Get Mystery Box with random crypto!

የትግራይ ተወላጆች አሸባሪው ህወሓትን ለመታገል ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ 'ኢትዮጵያን አፈርሳለሁ' ብ | አርአያ ተስፋማርያም/Araya Tesfemariam

የትግራይ ተወላጆች አሸባሪው ህወሓትን ለመታገል ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ

"ኢትዮጵያን አፈርሳለሁ" ብሎ የተነሳውን አሸባሪውን ህወሓት ለመታገል ቁርጠኛ መሆናቸውን በአዲስ አበባ ነዋሪ የሆኑ የትግራይ ተወላጆች ተናገሩ።

የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ዛሬ በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ በክፍለ ከተማው ከሚኖሩ የትግራይ ተወላጆች ጋር ውይይት አካሂዷል።

በውይይቱ ወቅት እንደተገለጸው፤ አሸባሪው ህወሓት ስልጣን ላይ በነበረበት ወቅት የክፋት፣ የጥላቻና የዘረኝነት እንቅስቃሴዎችን ሲያራግብ ቆይቷል።

አሸባሪው ህወሃት የዘራውን አሉታዊ አስተሳሰብ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ከውስጡ አውጥቶ የአሸባሪውን የክፋት አመለካከት በጽኑ ሊታገለው እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።

በመድረኩ አስተያየታቸውን የሰጡት ወይዘሮ ንግስቲ አበበ፤ አሸባሪው ህወሓት በሴራ ፖለቲካ ዘረኝነት እንዲስፋፋና ዜጎች እርስ በርስ እንዲጋጩ አድርጓል፤ እያደረገም ነው።

ይህ የሽብር ቡድን ለእኩይ ዓላማው ሲል የትግራይ ወጣቶችና ህፃናትን በማስገደድ ለጦርነት በመማገድ እያስጨረሰ መሆኑንም አንስተዋል።

አሸባሪው ሕወሃት ለህዝብ የማይጠቅም መሆኑን ጠቁመው፤ ቡድኑን ለማስወገድ እስከ መጨረሻው ለመታገል ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል።

የቡድኑን ዓላማ ለማስፈፀም በአዲስ አበባ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ አካላትን በማጋለጥ የበኩላቸውን ሚና እንደሚወጡ ገልጸው፤ "እኔ እያለሁ ኢትዮጵያ አትፈርስም" ብለዋል።

በማንኛውም መንገድ የአገር ሰላምን ለማደፍረስ ከሚያሰሩ አካላት መራቅ አስፈላጊ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ሌላው የክልሉ ተወላጅ አቶ ማቲዎስ ገብረሥላሴ፤ “ዜጎች ሁሉ የኢትዮጵያን አንድነት ለማስቀጠል መስራት ይኖርባቸዋል” ብለዋል።

ትግራይ የኢትዮጵያ ጠንካራ መሰረት መሆኗን የተናገሩት አቶ ተካ አበበ፤ የአሸባሪውን ሴራ ለመቀልበስ የትግራይ ህዝብ እንደ ሌሎች ኢትዮጵያዊያን በአንድነት መቆም እንደሚጠበቅበት አስገንዝበዋል።

በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያን ለማዳን በሚደረገው ጥረት ውስጥ ሁሉም በአንድነት ሊቆም እንደሚገባም ጠቁመዋል።

ሌላኛዋ የክልሉ ተወላጅ ወይዘሮ መሰሉ ረዳ እንደገለጹት፤ አሸባሪው ህወሓት የትግራይ ህዝብ እርዳታ እንዳያገኝ በማድረግ ለክልሉ ሕዝብ ጠላትነቱን በማስረጃ አረጋግጧል።

ይህ የሽብር ቡድን ዳቦ ሊሰጣቸው የሚገባ የትግራይ ህፃናትን ከእናቶቻቸው ጉያ ነጥቆ ሀሺሽ በመስጠት ወደ ጦርነት መማገዱ የሚያሳዝንና ሊወገዝ የሚገባው ድርጊት እንደሆነም አመልክተዋል።

በተለይም "ለክልሉ ሕዝብ ደህንነት የአካባቢው ተወላጆች ይህንን የሽብር ቡድን በጋራ መታገል አለብን" ብለዋል።

"እኔ ያልመራኋት ሀገር ትፍረስ" በማለት የሽብር ተግባር የሚፈጽመው አሸባሪው ህወሃት ለትግራይም ሆነ ለኢትዮጵያ ህዝብ እንደማይጠቅም አብራርተዋል።

የክፍለ ከተማው የህዝብ ግንኙነት አማካሪ አቶ ዘመን ተስፋዬ በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ አሸባሪው ህወሓት ከውጪ ሀይሎች ጋር በመሆን ሀገር የማፍረስ እንቅስቃሴውን በጋራ መመከት ይገባል።

አሸባሪው ቡድን የከፈተውን የውክልና ጦርነት በመመከት ረገድ የክልሉ ተወላጆች የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱም ጠይቀዋል።

በተለይም በአዲስ አበባ የሚኖሩ የክልሉ ተወላጆች የከተማውን ሰላምና ፀጥታ በማስጠበቅና የኢኮኖሚ አሻጥርን በመዋጋት የበኩላቸውን መወጣት እንደሚገባቸው መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል።