2022-08-07 06:53:30
ልመናዋ ክብሯ የልጁዋም ቸርነት በሁላችን ላይ ለዘለዓለም በእውነት ይደርብንና አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ይሕ ነው።
በበጎ ምግባር በሃይማኖትም ፍጹም የሚሆን እግዚአብሔርን የሚፈራና ቸር የሚሆን አንድ ሰው እንደ ነበር ተነገረ። በሕፃንነቱ ሳለ በንጽሕና በቅድስና ጸንቶ የመላእክትን አስኬማ ተቀበለ። የምንኩስናን ልብስ ከለበሰ ጀምሮ አራት ዓመት በሆነው ጊዜ በሰውነቱ የሌሊት ሕልም ዝንየት ስለመታው ደንግጦ የሚሠራውን አጣና ሰውነቱን ገሠጻት። ሰውነቴ ሆይ ከዛሬ ጀምሮ በሞት ወጥመድ እንደ ተያዝሽ እንደ ተጠመድሽ ዕወቂ አላት።
ነገር ግን ሰውነቴ ሆይ ከጽብዓ ሰይጣን ታመልጪ ዘንድ የምታመልጭበትን መርምሪ ዕወቂም። ከዛሬ ጀምሮ የዚሕን ዓለም ጣዕም ቀምሰሽዋልና። ከዚሕም ነገር በኋላ የዚሕ ሕፃን ልቡና ተመለሰለትና የነፍሱን ረድኤት ለማግኘት ከልቡናው ጋራ ተማከረ አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች የክብርት እመቤታችንንም ረድኤቷን መረመረ።
እመቤቴ ሆይ በልቡና ትጋት ስሚኝ እኔ ባለ ዘመኔ ሁሉ ጊዜ ያንች አገልጋይ እሆን ዘንድ እወዳለሁና አላት። አንቺን ስለ መውደድ ያንቺን ልብስ የተባለች ይሕችን የምንኩስናን ልብስ ስለ ለበስኳት አንቺን ስለመውደድ በወገቤ ቅናተ ዮሐንስን ታጥቄ ነበር እኮን ይኸውም የድንግልና ቅናት አምሳል ነው። እነሆ ለባለሟልሽ ለዮሐንስ ተሰጠ፡፡ አንቺን ስለወደድሁ መከራ የምቀበልበትን የከበረ ቆብን በራሴ ላይ አኖርሁ።
ይኸውም የእናትሽ የሐና ዘመዶች በዕለተ ዓርብ በልጅሽ ተዋሕዶ ቀን የደፉለት የአክሊለ ሶክ አምሳል ነው። ንግሥት ሆይ አንቺንም ስለመውደዴ በአንገቴ ላይ የመላእክትን አስኬማ አስገባሁ። ይሕችውም ልጅሽ መድኃኒታችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ያን ጊዜ የያዘችው የአይሁድ ብዕል አምሳል ናት። እመቤቴ ሆይ ይሕን ሁሉ አስበሽ ከሰይጣን ወጥመድ ሰውነቴን አድኛት። እመቤቴ ሆይ ያንቺ አገልጋይ እሆን ዘንድ ልቡናሽ ከወደደ በፍጥረት ሁሉ ባሕርይ ያለ የኃጢአት ሕልም ዝንየትን አጥፊልኝ ያለ ኃጢአት በንጽሕና ጸንቼ ያንቺን ቸርነት እነግር ዘንድ።
በሕይወተ ሥጋ ሳለሁ ዘወትር አመሰግንሽ ዘንድ ያለ ኃጢአት ተአምራትሽን እናገር ዘንድ የአምላክ እናት ሆይ በቸርነትሽ ብዛት ይሕን የልቡናዬን ፈቃድ ፈጽሚልኝ ይሕም ባይሆን ከዚሕ ከአላፊ ዓለም አነዋዋር ሰውነቴን ለይያት። ያን ጊዜ አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ተገልጻ ልጄ ወዳጄ አትዘን አትሸበር በልቡናህም ጥርጥር አይደር ለሚሠራት ሁሉ በጎ የምትሆን ይሕችን ምክር እኔን ስለ መውደድ አስበሀታልና አለችው።
