Get Mystery Box with random crypto!

#ርዕስ:- “እነ እሙጢ ጋ እየሄድኩኝ ነው” #ደራሲ:- ሌሊሳ ግርማ #ክፍል....1   “ለዛሬ | ልብወለድ Ethio_Fiction

#ርዕስ:- “እነ እሙጢ ጋ እየሄድኩኝ ነው”
#ደራሲ:- ሌሊሳ ግርማ

#ክፍል....1

  “ለዛሬ ይበቃኛል” ብሎ ወደ ሰፈር ሊያዞር ሲል አንድ ተጨማሪ ስራ መጣ። “ራይድ ነህ አይደል?” ብሎ ተጠግቶ ጠየቀው። አመኔታ የሚጣልበት አይነት ነው። ቦርጭ እና ቅላት አለው። በተለምዶ ካለ ጥሪ ተሳፈሪ አይጭንም።
“አዎ ነኝ” ከማለቱ “ጠብቃት ትመጣለች… ልጅ ይዛለች” አለው። “ጠሪ አክባሪ” የሚባለው አይነት መሆኑ ነው። የሚሄዱትን ራሱ ሳይሄድ የሚያገናኘው። ልጅቷ መጣች። ህጻኑን ይዛ ከኋላ ወንበር ተሳፈረች። ወደ ኋላ በሚያሳየው መስታወት ሲገመግማት እንዲሁ አልወደዳትም። ወደምትፈልግበት ከደረሰች በኋላ “የምከፍለው የለኝም” ብላ አይኗን ልታፈጥ የምትችለው አይነት ትመስላለች።

ብዙውን ጊዜ መጓጓዣውን ጠርቶ የሚያሳፍረው… ጉዞው ከመጀመሩ በፊት ይከፍላል። እንደ ቅርበቱ። ለተጓዡ እንደሚሰጠው አክብሮቱ። ብዙም ትውውቅ ያላቸው አይመስልም። በጎዳና ላይ ሲያልፍ “ራይድ ጥራልኝ” ብላው ተባብሯት ሊሆን ይችላል።
 ከፍ ያለ ዋጋ ያለው ነገር በእጇ ታቅፋለች። ያመናት በታቀፈችው ህጻን ምክንያት ነው። የታቀፈችው ህጻን ከታቃፊዋ ወጣት በላይ ንጹህ ይመስላል። በነጭ መታቀፊያ ነው የተጠቀለለው። ብዙም ደስ ሳትለው ነው መኪናውን አስነስቶ ጉዞ የጀመረው።

አንድ ጊዜ ብቻ ወደ ኋላ አንገቱን አዙሮ በደንብ በአይኑ ከላይ እስከ ታች አዳርሷታል። ከሰላምታ በስተቀር ተሳፋሪን ማየት አይወድም። ዞሮ ማየት ሳያስፈልገው፣ ምን አይነት ሰው እንደተሳፈረ ያውቃል። አንዳንዶቹ ጠረናቸው ማንነታቸውን ይናገርላቸዋል። ሌሎቹ ዝምታቸው። ዝምታቸው የሆኑትን ሳይሆን ምን መስለው መቅረብ እንደሚሹ ይነግረዋል። ራሳቸውን ስለሚያከብሩ፣ መዋረድ ስለማይፈልጉ… የተጠየቁትን መክፈላቸው አይቀርም።
ከመነሳቱ በፊት መዳረሻዋን እና ስልክ ቁጥሯን ጠየቃት። ስልክ ቁጥርም የቁጥሩን ባለቤት ማንነት ለማሳየት ይጠቅማል። ተደብቆ ሰው ለመሳደብ የፈለገ ሰው፣ የሚደውልበት አይነት ቁጥር ነው። 0911 ወይንም ሁለት፣ ወይንም በአንድ ሶስት የሚጀምሩ አድራሻ ያላቸው ስልኮች ናቸው። ስልኳን ነገረችው እና ሞላው። ፈረሱ ስራውን ጀመረ።