Get Mystery Box with random crypto!

ልብ ብለው ያንቡት በኛ ምክንያት ብዙዎቸ በተለያየ ምክንያት ተሰናክለዋል + የአንድ ሰው ውሎና | ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቶች

ልብ ብለው ያንቡት በኛ ምክንያት ብዙዎቸ በተለያየ ምክንያት ተሰናክለዋል

+ የአንድ ሰው ውሎና አመሻሽ +

ይህ እስካሁን ምንጩን ያላገኘሁት አንድ ወንድሜ የላከልኝ በፈረንጅ አፍ የተጻፈ የቆየ የአንድ ሰው ገጠመኝ ነው :-

አንድ ወንድም ስልኩን ድምፅ አልባ ማድረግ ረስቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ስብከት ይማራል:: በዚህ መካከል ስልኩ ይጮኃል::

ሰባኪው ስብከቱን አቁሞ በዓይኖቹ ተቆጣው:: ከስብከቱ በኋላ ምእመናን ስብከቱን በመረበሹ ወቀሱት:: አንዳንዶቹም እያዩት ራሳቸውን በትዝብት ነቀነቁ:: ከሚስቱ ጋር ወደ ቤታቸው ሲሔዱም ሚስቱ ስለ ቸልተኝነቱ ምክር መሥጠትዋን ቀጠለች::
እፍረት መሸማቀቅና ውርደት ዘልቆ እንደተሰማው በፊቱ ላይ ይታይ ነበር:: ከዚያች ሰንበት በኋላ እግሩን ወደ ቤተ ክርስቲያን አንሥቶ አያውቅም::

ውስጡ የተረበሸው ይህ ሰው ያንኑ ምሽት ወደ መጠጥ ቤት አመራ:: አእምሮው እንደታወከ ነበር::

ቁጭ ባለበት ድንገት የሚጠጣበት ጠርሙስ ወድቆ ተሰበረና መጠጡም በዙሪያ ተረጨ:: ፍንጣሪው የነካቸው ሰዎች ወደ እሱ መጠጋት ጀመሩ:: ሊጮኹበትና በጥፊ ሊሉት እንደሆነ ታውቆት ቀድሞ ዓይኖቹን ጨፈነ::

ሰዎቹ ግን በተሰበረው ጠርሙስ ስብርባሪ ተጎድቶ እንደሆነ ተጨንቀው ጠየቁት::

አስተናጋጁ መጥቶ የፈሰሰበትን እንዲያደርቅ ማበሻ ሰጠው:: የጽዳት ሠራተኛዋ መሬቱን ወለወለች::

የቤቱ ባለቤት "አይዞህ ያጋጥማል? ዕቃ የማይሰብር ማን አለና?" አለችውና ሌላ መጠጥ አስመጣችለት::
ከዚያች ቀን ጀምሮ ከዚያ መጠጥ ቤት ቀርቶ አያውቅም::

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስልክን ክፍት ማድረግና ሥርዓተ አምልኮ መረበሽ መቅደስ ውስጥ ጫማ አድርጎ የመግባት ያህል ስኅተት ነው:: እንኩዋን ቤተ ክርስቲያን ኤምባሲ እንኩዋን ስልክህን ውጪ አስቀምጠህ ትገባለህ:: ሰውዬው ላጠፋው ጥፋት ግን በፍቅር የሚያናግረው ሰው በማጣቱ ከነ ስልኩ ሊጠፋ ወሰነ::

ቤተ ክርስቲያን የድኅነት ሥፍራ ናት:: መጠጥ ቤት ደግሞ የጥፋት ጎዳና ነው:: በዚህ ሰው ታሪክ ውስጥ ግን በድኅነት ሥፍራ ካሉ ሰዎች ይልቅ በጥፋት ሥፍራ ያሉ ሰዎች ለሰውዬው ስኅተት የተሻለ ፍቅር አሳዩ:: አንዳንዴ የአንዳንድ ምእመናን ጠባይ ነፍሳትን ወደ ሲኦል ይሰድዳል::

አንዳችን የአንዳችን ጠባቂ መሆን እንችላለን ዓለምን ለመፈወስ የሚቻለንን እናድርግ:: ነፍሳትን ከማዳን ነፍሳትን ማጥፋት በጣም ቀላል ነው::

መድኃኔዓለም ክርስቶስ የኃጢአተኞች ወዳጅ ነበረ:: እሱ የማንንም ቅስም በክፉ ቃል አልሰበረም:: እኛ ግን ሰው ላይ ስንጨክን መጠን የለንም:: በዚህ ምክንያት እንደ ኒቼ ያሉ ሰዎች "ብቸኛው ክርስቲያን መስቀል ላይ የሞተው ነው" ብለው እስኪዘብቱብን ደርሰዋል::

መጽሐፍ ግን ሰው ሲሳሳት ስናይ ምን ማድረግ እንዳለብን እንዲህ ሲል ይናገራል :-

"ወንድሞች ሆይ፥ ሰው በማናቸውም በደል ስንኳ ቢገኝ፥ መንፈሳውያን የሆናችሁ እናንተ እንደዚህ ያለውን ሰው በየውሃት መንፈስ አቅኑት" ገላ. 6:1

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ

የፌስቡክ ገጽ :- https://t.me/eotcy