2022-07-30 00:01:21
ⒶⓇⓉⒾⓄⓈ
ⒶⓇⓉⒾⓄⓈ
ARTIOS DEVOTION
ⓟⓗⓘⓛⓔⓜⓞⓝ
ቀን #5 የልቤ ሰው - ተወዳጅ ወንድም ፊል 12 - 16
---------------------------------
¹² የልቤ ሰው የሆነውን እርሱን መልሼ ወደ አንተ ልኬዋለሁ።
¹³ ስለ ወንጌል በታሰርሁበት ጊዜ በአንተ ፈንታ ሆኖ እንዲያገለግለኝ ለራሴ ላስቀረው ፈልጌ ነበር፤
¹⁴ ነገር ግን አንተ የምታደርገውን መልካም ነገር ሁሉ በውዴታ እንጂ በግዴታ እንዳይሆን ሳላማክርህ ምንም ማድረግ አልፈልግም።
¹⁵ ምናልባት ለጥቂት ጊዜ ከአንተ የተለየው፣ ተቀብለህ ለዘለቄታው አንተ ዘንድ እንድታቈየው ነው፤
¹⁶ ከእንግዲህ ወዲህ ግን እንደ ባሪያ ሳይሆን ከባሪያ በላይ የሆነ ተወዳጅ ወንድም ነው። ለእኔ ተወዳጅ ነው፤ ለአንተ ግን በሥጋም በጌታም ይበልጥ ተወዳጅ ነው።
---------------------------------
ባለፉት ሦስት ጥናቶች ውስጥ ሐዋርያው ጳውሎስ በአናሲሞስና በፊልሞና መካከል ተከስቶ የነበረውን ግጭት ለመፍታት እንደ መንደርደርያ ያስቀመጣቸውን ሀሳቦች አይተናል።
በዛሬው ጥናታችን ደግሞ ወደ ዋናው ሃሳብ ይበልጥ የተጠጋበትን መልዕክት እንመለከታለን። የደብዳቤው ማዕከላዊ ሃሳብ ያለው "ተቀበለው" የሚለው በቁ. 17 ላይ የተጠቀሰው ቃል ሲሆን እርሱን በሚቀጥለው ጥናታችን እንደምንዳስስ ተስፋ አደርጋለሁ።
የዛሬው ጥናታችን የመክፈቻ ቃል "
የልቤ ሰው" (ቀ.12) የሚል ሲሆን፤ የማይጠቅም የነበረ ሰው (ቁ.11) ወደ ጳውሎስ መጥቶ ምን ቢደረግ? ወይም ምን ቢደረግለት? አልያም በምን ያህል ጊዜ ውስጥ ተለውጦ ነው የጳውሎስ የልብ ወዳጅ ሊሆን የቻለው? ለሚለውን ጥያቄ መልስ ለመፈለግ ሳስብ በመደነቅ እሞላለሁ።
የልቡ ሰው መሆን ብቻ ሳይሆን ከእርሱ ጋር ሆኖ የጳውሎስ አገልጋይ እስከመሆን የሕይወቱን ሙሉ ለሙሉ መለወጥ ስናይ የወንጌል መልዕክት ምን ያህል ኃይለኛ እንደሆነ መገንዘብ እንችላለን።
ጳውሎስ ለፊልሞና የአናሲሞስን መለወጥ ካበሰረው በኋላ አሁንም ቢሆን ሕጋዊ ባሪያው በሆነው አናሲሞስ ላይ ያለ አሳዳሪው(ፊልሞና) ፈቃድ አንዳች ነገር እንደማያደርግ መናገሩን ስናይ የጳውሎስን ሰው አክባሪነት፣ ጨዋነትና የአገልግሎት ሹመቱን በአግባብ የሚጠቀም በሳል ሰው መሆኑን እንረዳለን።
ጳውሎስ አናሲሞስን ከዚህ "ተቀበለው" ከሚል ትንሽዬ ደብዳቤ ጋር ወደ ፊልሞና ሲልከው በመካከላቸው ሊኖር ስለሚገባው ቤተሰባዊና የሥራ ግንኙነት ግልጽ መመርያ ይሰጣል። እነዚህም፦
1.
ለዘለቄታው ፦ ዘለቄታዊ የሚለው አባባል ምናልባት አናሲሞስ የፊልሞና የእድሜ ልክ ባሪያ (በዚያን ዘመን በነበረው የማህበረሰብ አኗኗር መሠረት) ሊሆን እንደሚችል ይጠቁማል። በሌላ በኩል ደግሞ በተፈጠረው ችግር ምክንያት የነበራቸው የሥራ ውል እንዳይፈርስ የአሰሪና ሰራተኛ ግንኙነታቸውን እንዲቀጥል መፈለጉን የሚያመለክት ይመስላል።
2.
ተወዳጅ ወንድም፦ ጳውሎስ በአናሲሞስና በፊልሞና መካከል ያለውን የባሪያና የጌታ ግንኙነት በቀጥታ በመቃወም መለወጥ አልፈለገም። ይልቁንም ግንኙታቸውን ከወንጌል ባገኙት ወንድማማችነት ላይ እንዲገነቡት ያሳስባቸዋል እንጂ። ይህ በተዘዋዋሪ ሰው ወንድሙን እንደ ባሪያ መቁጠር የለበትም የሚል አንድምታ አለው። ቁ.16 ላይ "በሥጋም" ሲል አብረው ከመኖራቸው የተነሳ ያላቸውን ቤተሰባዊነት ሲያመለክት በጌታም ሲል በዳግም ልደት ያገኙትን ዘላለማዊ ሕብረት ያሳያል።
በአጠቃላይ ጳውሎስ ትልቅ የምስራች የያዘችውን ደብዳቤ አስይዞ አናሲሞስን ወደ ፊልሞና ሲልከው በመካከላቸው ተፈጥሮ የነበረው ግጭት በሰላም ተፈቶ ሕብረታቸው ታድሶ እንደገና አብረው የመኖር ተስፋ ሰንቆ ስናይ የወንጌልን መልዕክት የመለወጥ አቅም በሚገባ እንገነዘባለን።
የእግዚአብሔር ጸጋና ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!!! ዛሬ የማሰላስለው የቃሉ እውነት፦ ወንጌል በደለኛውን ለውጦ የልብ ሰውና ተወዳጅ ወንድም ያደርጋል።
የዛሬው ፀሎት፦ ጌታ ሆይ በምኖርበት ማሕበረሰብ ውስጥ የእርቅና የሰላም ሰው አርገኝ።
ጌታ ቢፈቅድ ከነገ ወዲያ እስከምንገናኝ ደህና ሁኑ!!
ባይሣ ገመቹ
ሐምሌ 23 , 2014
ⒶⓇⓉⒾⓄⓈ
ⒶⓇⓉⒾⓄⓈ
ይ ላ ሉን
@artios_media
@artios_media
@artios_media
ይ ላ ሉን
2.4K viewsFeyisa Megersa, 21:01