የሚንቀው | ልብወለድ Ethio_Fiction

“እኔ ስራ አለኝ እንጂ ሌላ ምን አለኝ” ብሎ የንቀቱን አቅጣጫ ወደ ራሱ መለሰው። አንድ የሚንቀው ነገር ሁሌ በቅርብ ያስፈልገዋል። መጀመሪያ ተሳፋሪዋን ነበረ። ቀጥሎ ደግሞ እሷ በለቅሶ እና ለእሱ በጥቂቱ ባሳየችው አሳቢነቷ፣ እሷን አክብሮ ራሱን አርክሶ ቁጭ አለ።
“እሷ ባል አላት … እኔ ሚስት የለኝም።  እሷ ልጅ አላት…እኔ ልጅም በህይወቴ ላይ በቅርብ ርቀት አይታየኝም። ልጅነቴንም በፍጥነት አጥቻለሁኝ። ድንገት ከመሬት ተነስታ ከበረችብኝ እያለ አሰበ። ወደ ታች መውረድ ቀጠልን። መንገዱ ወደ ሁለት እንደሚሰነጠቅ ረስቷል። ሁለተኛውን ቅያስ ማንም የሚጠቀመው የለም። በታች የሚሄደውን ማንም የሚያዘወትረውን ቅያስ እንዲይዝላት ደጋግማ አስጠነቀቀችው። ቆሻሻው መንገድ ነው፡፡

የሀይላንድ ፕላስቲክ በአንድ ላይ ተከማችቶ በዚህ ቅያስ ጥጋጥግ ላይ ተከምሯል። የቆሻሻው መግፊያ ጋሪዎች ተደርድረው ክብደታቸውን ወደ ፊት ዘንበል አድርገው ቆመዋል። ቆሻሻ ገንዳ ያለበት አካባቢ የተለመደ እይታ ነው። ከቆሻሻ ገንዳው ትንሽ ፈቀቅ ብሎ የላስቲክ ቤቶች አሉ። ሁለት ሊሆኑም ብዙ ሊሆኑም ይችላሉ፡፡ ከተነሳችበት የዛ አይነት ርቀት የመጣችው ለዚህ መዳረሻ ይሆናል ብሎ ፈፅሞ አልጠረጠረም፡፡
መኪናውን ዳሩ ላይ ከላስቲኩ ቤት አጠገብ አቆመ።  እነ እሙጢ መአት ሆነው እየተሯሯጡ ወጡ። አንድ ጥርሷ የጎደላት፣ ያልጎደሉት ደግሞ ተዛንፈው የተበላሹባት፣ ትንሽ ከሌሎች በእድሜ ከፍ የምትለው ሴትዮ ልትሆን ትችላለች፤ እሙጢ፡፡ ደጋግማ በሥሟ ጠራቻትና ታቅፋ የቆየችውን ነገር ተቀበለቻት። እሙጢ በአስተቃቀፏ እንደዛ አይነት ህጻን ለመታቀፍ የመጀመሪያዋ እንዳልሆነ ግልፅ ነበር፡፡

ከበው ተቀበሏት፤ ወደ ላስቲክ ቤታቸው አጅበው አስገቧት። ከማስገባታቸው በፊት ግን የጉዞ ተመኑን ጠይቃ ለሾፌሩ ከፍላዋለች። አልቀበልም ብሎ ለመግደርደርም አልተመቸውም። የናቃት እንዳይመስል ተመኑን በልኩ ወሰደ። ቲፑን ግን እንቢ አለ።  ሊያዝንላት የጀመረው ሰው፣ በተቃራኒው አዝናለት ጨምድዳ አስጨበጠችው፡፡
የጎዳና ተዳዳሪዎቹ ቤት አጅበዋት እስኪገቡ ድረስ እንደ ሰላይ በጥንቃቄ ተከታትሎ፣ ለመሄድ ተነሳ። በእሙጢ ስም ፋንታ የእሷን የእናትየውን ቢያውቀው የበለጠ ደስ ይለው እንደነበር እያሰበ ጎዳናውን ተያያዘው፡፡

#ተፈፀመ
በድርሰቱ ላይ ያላችሁን ሃሳብና አስተያየት
በአስተያየት መስጫው ይግለፁልን

Share - @ethio_fiction

Comment -
@sam_lizu