2022-08-03 15:40:37
ዕጨጌ ፊሊጶስ እና ቅበላ:-
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ዛሬ ሐምሌ ሃያ ስምንት የብርሃን ዓለም ተክለ ሃይማኖት ደቀ መዝሙር ከሆኑ ከ12ቱ ከዋክብት አንዱ የሆኑት 3ተኛው ዕጨጌ ፊሊጶስ እረፍታቸው ነው::
በደብረ ሊባኖስ ገዳሙ በወርሀ ግንቦት ያጥናሉ::ሀገረ ሙላዳቸው በሠላሌ ዝማ በምትባል ስፍራ ነው::
ከአባ ዮሓንስ ዲቁና ተቀበሉ መጽሐፈ ነቢያትንና ሐዋርያትን መዝሙረ ዳዊትን ተምረዋል::
በደብረ ሊባኖስ ገዳም በሥርዓተ ምንኩስና በትኀርምት መኖር ጀመሩ::
ተጋድሏቸውና መንፈሳዊ ሕይወታቸው ተነግሮ አያልቅም እፍኝ አተር በቀን እየተመገቡ ሦስት ዓመት ኖሩ በኋላ በአቡነ ተክለ ሃይማኖት እጅ መንኲሰው ሢመተ ክህነት ተቀበሉ::
በጳጳሱ አባ ያዕቆብ ጵጵስና ተቀበሉ በሰላም ሲያስተዳድሩ ንጉሥ ዐምደ ጽዮን የአባቱን ዕቁባት ማግባት አይገባህም ሲሉ ተቃወሙት::
የንጉሡም አሽከሮች ደበደቧቸው ገረፏቸው ደማቸውም ፈሰሰ ከደማቸው እሳት ተነስቶ ከተማይቱን አቃጠላት::
ንጉሡም ፈርቶ ወደ ትግራይ አባረራቸው:: አባታችንም በተሰደዱበት በሔዱበት አገር እግዚአብሔር ከሳቸው ጋር ነውና ተአምር አደረጉ በአምልኮ ጣዖት ያሉትን ወደ ክርስትና መለሱ የሥነ ምግባር ድቀት ያለባቸውንም መክረው መለሱ::
ኋላም ንጉሡ ሲሞት ወደ ደብረ ሊባኖስ ተመለሱ በንጉሡ ፈንታ የነገሠው ልጁ ወደ ዛይ ደሴት ዝዋይ ለሰባት ዓመት አሰራቸው::
ከዚህ በኋላም አስጠርቶም ወደ ዳሞት አጋዛቸው በዛም የበዙ አረማውያንን ክርስቲያን አደረጎቸው እየመከሩና ወንጌልን እያስተማሩ አንድ ዓመት ተቀመጡ::
ዝናቸውን የሰሙ አቡነ ሰላማ አስጠሯቸው ብዙም መንፈሳዊ ጨዋታት ተጨዋወቱ ጳጳሱም አደነቁ ወደ ደብረ ሊባኖስ እንዲሄዱ ፈቀዱላቸው ንጉሡም ተስማማ::
በደብረ ሊባኖስ ገዳምም ብዙ ሥራ ፈጸሙ ዛሬ የምናየው የገዳሙን ሥርዓት የቀረጹት አባት አቡነ ፊሊጶስ ናቸው::
የደብረ ሊባኖስ ቤተ ምርፋቅ ሹመትና የሥራ ድርሻ የመጋቢው የቂሰ ገበዙ የሊቀ አበውና ሊቀ ረድ የሥራ ድርሻ የፀባቴው አሿሿምንና የሥራ ድርሻ ቀርጸው አስቀምጠው ገዳሙም እስከ ዛሬ በረከታቸው ይደርብንና እየተጠቀሙበት ይገኛሉ::
ስለ ቤተ ክርስቲያን መምህራን የሥራ ድርሻና ስላላቸው ክብር ስለ ድርጎ አሰጣጥና የጸሎት ሰዓታት በሥርዓት ቀርፀው ያስቀመጡ አባት ናቸው::
በዛሬው ቀንም ስለ ሰባቱ ቱሩፋታቸው ሰባት አክሊል ሰጥቷቸው ቃል ኪዳንም ሰጥቷቸው በ74 ዓመታቸው አረፉ::
