Get Mystery Box with random crypto!

የድምጻዊት አስቴር አወቀ “ሶባ” አዲስ አልበም የጥምቀት ዋዜማ ይወጣል ! በዘመን አይሽሬ ድምጿ | ዳሰሳ አዲስ-Access Addis

የድምጻዊት አስቴር አወቀ “ሶባ” አዲስ አልበም የጥምቀት ዋዜማ ይወጣል !

በዘመን አይሽሬ ድምጿ እና ከመድረክ አያያዟ በተጨማሪ በራሷ ተወዳጅ ግጥምና ዜማዎቿ የምትታወቀው ተወዳጇ ድምጻዊት አስቴር አወቀ “ሶባ” የተሰኘ አዲስ አልበም የጥምቀት ዋዜማ እንደሚወጣ ሰዋሰው መልቲሚድያ አስታውቋል፡፡

በያዝነው አዲስ ዓመት መጀመሪያ ላይ ለሕዝብ የተዋወቀው እና ከመቶ በላይ አንጋፋና ወጣት ተወዳጅ ድምጻዊያንን በጋራ ለመስራት ያስፈረመው ሰዋሰው መልቲ ሚድያ ፤ አስር የሙዚቃ ስራዎችን ያካተተው የድምጻዊቷ “ሶባ” የተሰኘ አዲስ አልበምን የጥምቀት ዋዜማ በሰዋሰው መተግበሪያ በኩል ለአድማጮች ያደርሳል ተብሏል፡፡

ዛሬ ታህሳስ 25 ቀን 2015 ዓ/ም ድምጻዊ አስቴር አወቀ ከሰዋሰው መልቲ ሚድያ ጋር ስትፈራረም የሰዋሰው የማኔጅመንት አባላት ድምጻዊ አስቴር አወቀ እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
ድምጻዊት አስቴር አወቀ ከዚህ በፊት ሃያ አራት የሚደርሱ ዘመን አይሽሬ ተወዳጅ የሙዚቃ አልበሞችን እና ሁለት ነጠላ ዘፈኖችን ለሙዚቃ አፍቃሪያን ያደረሰች ሲሆን “ሶባ” ሃያ አምስተኛ አልበሟ ነው፡፡

ድምጻዊቷ ከሃገር ውስጥም በተጨማሪ በታላላቅ ዓለማቀፍ መድረኮች ስራዎቿን በማቅረብ ከፍተኛ አድናቆትን በማግኘት ኢትዮጵያዊቷ የሶል ሙዚቃ ንግስት በመባልም ትታወቃለች፡፡
ሰዋሰው መልቲ ሚድያ ጥበበኞች የሚገባቸውን የፈጠራ ዋጋ እንዲያገኙ በማድረግ የሃገራችን ጥበብ ባህር ማዶ ተሸጋሪ እንዲሆን ለማስቻል በከፍተኛ ኢንቨስትመንት የተቋቋመ ሀገር በቀል ድርጅት ነው፡፡