2022-07-29 14:26:28
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ዛሬ ሐምሌ 22 በዚህች ቀን ኢቲዮጲያዊው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ጴጥሮስ በሰማዕትነት አረፉ::
የ20ኛው ክፍለ ዘመን ታላቅ ሰማዕት የሆኑት አቡነ ጴጥሮስ በ1875 ዓ.ም በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሰሌላ አውራጃ ፍቼ ከተማ ተወለዱ::
አቡነ ጴጥሮስ በሰማዕትነት እንደሚሞቱ አስቀድመው መምህራቸው በትንቢት ነግረዋቸው ነበር።
"አለቃ ተጠምቀ" የተባሉ ቅድስናን ከሊቅነት ጋራ አስተባብረው የያዙ የቅኔ መምህራቸው አንድ ቀን አቡነ ጴጥሮስን ጠርተው "ኃይለ ማርያም አንተ ወደፊት ጳጳስ ትሆናለህ፤ በወቅቱም አረመኔ በዚህች ሀገር ይሰለጥናል። ታዲያ ያኔ አንተ ለነፍስህ ሳትሰቀቅ በሰማዕትነት እለፍ፤ ሰማዕትነት ክፍልህ ነው፣ አደራ" ብለዋቸው ነበር። ይኸውም ትንቢት ደርሶ አቡነ ጴጥሮስ በሰማዕትነት ለማረፍ በቅተዋል።
ብፁዕ አባታችን የጵጵስና ስማቸውን ከማግኘታቸው በፊት መምህር ኃይለ ማርያም ይባላሉ ነበር።
በልጅነታቸው ወላጆቻቸው ወደ ደብረ ሊባኖስ በመውሰድ በሃይማኖትና በምግባር ተኮትኩተው እንዲያድጉ አድርጎቸዋል።
የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ከንባብ እስከ ቅኔ ያሉትን ትምህርቶች በሚያስገርም ፍጥነት ከተማሩ በኋላ ወደ ቅኔ አውድማ ጎጃም በመሔድ በዋሽራ የቅኔ ትምህርታቸውን ፈጽመው መምህር ሆነዋል።
የዜማውንም ትምህርት ወደ ጎንደር ሔደው ተምረዋል። ወሎ ቦሩ ሜዳ ከሊቁ አካለ ወልድ የብሉያትን፤ ሐዲሳትንና የሊቃውንት ትምህርት በሚገባ አሒዱ።
በ1900 ዓ.ም ወሎ አማራ ሳይንት ሔደው ምስካበ ቅዱሳን ገዳም ገብተው ወንበር ዘርግተው ለ9 ዓመታት ቅኔንና መጻሕፍትን አስተማሩ።
በ1910 ዓ.ም ወደ ደብረ ሊባኖስ መጥተው ሥርዓተ ምንኩስና ፈጸሙ። በመምህርነት ተሾመው ደብረ መንክራት ምሁር ኢየሱስ ገዳም ለ6ዓመታት፤ በ1916 ዓ.ም በዝዋይ ደብረ ጽዮን ቅድስት ገዳም ለ3ዓመታት፤ በ1919 ዓ.ም አ.አ ማርቆስ በመምህርነትና የዓፄ ኃይለ ሥላሴ መምህረ ንስሐ ሆኑ።
ኢትዮጵያ የራሷን ጳጳሳት ስትሾም በስነ ምግባር ከተመሰከረላቸውና ከተመረጡ ጳጳሳት አንዱ ሆነው ግንቦት 18 ቀን 1921 ዓ.ም ጵጵስና ተሾሙ።
ብፁዕ አባታችን "አቡነ ጴጥሮስ ጳጳስ ዘምሥራቅ ኢትዮጵያዊ ተላዌ አሠሩ ለአቡነ ኢየሱስ ሞዐ" ተብለው መንዝና ወሎ አገረ ስብከት ተሾሙ።
