Get Mystery Box with random crypto!

+• የቀስት ጸሎቶች •+ የጊዜ ባለቤት ለሆነው ፈጣሪያችን 'ጊዜ አጣሁ' ማለት ከጀመርን ሰንበትበ | መምህር ዘበነ ለማ (ዶ/ር)

+• የቀስት ጸሎቶች •+

የጊዜ ባለቤት ለሆነው ፈጣሪያችን "ጊዜ አጣሁ" ማለት ከጀመርን ሰንበትበት ብለናል:: የፈጣሪን በረከት መንዝረን ስናበቃ ለእርሱ የሚሆኑ ሽርፍራፊ ደቂቃዎችን ለመመደብ እናመነታለን:: አባቶቻችን እና እናቶቻችን "ጸልዩ! ኧረ ተዉ ጸልዩ!" ብለው ለዘመናት ወተወቱ:: ይህ ምክራቸው ግን ፍጹም ሰሚ አጣ:: በጊዜ ያልተካንነውን ጸሎት ሁሉም ጭንቅ ሲሆን በወከባው መሃል ለመጸለይ ብንፈልግም ተሳነን:: "ሠርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ" እንደሚባለው ሠርግ የተባለ ሞት ደርሶ ስንኳ በርበሬ መቀንጥሱን አልቻልንም:: በተጋድሎው እጅግ ደክመን በመንፈሳዊው ውጊያው ላይ ሰይጣን ሙትና ቁስለኛ እያደረግን አለን::

ከትእዛዛቱ ምን ያህል እንደራቅን የምናውቀው "ሳታቋርጡ ጸልዩ" (1 ተሰ 5:17) መባላችንን ስናስታውስ ነው:: ጸሎቱ እንዳይቋረጥ የታዘዘው ውጊያውም ስለማያቋርጥ ነው:: ሰይጣን ድካም የሌለበት፣ እንቅልፍ የማያስፈልገው፣ ተስፋ የማይቆርጥ እና የብዙ ሺህ ዓመታት የሥራ ልምድ ያለው ከይሲ ነው:: የእኛን የሰዎችን ሁኔታ በሚገባ ስለተገነዘበም ቀጥታ ከመግጠም ይልቅ እንደ ደፈጣ ተዋጊ እየተደበቀ፣ እያዘናጋ እና እያደባ ያጠቃናል:: "የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ።" (ኤፌ 6:11) የሚለው ቃል አንድም ሳይቀር ያሉንን መንፈሳዊ ትጥቆች ሁሉ ታጥቀን እንድንነሳ የሚያሳስብ ነው:: ይህ የውጊያውን ብርቱነት በአጽንኦት ያስታውሰናል::

የጥንቶቹ ብርቱ አባቶች እና እናቶች ሰይጣንን እያቆሰሉ ድል ከነሱበት መሣሪያ አንዱ የቀስት ጸሎት ነው:: የቀስት ጸሎት ማለት ከመንፈሳዊ መጻሕፍትም ሆነ ከራሳችን ሊገኙ የሚችሉ አጭር እና በተመስጦ የሚባሉ አጫጭር ጸሎቶች መጠሪያ ነው:: በተለይም ደግሞ የምንኩስና ተጋድሎ በተፋፋመበት የግብጽ በረሃ ከጥንት አንስቶ የዚህ አይነት ጸሎቶች ጥቅም ላይ ይውሉ እንደነበር የሚያሳዩ ማስረጃዎች አሉ:: አባ ፖላሞን ከርሱ በቀደሙ ብርቱዎች ትምህርት ላይ ተመስርቶ አባ ጳጉሚስን ሲያስተምረው "ሳናቋርጥ እንድንጸልይ ታዝዘናልና፤ አጫጭር ጸሎቶቹን ሳንቆጥር ልንጸልይ ይገባናል" ብሎት ነበር:: ታላቁ ቅዱስ ወግሪስም "አጭር የተመስጦ ጸሎቶችን ተጠቀሙ" በማለት የሚመክር ሲሆን የእነዚህ ጸሎቶች ኃያልነትም ይታይ ዘንድ ቅዱስ ዮሐንስ ዘአስቄጥስ አጭርና በተመስጦ የሚባሉት ጸሎቶቹ ሰይጣንን ሲያቆስሉት በራዕይ ተመልክቶ ነበር::

