ፀጋን ለማግኘት ወደ ፀጋው ዙፋን መቅረብ::
ፀጋ ነፃ ስጦታ ነው:: ነፃ የሆነው በገንዘብም ሆነ በየትኛውም ውድ ነገር የማይለወጥ ወይንም የማይገዛ ስለሆነ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ፀጋ እና እውነትን ተሞልቶ: በእኛ አድሮ:በፀጋ ላይ ፀጋን ሰጠን:: ከዚህም የተነሳ በፀጋው ውስጥ ከሰው ያልሆነ በቃል የማይገለፅ አቅም/ ችሎታ አለ::
ታድያ በተለያየ ምክንያት ይህን መረዳት እና በህይወታችን መተግበር ቢያቅተን: ተስፋን አንቁረጥ:: አሁንም ፀጋን ለማግኘት ወደ ፀጋው ዙፋን በእምነት እንቅረብ:: በአቅማችን: በገንዘባችን እንዲሁም በሰው ባልቻልነው ነገር ላይ: ብዙ በሚያታግለን ነገር ላይ: የመጨረሻ የሚባለውን አቅማችንን: ትግሉ ላይ ሳይሆን: የሚረዳንን ፀጋ ለማግኘት ወደ ፀጋው ዙፋን ለመቅረብ እንጠቀምበት::
ስንቀርብ ደግሞ በማጉረምረም: አታየኝም ወይ በሚል ኩርፍያ እና ንዝነዛ ሳይሆን: በራሴ አልቻልኩትም አንተ ግን ትረዳኛለህ: በሚል እምነት ይሁን:: ያኔ እሱ በእምነት ስለቀረብን ደስስ ይለዋል:: መልሶም በአባታዊ ድምፁ "ፀጋዬ ይበቃሃል/ይበቃሻል" ይለናል::
በመጨረሻም የሚረዳው ፀጋ ከፀጋው ዙፋን በእምነት ሲገኝ ያኔ አሸናፊ ብቻ ሳይሆን ከአሸናፊዎች በላይ ያደርጋል::
ዛሬ ማነው ከእኔ ጋር ፀጋ ይብዛልኝ የሚል?
ሳሙኤል ተስፋሚካኤል ብዙነህ