ቅዱስ አባታችን ቅድስት ቤተክርስቲያናችንና ቅድስት ሀገራችንን በጸሎታቸው፣ ሕዝቡን በትምህርታቸው እየጠበቁ በተጋድሎ እየኖሩ ሳለ አረመኔው የኢጣሊያ ፋሺስት በ1928 ዓ.ም በኢትዮጵያ ላይ የግፍ ጦርነትን አውጆ ሕዝቡን በግፍ ይገድል ቤተ ክርስቲያንን ያቃጥል ጀመር።
በየገዳማቱ በርካታ ካህናትና መነኮሳት ተገደሉ፣ ብርቅዬ የቤተ ክርስቲያን ቅርሶች ተዘረፉ።
አቡነ ጴጥሮስ ይህን ግፍ በማየታቸው ከሀገራችን አርበኞች ጋር በመሆን በጸሎታቸው ሊዋጉት ተነሡ።
አባታችን ዓፄ ኃይለ ሥላሴ በመከተል ወደ ማይጨው ሔደዋል። በዚያም በመርዝ የተደገፈ ጦርነትን ፋሺስት እያደረገ ሕዝቡን ሲገል ሥራዊቱን ሲበትን ተመለከቱ።
ወደ አ.አ ከተመለሡ በኋላ ደብረ ሊባኖስ ሔደው ለሀገርና ለነፃነት መሞት ቅዱስ ተግባር መሆኑን ለሠላሌ በሚገባ አስተምረዋል።
በደብረ ሊባኖስ ገዳም በጾምና በጸሎት ተጠምደው እግዚአብሔር የኢትዮጲያን ሕዝብ በምሕረቱ እንዲታደጋት እየተማጠኑ ወደፊት ለሚመጣባቸው ተጋድሎ መዘጋጀት ጀመሩ::
ወደ አ.አ በመመለስም ይህን ተግባራቸውን ይፈጽሙ ነበር። ጠላት በመላዋ ከተማ ያሰማራቸው ባንዳዎችን አባታችንን ይቃወሟቸው ይፈለጉም ጀመረ።
አባታችን ግን "የሀገሬ ሕዝብ ለጠላት እንዳይገዛ በአደባባይ አውግዤ ጠላትን ረግሜ ባልፍ ይሻለኛል" ብለው ወሰኑ።
በግዜው የፋሽስት ኢጣልያ እንደራሴ የሆነው ራስ ኃይሉ በጥብቅ ይፈልጋቸው ያድናቸው ነበር።
እሱም ብፁዕ አባታችንን ወስዶ ለግራዚያኒ ሐምሌ 22 ቀን 1928 ዓ.ም አሳልፎ ሰጣቸው። ግራዚያኒን አጥብቆ ሲፈልጋቸው ነበርና ተደሰተ።
በኋላ ተይዘው ታሰሩ ሕዝቡንም ለፋሽሽት ለጣሊያን መንግስት እንዲገዛ ስበክ ተናገር ተባሉ።
ለዚህም መደለያ የተቀናጣ ቤት፣ ዘመናዊ መኪና፣ ከሮም መንግስት ዕውቅና ይሰጧታል ቢላቸው አሻፈረኝ አሉ።
ነገር ግን ሊገደሉ ሲፈረድባቸው በአደባባይ የእሳቸ ፍርድ ለሚጠባበቀው ሕዝብ መስቀላቸውን አንስተው በ4 አቅጣጫ ባረኩ።
በፍርድ ወንበር ላይ የተቀመጠው ዳኛም አቡነ ጴጥሮስን " ሕዝቡን ቀስቅሰዋል ራሶም አምፀዋል ሌሎችም እንዲያምጹ አድርጎዋል" አላቸው።
ቀጥሎም "ካህናቱም ሆነ የቤተ ክህነት ባለስልጣናት ሊቀ ጳጳሱም አቡነ ቄርሎስ የጣሊያን ገዢነት አምነው አሜን ብለው ሲቀበሉ እርሶ ለምን አመፁ? ለምን ብቻዋን አፈንጋጭ ሆኑ?" ሲል ጠየቃቸው።
ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ በቆራጥነት የሚከተለውን መለሱ፦
"አቡነ ቄርሎስ ግብፃዊ ናቸው፤ ስለ ኢትዮጵያና ስለ ኢትዮጵያዊያን የሚገዳቸው ነገር የለም፤ እኔ ግን ኢትዮጵያዊ ነኝ ሕዝቤም ጭምር፤ ሓላፊነትም ያለብኝ የቤተ ክርስቲያን አባት ነኝ፤ እኛ ኢትዮጵያዊያን ስንሞትም ስንኖርም ኢትዮጵያዊ ነን" ብለው በቁርጠኝነት ተናገሩ።
ቀጠል አድርገውም "ለፈጣሪዬ ብቻ የምናገረውን እናገራለሁ። እኔን ለመግደል እንደወሰናችሁ ዐውቃለሁ።ስለዚህ በኔ ላይ የፈለጋችሁትን አድርጉ። ግን ተከታዮቼን አትንኩ።" አሉ።
