የመዲናዋ ህንፃዎች ግራጫ ቀለም ሊቀቡ ነው በሚል የሚናፈሰው መረጃ ከዕውነት የራቀ ነው ተባለ
የአዲስ አበባ ህንፃዎች ሁሉ ግራጫ ቀለም ሊቀቡ ነው በሚል ከሰሞኑ በማህበራዊ ትስስር ገጾች የሚናፈሰው መረጃ ከዕውነት የራቀ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ዮናስ ዘውዴ አስታወቁ።
የቢሮ ኃላፊው በተለይ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጹት፤ አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብና ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የህንፃ ስታንዳርድና የውጭ ማስታወቂያ ስታንዳርድ እየተዘጋጀ ነው፡፡ ሆኖም ግን ይህን መነሻ አድርጎ በማህበራዊ ትስስር ገጾች አዲስ ከተማ ግራጫ ቀለም ልትቀባ ነው በሚል በስፋት ሲዘዋወር የታየው መረጃ የተሳሳተ ነው ብለዋል፡፡
እስካሁን ድረስ የከተማዋ ህንጻዎች ቀለም ምን አይነት ይሁን የሚለው ጉዳይ ለውይይት ቀረበ እንጂ የከተማ አስተዳደሩ በጉዳዩ ላይ ምንም አይነት ውሳኔ እንዳላሳለፈ አመልክተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይም ከዚህ ቀደም ‹‹ከተማችን ቡራቡሬ ሆና ባለቤት አልባ መስላለች›› ማለታቸውን ያስታወሱት የቢሮ ኃላፊው፤ ይህን ችግር ማንኛውም የመዲናዋ ነዋሪም ሊታዘብ ይችላል። የከተማ አስተዳደሩም ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቷል ብለዋል።
ችግሩን ለመፍታት የውጭ ማስታወቂያውና የከተ ማዋ ቀለም ሁኔታ የሚመራበት ስታንዳርድ ዝግጅት ተደረገ እንጂ ውሳኔ ላይ አለመድረሱን ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት