እውነት ምንድነው? ምንጭ ፦ የፍልስፍና አፅናፍ ፀሀፊ ፦ አለማየሁ ገላጋይ በአንዳንድ መመዘኛዎች አብዛኛው ሰው እውነት ብሎ የተስማማበት ነገር ከሞላ ጐደል እውነትነት አለው ተብሎ ይታሰባል፡፡ ይሁንና ይሄ ብያኔ ከብዙ የእውነታ ማረጋገጫ መንገዶች አንዱ እንጂ የመጨረሻ ማጠቃለያው እንዳልሆነ ልብ ማለት ይገባል፡፡ ስለዚህ አንተም ሆንክ የሀዲስ ኪዳኑ ጲላጦስ «እውነት ምንድር ነው?›› ስትሉ ለጠየቃችሁት የጓደኞችህ መደምደሚያ አርኪ ምላሽ አይሆንም። ከሁሉም በፊት ውሸት እንድንናገር የሚገፋፉን ነገሮች ምንድን ናቸው ብለን መነሳት የእውነትን ተፈጥሮ መርምሮ ለማግኘት ይረዳናል:: አንድ ሰው እንደማያፈቅራት ልቡናው የሚያውቀውን ሴት ‹‹አፈቅርሻለሁ› ቢል ውሸት ተናግሯል ማለት ነው:: ወይም አንድ ልጅ የብስኩት ማስቀመጫውን አድፋፍቶ እያለ እናቱ ስትጠይቀው ‹‹አላደረኩም›› ቢል ዋሽቷል፡፡ ውሸት ማለት የምታውቀውን የምታስበውንና የሚሰማህን ክደህ መናገር ነው፡፡ እንዲህ ያለው ድርጊት በየዋህነት ወይም በስህተት ከሚፈፀመው የተለየ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ የእግር ኳስ ዳኛ በአጠራጣሪ ሁኔታ የገባን ጎል ቢሽር ማለት ነው፡፡ የቅርብ ጊዜው አሜሪካዊው ታላቁ ፈላስፋ ጆሲያህ ሮይስ (Josiah Royce) ለውሸት ትርጓሜ ሲሰጥ የሰው ልጅ ይሆነኝ ብሎ የድርጊት መወከያ ቃላቱን በማቀያየር የሚያውቀውን እውነታ ሲቃረን ነው ይላል፡፡ «አይደለም» መባል የሚገባውን «ነው በሚልበት ጊዜ፤ ወይም «ነው» ማለት ሲገባው «አይደለም›› ለማለት ሲደፍር። ሮይስ ውሸትን የፈታበት መንገድ ወደ ጥንታዊ የእውነት ትርጓሜ ይመራናል፡፡ ከ2ሺህ 5 መቶ አመታት በፊት ፕሌቶና አርስቶትል በዚሁ መንገድ ለእውነትና ውሸት ብያኔ ሰጥተው ነበር፡፡ ፕሌቶና አርስቶትል እንደሚሉት የጨበጥነው አስተያየት ትክክለኛ መሆኑ የሚረጋገጠው