Get Mystery Box with random crypto!

ራያ ከአላማጣ እና የራያ ወረዳዎች የተፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር 50 ሺህ መድረሱን ተመድ አስታወቀ ግ | Ayu Zehabesha-Official (አዩ ዘሀበሻ)

ራያ
ከአላማጣ እና የራያ ወረዳዎች የተፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር 50 ሺህ መድረሱን ተመድ አስታወቀ
ግጭት ከተነሳባቸው የአላማጣ ከተማ፣ ዛታ እና ኦፍላ የራያ ወረዳዎች የተፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር 50 ሺህ መድረሱን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ እርዳታ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት አስታወቀ።
ተፈናቃዮቹ የተጠለሉባቸውን የዞን ባለሥልጣናት ዋቢ አድርጎ ጽህፈት ቤቱ ሰኞ ሚያዝያ 14/2016 ዓ.ም. ባወጣው ሪፖርት መሠረት ከተፈናቃዮቹ መካከል 42 ሺህ የሚሆኑ በሰሜን ወሎ በምትገኘው ቆቦ ከተማ እንዲሁም 8300 የሚሆኑት ደግሞ በሰቆጣ እና ዋግ ኽምራ ዞኖች ተጠልለዋል ብሏል።
በአብዛኛው ሴቶች፣ ህጻናት፣ ታዳጊዎች እና አረጋውያንን ያሉበት ተፈናቃዮች በማኅበረሰቡ ባሉ ቤቶች ለመጠለል እየሞከሩ እንደሆነ ገልጾ፣ ሌሎች ደግሞ ከቆቦ ከተማ ሦስት ኪሎ ሜትር ርቀት በሚገኝ ጋራ ሌንጫ በተሰኘው የኢንዱስትሪ መንደር ክፍት ቦታ ላይ ተጠልለው ይገኛሉ ተብሏል።
በዚህ ስፍራ የተጠለሉ ተፈናቃዮች በአስቸጋሪ ሁኔታ ለበልግ ዝናብ መጋለጣቸውን የጠቀሰው የመንግሥታቱ ድርጅት መግለጫ የተወሰኑትን ተፈናቃዮች ወደ ሌላ ስፍራ ለማዘዋወር እየተሞከረ እንደሆነ መሬት ላይ ያሉ አጋሮቹን ዋቢ አድርጓል ጠቅሷል።
የፌደራል ኃይሎች ጣልቃ መግባታቸውን ተከትሎ በአላማጣ፣ ወልዲያ እና ቆቦ ከተሞች አካባቢ ከትናንትና ሚያዝያ 14/ 2016 ዓ.ም ጀምሮ የፀጥታው ሁኔታ የተረጋጋ መሆኑም ተገልጿል።
ከአላማጣ ወደ ቆቦ የሚወስደው እንዲሁም ከአላማጣ ወደ ማይጨው የሚወስዱ መንገዶች ለትራንስፖርት ክፍት መሆናቸውን እንዲሁም ባንክን የመሳሰሉ ሕዝባዊ አገልግሎቶች እንደገና ሥራ መጀመራቸው ተጠቁሟል።
በትግራይ ክልል የተቀሰቀሰውን ጦርነት ተከትሎ ወደ አማራ ክልል እንዲጠቃለሉ በተደረጉ የአላማጣ ከተማ እና ራያ ወረዳዎች እንደ አዲስ የተቀሰቀውን ግጭት ተከትሎ በአዲስ አበባ መቀመጫቸውን ያደረጉ የካናዳ፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ጣሊያን፣ ጃፓን፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ አሜሪካ ኤምባሲዎች ውጥረት እንዲረግብ ጥሪ አቅርበዋል።
አዩዘሀበሻ
Join @ayuzehabeshaofficial