ወደ ሕዝቡ ዞር ብለውም "አረማዊ የሆነው የፋሺስት መንግስት ቤተ ክርስቲያን ለማቃጠል፣ ሕዝበ ክርስቲያን ለመግደል፣ ሃይማኖትን ለማጥፋት፣ ታሪካችንን ለማበላሸት የመጣ ነው፤ እንጂ በጎ ለመሥራት ስላልመጣ ለዚህ ግፈኛ አትገዙ። ስለ ውድ አገራችሁ፣ ስለ ቀናች ሃይማኖታችሁ ተከላከሉ። ነጻነታችሁ ከሚረክስ ሙታችሁ ስማችሁ ቢቀደስ ታላቅ ዎጋ ያለው ክብር ታገኛላችሁ። የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዚህ ለጣላት እንዳይገዛ አውጋዣለሁ፤ የኢትዮጵያ መሬት ጠላትን ብትቀበል የተረገመች ትሁን። በፈጣሪዬ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተገዘተች ትሁን።" በለው አወገዙ።
ችሎት ላይ ያለውን ሕዝብ በሙሉ ስለ እርሳቸው ሲያለቅስ አሳቸው ግን መስቀላቸውን አውጥተው እየጸለዩ ሕዝቡን ባረኩ።
ወደ መግደያ ቦታም ወሰዷቸው በዚህ ጊዜ በዛሬዋ ዕለት ከአራዳ ጊዮርጊስ ዝቅ ብሎ ባለው ቦታ በአደባባይ በጥይት ሩምታ ዘንቦባቸው በሰማዕትነት አረፋ::
ቤተ ክርስቲያንም ጥቅምት 12 ቀን 1998 ዓ.ም "አቡነ ጴጥሮስ ሰማዕተ ጽድቅ ዘኢትዮጵያ" ተብለው እንዲጠሩ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል።
ጻድቁ በተወለዱበት ሥፍራም በፍቼ ከተማ ግንቦት 1 ቀን 2001 ዓ.ም ጽላት ተቀርጾላቸው ቤተ ክርስቲያን በስማቸው ታንጾላቸው መታሰቢያ ሐውልትም ቆሞላቸዋል።
ያልተነገረላቸው ሰማዕታት ያልተዘመረላቸው ጀግና የደብረ ሊባኖስ ኮከብ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ጴጥሮስ በረከቶ ይድረሰን።
ዛሬ ያሉ የቤተ ክርስቲያን ልሂቃን ሆይ መንፈሳዊ ጀግንነትን ከአባታችን ይዛችሁ የሀገር አንድነትን አስጠብቁልን የቤተ ክርስቲያን ርስት ጉልትን አትስጡብን።
የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት የአባታችን በረከት ይድረሰን ይደርብን ለዘላለሙ አሜን!
መልዕክት!
ዛሬ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር አንድ አባት እንዲህ ብለዋል ብለው ስማቸውን መጥራት ያልፈለጉትና የኢትዮጵያን አንድነትና ኢትዮጵያዊነትን በዚያ ጊዜ ያንጸባረቁበትን ቃል የወሰዱት ከብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ እንደሆነ አንባቢ ልብ ይሏል!
ቤተ ተክለ ሃይማኖት
ወኢያኅጥኦሙ እምዘ ፈቀዱ።
አሁኑኑ join ያድርጉ ሁሌ መረጃ ይደርሶታል
@beteteklehaimanot24
734 viewsJERMI, 11:26