16 የገጠር ቀበሌዎች የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ ሆኑ በአማራ ክልል ኤሌክትሪክ አገልግሎት በባህርዳር ዲስትሪክት ስር ያሉ 16 የገጠር ቀበሌዎች የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ ሆኑ፡፡ በክልሉ የአገር አቀፍ ኤሌክትሪክ አቅርቦት ፕሮግራም የባህርዳር ዲስትሪክት ማስተባበሪያ በ2015 በጀት ዓመት 10 የገጠር ቀበሌዎችን የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ አቅዶ ባከናወነው ስራ ሁሉም ቀበሌዎች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ በተጨማሪም ባለፈው በጀት ዓመት ግንባታቸው ያልተጠናቀቁ የ6 ቀበሌዎችን ግንባታ በማጠናቀቅ በአጠቃላይ በ16 ቀበሌዎች ለሚገኙ 6 ሺ 412 ነዋሪዎች የኤሌክትሪክ አገልግሎትን ተደራሽ ማድረግ ተችሏል፡፡ እነዚህን የገጠር ቀበሌዎች የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ለማድረግ 153 ነጥብ 4 ኪ.ሜ የመካከለኛ መስመር እንዲሁም 196 ነጥብ 1 ኪ.ሜ የዝቅተኛ መስመር ዝርጋታ የተሰራ ሲሆን የ36 የተለያየ አቅም ያላቸው የትራንስፎርመሮች ተከላ ስራም ተከናውኗል፡፡ በከፍተኛ ወጪ የተገነባውን ይህን የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት የአካባቢው ህብረተሰብ እንደ ራሱ ንብረት እንዲጠብቅ እንዲሁም ህገወጥ ተግባር ሲፈፀምም ከተቋሙና ከፀጥታ ሀይሎች ጋር በመተባበር ወደ ህግ በማቅረብ ረገድ የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ማስተባበሪያው አሳስቧል። #የኢትዮጵያኤሌክትሪክአገልግሎት ወቅታዊና ትኩስ መረጃዎች ወዲያውኑ እንዲደርሳችሁ ይህንን ድረ-ገፅ ይመልከቱ፡ http://www.eeu.gov.et 2.9K views14:25