ከእነዚህ የቀስት ጸሎቶች መካከል "ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ማረኝ" የሚለው ጸሎት ተወዳጅነትን ያተረፈ ነው:: ይህ ጸሎት በተለያየ አይነት ሁኔታ ለዘመናት አገልግሎት ላይ ውሏል:: በሀገራችንም "እግዚኦ ማሐረነ ክርስቶስ" (አቤቱ ክርስቶስ ሆይ ማረን) በሚለው ይታወቃል:: እንዲህ አይነት ጸሎቶች በሀገራችን የምንኩስና ታሪክ ውስጥ እንደነበሩ ማሳያ ከሚሆኑት አንዱ ደግሞ ቅዱስ አቡነ ሃብተማርያም ናቸው:: የታላቁ አቡነ ሃብተማርያም ገድል እንደሚነግረን ከሆን አባታችን ይህንን ጸሎት ከሰሙበት ጊዜ ጀምሮ ዘወትር እየደጋገሙ ይጸልዩት ነበር:: ዛሬም ድረስ ከመነኮሳት እስከ ምእመናን ድረስ ተወዳጅ ጸሎት ሆኖ እንደቀጠለ ነው::

የቀስት ጸሎቶች ሰይጣንን እረፍት ይነሱታል:: የእኛን ኅሊና ደግሞ ሁሌም ከፈጣሪ በማገናኘት "አልእሉ አልባቢክሙ" (ልቡናችሁን ከፍ ከፍ አድርጉ) የሚለውን ሰማያዊ ትእዛዝ ፈጻሚ ያደርጉናል:: የጸሎት መጽሐፍ መጨበጥ በማንችልባቸው ጊዜያት ሁሉ ከፈጣሪ የምንገናኝባቸው ድልድዮች ናቸው:: ከእነዚህ አጫጭር ጸሎቶች መካከል የተወሰኑትን እንመልከት:-

* ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ማረኝ

* አቤቱ ንጹህ ልብን ፍጠርልኝ፤ የቀናውንም መንፈስ በውስጤ አድስ (መዝ 50:10)

* አቤቱ ጌታዬና ንጉሤ ሆይ፤ ለባልንጀሮቼ ክፉ ያለማሰብን እና የራሴን ኃጢአቶች የማየት ጸጋ ስጠኝ (ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ)

* አቤቱ፥ እኔን ለማዳን ተመልከት፤ አቤቱ፥ እኔን ለመርዳት ፍጠን። (መዝ 70:1)

* ጌታ ሆይ፤ እንደ ፈቃድህ እና እንደ እውቀትህ ማረኝ! (ቅዱስ መቃርዮስ)

* ጌታ ሆይ እርዳኝ!

የሚከተሉት ደግሞ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ከደረሳቸው የሃያ አራት ሰዓት አጫጭር ጸሎቶች መካከል የተመረጡ ናቸው:-

* አቤቱ ጌታ ሆይ፤ ከዘለዓለማዊ ስቃይ አድነኝ!

* እቤቱ ጌታ ሆይ፤ ከፈተና ሁሉ አድነኝ!

* አቤቱ ጌታ ሆይ፤ አትተወኝ!

* አቤቱ ጌታ ሆይ፤ ትሕትናን፣ ንጽሕናን እና መታዘዝን ስጠኝ::

* አቤቱ ጌታ ሆይ፤ ስምህን አመሰግን ዘንድ ጸጋህን ላክልኝ::

* አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፤ በሕይወት መጽሐፍ ስሜን ጻፈው፤ መጨረሻዬንም አሳምርልኝ::

በእነዚህ እና መሠል ጸሎቶች ሕይወታችንን እናስጊጥ:: ለመጸለይ የግድ ሰዓት መጠበቅም ሆነ የጸሎት መጽሐፍ መጨበጥ የለብንም:: ልባችን ያረፈበትን አንድ አጭር ጸሎት (ወይም እንዳለንበት ሁኔታ ተስማሚ የሆነውን አጭር ጸሎት) የእግር ጉዞ ስናደርግ፣ በመኪና ስንሄድ፣ ስንቀመጥም ሆነ ስንተኛ በውስጣችን እየደጋገምን እንጸልይ::

ጸሎት የሁሉ ነገር መክፈቻ ቁልፍ መሆኗን አንዘንጋ!

Fresenbet G.Y Adhanom