ጌትነቱም ለዘለዓለም ይኖራል ነቢይ እንዳንተ ስላሉ ሰዎች በሥራቸው ንጹሓን የሆኑ በእግዚአብሔር ሕግ ጸንተው የሚኖሩ ንዑዳን ክብራን ናቸው ብሏል። በፍጹም ልቡናቸው የሚሹት አምልኮቱንም የሚጠብቁ ንዑዳን ክብራን ናቸው። አቸናፊ ልጄም ጌትነቱን በምታናገር ወንጌል ከቂም ከበቀል ንጹሐን የሆኑ ንዑዳን ናቸው ብሏል፣ እግዚአብሔርን ያዩታልና። ዳግመኛም አዶናይ ልጄ ተመልሳችሁ እንደ ሕፃናት ካልሆችሁ መንግሥተ ሰማይትን አትወርሷትም አለ። እመቤታችን ይሕን ተናግራ ያለነውር ያለ ነቀፋ ንጹሓት ክቡራት በሚሆኑ እጆቿ ባረከችው። ያሳብህን ፈቃድና የልቡናህን ተምኔት ሁሉንም እነሆ አደርግልሃለሁ አለችው። የመላእክትን ንጽሕና ገንዘብ አደርግልሀለሁ። አንተ የጠላኸው ይሕ የሚያስነቅፍ ነገር እንግዲህስ ወዲህ ሁለተኛ አያገኝህም።
ይሕ አንተ ንቀህ አጥቅተህ አቅለህ የጣልኸው ኃጢአት እንግዲህ ወዲህ ሁለተኛ አይደርስብህም። ከእንግዲህ ወዲህ ከኔ ፍቅርና ከእግዚአብሔር ፍቅር የሚለይ የሚያርቅ ይህ የበደል ኃጢአት ዳግመኛ ወዳንተ አይቀርብም። ስለዚህ ነገር በፍጹም ልቡናህ ፈጽሞ ደስ ይበልህ የልቡናህን ፈቃድ አድርጌልሃለውና።
ዳግመኛም ወዳጄ ሆይ በእኔ ቃል ኪዳን እመን እንጂ አትጠራጠር እኔም ዘወትር ካንተ አልቀርም እቀበልሃሁ እሺ በጀም እልሃለሁ አለችው። የበጎ ምልክት አደርግልህ ዘንድ እጅህን ስጠኝ በእጅህ ላይ ፍጹም ድኅነት ይደረጋልና፡፡ ከዛሬ ጀምሮ ካንተ አልለይም ልጄ ከዚሕ ከሚያልፈው ዓለም ለይቶ እስኪወስድህ ድረስ ካንተ ጋራ እኖራለሁ እንጂ። ካንተ አልለይም እንዳለችው በእጁ ላይ ብዙ ድንቅ ፍጹም ተእምራት አደረገችለት ሊቃውንትና ጳጳሳት ነገሥታትና መኳንንት ደኅነቱን እስኪያደንቁ ድረስ። የሌሊት ህልም ዝንየትም ከዚሕ ዓለም ዐርፎ እስኪለይ ድረስ ሁለተኛ አልተዋጋውም።
አምላክን በወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ በጸናች በክብርት እመቤታችን አማላጅነት ወደ መንግሥተ ሰማያት ገባ። ፍጹም ልመናዋ ክብሯም በባሪያዋ በተክለ ጻዲቅ እና በሁላችን በወንዶችም በሴቶችም በሽማግሎችም በዲያቆናትና በቀሳውስትም ተአምሯን ለመስማት ከዚሕ በቆምነ በእኛም ላይ ይደር። የተወደደች የከበረች ከፍ ከፍ ያለች ዛሬ የተድላ የደስታ ቃል በእውነት ያለ ሐሰት ታሰማን። በቃሏ በዚሕ ዓለም ጥፋት ከታዘዘበት ሰዓትና ከዕለተ ሞት እኔ በእውነት እጠብቃችሁ አለሁ ትበለን በሚመጣው ዓለም መንግሥተ ሰማያትን እንድትወርሱ አደርጋለሁ ትበለን። ከናንተ አንድ ስንኳ በኃጢአት በመጣ ሞት አልለይም። ስማችሁንም ተቀዳሚ ተከታይ በሌለው አቸናፊ ልጄ በቀይ ደሙ ቀለምነት እጽፈዋለሁ። የሐዋርያት የነቢያት ስም ከተጻፈበት ዘንድ ።
በሰማይና በምድርም ያለ የፍጥረት ሁሉ አንደበት በእውነት ይደረግልን ይበል።
98 viewsኢየሱስ እግዚአብሔር የእግዚአብሔር ልጅ, 03:53