Get Mystery Box with random crypto!

††† እንኳን ለአባታችን ታላቁ ቅዱስ በርሱማ ሶርያዊ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ | አቡነ አቢብ (አባ ቡላ)

††† እንኳን ለአባታችን ታላቁ ቅዱስ በርሱማ ሶርያዊ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

@mekra_abaw
@mekra_abaw
@mekra_abaw

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ታላቁ አባ በርሱማ †††

††† ታላቁ (THE GREAT ይሉታል) አባ በርሱማ በሶርያ ቤተ ክርስቲያን ምንኩስናና ገዳማዊ ሕይወትን ያስፋፋ አባት ነው::

በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን ምድረ ሶርያን ጨምሮ በብዙ ቦታዎች የቅድስና ሕይወትን ያስፋፋው ቅዱስ በርሱማ ለቤተ ክርስቲያን ምሰሶ ከሆኑላት አበው አንዱ ነው:: እርሱ ከተጋድሎው ብዛት ለ54 ዓመታት ያለ እንቅልፍ ቆይቷል::

በእነዚህ ዘመናትም ግድግዳ ላይ ጠጋ ብሎ ከማረፉ በቀር መቀመጥን እንኩዋ አልመረጠም:: በመዓልትም በሌሊትም በፍቅር አብዝቶ ስለ ራሱና ስለ ሕዝቡ በመጸለዩ የብዙዎቹን ነፍስ ወደ ሕይወት ማርኩዋል::

ገዳማትን ከማስፋፋትና ደቀ መዛሙርትን ከማብዛቱ ባለፈ በስብከተ ወንጌልም የተመሰከረለት አባት ነበር:: በ431 (423) ዓ/ም በኤፌሶን በተደረገው የቅዱሳን ጉባኤ ላይ ከተገኙ ሊቃውንትም አንዱ ነው:: በቅድስና ሕይወቱ የተገረመው የቁስጥንጥንያው ንጉሥ (ትንሹ ቴዎዶስዮስ) የንግሥና ቀለበቱን እና ማኅተሙን ሸልሞታል::

ቅዱሱም የዋዛ አልነበረምና በንጉሡ ማኅተም እያተመ "ተፋቀሩ" የሚሉ ብዙ አዋጆችን ወደ መላው ዓለም ልኩዋል:: በ451 (443) ዓ/ም በኬልቄዶን 636 ሰነፍ ዻዻሳት ጉባኤ አድርገው አባ ዲዮርስቆሮስን እንደ ገደሉት ሲሰማም ወደ ቤተ መንግስት ሒዶ ከሃዲዎቹን (መርቅያንና ሚስቱ ብርክልያን) በአደባባይ ዘልፏቸዋል::

ስለ አዘነባቸውም ተቀስፈዋል:: ታላቁ ቅዱስ አባ በርሱማ ፀሐይን ማቆሙን ጨምሮ በርካታ ተአምራትን ሠርቶ በዚህች ቀን ዐርፏል::

††† ቸር አምላኩ ከበረከቱ ይክፈለን::

††† የካቲት 9 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አባ በርሱማ ሶርያዊ (ለሶርያ መነኮሳት ኁሉ አባት)
2.አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ (ኢትዮዽያዊ) የመነኮሱበት በዓል
3.ቅዱስ ዻውሎስ ሶርያዊ (ሰማዕት)
4.ቅዱስ ዼጥሮስ ሰማዕት

††† ወርሐዊ በዓላት
1."318ቱ" ቅዱሳን ሊቃውንት (ርቱዐነ ሃይማኖት ዘኒቅያ)
2.የብሔረ ብፁዐን ጻድቃን
3.አባ መልከ ጼዴቅ ዘሚዳ (ኢትዮዽያዊ)
4.ቅዱስ ዞሲማስ ጻድቅ (ዓለመ ብፁዐንን ያየ አባት)

††† "ምን ይዤ ወደ እግዚአብሔር ፊት ልምጣና በልዑል አምላክ ፊት ልስገድ? የሚቃጠለውን መስዋዕትና የአንዱን ዓመት ጥጃ ይዤ በፊቱ ልምጣን? እግዚአብሔርስ በሺህ አውራ በጐች: ወይስ በእልፍ የዘይት ፈሳሾች ደስ ይለዋልን? . . . ሰው ሆይ! መልካሙን ነግሮሃል:: እግዚአብሔርም ከአንተ ዘንድ የሚሻው ምንድር ነው? ፍርድን ታደርግ ዘንድ: ምሕረትንም ትወድ ዘንድ: ከአምላክህም ጋር በትሕትና ትሔድ ዘንድ አይደለምን" †††
(ሚክ. 6:6)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††