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የአባታችን በረከትና ቃል ኪዳን ከኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን::
ቅበላ
አባቶቻችን ከሐምሌ 28-30 ለጾመ ፍልሰታ ጾምን በመጾም ቅበላ ያደርጋሉ::
ቅበላ ማለት በእንግድነት ለሚመጣው እንግዳ ለእንግዳው የሚመጥነውን ያህል ክብር ለመስጠት አዘጋጅቶና ተዘጋጅቶ መቀበል ነው::
ቅበላው መንፈሳዊ ከሆነ በመንፈሳዊ ሕይወት ጸድቶ መዘጋጀት ነው:: መጪው ጾም ከሆነ ለዚህ እንግዳ ንስሐ መግባትን በመጾም በመስገድ በጾሙ ወቅት ለሚፈጸሙ ሥርዓቶች ራስን አዘጋጅቶ መቀበል ነው::
በዚህም ምክንያት ቅበላን በመብል በመጠጥ ሳይሆን ጾምን ሯሷን ጹመው ቅበላ ያደርጉባታል አበው::
ምክንያቱም በጉጉት የሚጠብቋት የሚጠቀሙባት በዓመት የሚናፍቋትን የጾም እንግዳ ሊቀበሉ ነውና! እንግዳ ሲመጣ እንደ እንግዳው ክብር መዘጋጀት ይገባልና::
እኛ ልጆቻቸው ዛሬ እንደሚታየው እንደነርሱ ባንሆን እንኳ እነርሱ የሰሩትን ሥራ ሠርተን ልንመስላቸው ይገባ ነበር::
ቅበላ ምግብን በመበቀል አልነበረም:: በጾም እንደ አበው ይገባ ነበር:: ግን ለክርስቲያኖች በማይገባ በመብል በመጠጥ በዝሙት በጭፈራ በዳንኪራ ጾምን መቀበል ነውር ነው::
አንድ መንፈሳዊ ሰው ክርስቶስን ነው የተሸከመው በክርስቶስ ነውና ክርስትናን ያገኘው እና ክርስቲያን መሆን አለበት::
አብዝቶ መብላትና መጠጣትን በማንኛውም ቀን ቢሆን ለክርስቲያን በዚህ ግብር መታደም መታየትም ማሰብም አይገባም::
በክርስቶስ ደም የከበረን ሰውነት በዝሙት በሥካር በጭፈራ በእንደዚህ ያሉ ግብር ማቆሸሽ ተገቢ አይደለምና::
በየደብሩና በየገዳሙም ሱባኤ ያሰብንም ንስሐ ገብተን የበደልነውን ክሰን የቀማነውን መልሰን በፊት ከምልበላው ከምንጠጣው ቀንሰን በመጥን ብቻ ሳይሆን በዓይነትም ቀንሰን አስመሳይ ሳንሆን ሆነን መጾም መጸለይ መስገድ መመጽወት በረከትም መታደልም ነው::
አበው "ከምግብ ብቻ በመከልከል እንጾማለን አትበሉ .. ከክፉ ግብር መራቅ ጾማችንን ትክክል ታደርጋለች" ይላሉ::
ከጾም በኋላ በሚኖረው ሕይወታችን በረከታችንን ሳናስወስድ የተውነውን ግብር ተመልሰን ሳንደግመው ልንጓዝ ያስፈልጋል::
በዚህም የአባቶቻችን ልጆች እንባላለን አባቶቻችን የወረሷትን መንግስት በእውነት እንወርሳለን::
ለዚህም አምላከ ተክለ ሃይማኖት ይርዳን አሜን! ይቅርታውና ቸርነቱ ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን::
ቤተ ተክለ ሃይማኖት
ወኢያኅጥኦሙ እምዘ ፈቀዱ።
አሁኑኑ join ያድርጉ ሁሌ መረጃ ይደርሶታል
@beteteklehaimanot24
359 views12:40