Get Mystery Box with random crypto!

__ጦማር ዘጴጥሮስ__ ቁጥር ፬:- ለጥምቀት በዋጋ መማለጃ የተቀበለ የተሻረና የተወገዘ ነው። | በትረማርያም አበባው Betremariam Abebaw

__ጦማር ዘጴጥሮስ__
ቁጥር ፬:- ለጥምቀት በዋጋ መማለጃ የተቀበለ የተሻረና የተወገዘ ነው።

ቁጥር ፭:- ልጄ ሆይ የክህነትን ስጦታና የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ በገንዘብ አትሽጥ። በክህነት ላይ አትነግድ።

ቁጥር ፮:- በክህነት መማለጃ የሰጠም የተቀበለም ክህነት የለውም።

ቁጥር ፯:- የበደለህን በየሰባቱ ሰባ ጊዜ ይቅር በለው።

ቁጥር ፰:- ከኃጢአቱ ንስሓ የሚገባን ተቀበለው የበደለውንም ይቅር በለው። በእጅህም አንሣው ገሥጸውም። የታመሙትን ጎብኝ፣ የተራቡትን አብላ፣ የተጠሙትን አርካ፣ የተራቆቱትን አልብስ፣ ወደታሠሩትም ሂድ።

ቁጥር ፱:- ከእግዚአብሔር ቅዱሳት መጻሕፍትን ስማ።

ቁጥር ፲፩:- አባት እናት ለሌለው እራራለት። በራስህ ላይ ለሰይጣን መንገድ አትስጥ።

ቁጥር ፲፫:- ችግረኛ ካህን ካየህ ከተቀበልከው ገንዘብ እርዳው።

ቁጥር ፲፬:- ለአብያተ ክርስቲያናት፣ ለአድባራትና ለገዳማት ግንባታ ራስህን አትጋ።

ቁጥር ፲፯:- ችግረኛን ከቤትህ በር ላይ አታባረው። ቸል ቸል አትበለው። አትናቀው። አታቃለው። ከአንተ ጋርም በማዕድህ እንዲቀመጥ አድርገው።

ቁጥር ፲፱:- ምእመናንን ለመጥቀም ካልሆነ በስተቀር ወርቅና ብር አትሰብስብ።

ቁጥር ፳-፳፩:- ለምእመናን ልጆች ሰላምን አብዛ። ልጄ አረጋውያንን አክብራቸው። ነገራቸውንም ስማቸው። ገሥፀው ንገረው እንጂ በኃጢአቱ ምክንያት በሰው ላይ አትሳለቅ። እግዚአብሔርን ወደ መፍራትም በየዋህነት መልሰው።

ቁጥር ፳፪:- ቀጥተኛ በሆነ ነገር ነገሥታትን እዘዛቸው። በመጥፎ ሥራቸው ውቀሳቸው። ቁርባን መቁረብ ጥፋትን ይከላከላል።

ቁጥር ፳፫:- በ3ኛው፣ በ7ኛው፣ በ12ኛው፣ በ30ኛው፣ በ40ኛው፣ በ60ኛው ቀን ሙታንን አስቧቸው። ልጄ ሆይ የተጠመቀ ኃጢአተኛ ነፍሱ በሞተ በ40ኛው ቀን ከክርስቶስ ፊት እንደምትቀርብ እወቅ። እንደ ሥራውም ይከፈለዋል።

ቁጥር ፳፬:- ምእመናን የመለኮትን የተቀደሱ መጻሕፍት ለመስማት በእግራቸው ይቁሙ። ለመጠመቅ የሚፈልግን ሰው በውኃ ከመጠመቁ በፊት የደስታ ቅባት ቀባው። ከተጠመቀ በኋላ ደግሞ ቅብዐ ሜሮን ቀባው።

ቁጥር ፳፱-፴:- ያልተጠመቀ ሰው ያረደውን አይብሉ። የአይሁድን ቂጣ አትብሉ። ከእነርሱ ጋር አትጋቡ።

ቁጥር ፴፪:- አማኝ ሆይ መተኛት በፈለግህ ጊዜ ፊትህን አማትብ። ከሰማዕታት አፅም ተባረክ።

ቁጥር ፴፫:- ካህን ሆይ ከንጹሕ ስንዴ በቀር በመሥዋዕቱ ላይ ስብና ሥጋ አታቅርብ። በመሠውያው ላይም አታስቀምጥ። ከወይን ፍሬ በስተቀርም ከጠጅ መሥዋዕት አትሥራ። የስንዴ እሸት በደረሰ ጊዜ የተለቀመ ይሁን።

ቁጥር ፴፭:- የፋሲካ በዓል ከሁሉም በዓላት ይበልጣል። ይከብራልም። ከደስታ በስተቀር ሐዘን አይደረግበትም።

ቁጥር ፴፮:- በቅዳሴ ጊዜ ሙታንን ሁልጊዜ አስታውሱ። እጅግ ይጠቅማቸዋልና።

ቁጥር ፴፯:- ከቂጣ በዓል በኋላ በሚውለው እሑድ የፋሲካን በዓል አክብሩ።

ቁጥር ፵፬:- የሕጉን ታቦት ሁሉ ባርክ። በእግዚአብሔር ማኅተም አትመው። በምትባርከው ጊዜ ሰባት ቀሳውስት ከአንተ ጋር ይኑሩ። ክህነትን ለመስጠትም በቅብዐ ሜሮን አትም። እንዲሁም ንጉሥን ለማንገሥ አትም።

ቁጥር ፶፩:- ከሊቀ ካህናት ሳያገኝ ክህነትን ነጥቆ የወሰደ ሰው ቢኖር ከእግዚአብሔር ቤተክርስቲያን ይሰናበት።

ቁጥር ፶፪:- በሰንበታትና በበዓላት የዮሐንስን ወንጌል በመሠውያው ላይ ያንብቡ። እርሱ የመለኮትን ምሥጢር የሚናገር ነውና።

ቁጥር ፶፫:- በሁሉም ቤተ መቅደስ ውስጥ ሁለት መሠውያ ይኑር። አንዱ ከቦታ ወደቦታ የሚንቀሳቀስ፣ ሁለተኛው ከቦታው የማያነቃንቁት ይሁን።

ቁጥር ፶፯:- ሕዝባዊ ካህንን ቢሰድበው ወይም ቢረግመው እግዚአብሔር ከሚመለክባቸው አገሮችና ከቤተክርስቲያኑ ይሰደድ።

ቁጥር ፷:- ከምእመናን ኃጢአቱ የበዛ ሰው ቢኖርና እንዲወገድለት ቢፈልግ ኃጢአቱን ለካህን እና የእግዚአብሔርን መጻሕፍት ለሚያውቁ ሊቃውንት ይግለጣት።

ቁጥር ፷፪:- የክህነት ልብስ ከሌሎች ሕዝባውያን ልብሶች የተለየ ይሁን። ልብሱ ከመጠምጠሚያው በስተቀር ሰፊ ይሆን ዘንድ ይገባል።

ቁጥር ፷፬:- ካህን ቀን መዝሙረ ዳዊትን ያንብብ፣ ሌሊት ደግሞ የነቢያትን ምስጋና ያንብብ።

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን
መ/ር በትረማርያም አበባው