Get Mystery Box with random crypto!

#እቱ_ጉንጬን_ሳሚኝ . . ሰርክ ተናፋቂ የአመሻሽ ጨረቃ፣ በኮኮብ መቀነት ተንዠርግጋ ደምቃ። እንደ | ኢትዮ ስነ ቃል

#እቱ_ጉንጬን_ሳሚኝ
.
.
ሰርክ ተናፋቂ የአመሻሽ ጨረቃ፣
በኮኮብ መቀነት ተንዠርግጋ ደምቃ።
እንደ ፍቅር አምላክ፤
እንደ ከመት ጣዖት አምራ ተሽሞንሙና፣
'ካማልኩቱ ሰፌድ ህብረ ቀለም ዘግና።
ልክ እንደ መሽቀርቀር እራሷን ብትኩልም
እመኚኝ የኔ ውድ፤
ቅንጣት ነው ውበቷ አንቺን አታክልም።
ፀሃይን አወቅሻት ?፤
አንቺን አታክንም፤
በወል ብርሃኗ በምትፈነጥቀው፣
አንቺን ያየሽ ሁሉ፤
ለገፅሽ ተማርኮ ውብ ፀዳሏን ናቀው።

በመስተፋቅርሽ፤
በመስተዋድድሽ፤
ስቀሽ የሰወርሺው መኖሩን የረሳ፣
አይንሽን ሊሳለም የቀዬው ጎረምሳ።
ከመንገድ ዳር ቆሞ ላንቺ እየማለለ፣
"መዓዛዋ ወይራ ናርዶስ ልጅ ናት" አለ።
አንቺ ናርዶስ ሽቶ፤
አንቺ ውብ መዓዛ፤
ከፃድቃን ፊት ቆሜ ሀጥያቴን ስታጠብ፣
ካባተለኝ እድፍ ስርቅ ከስጋ ጠብ።
እንደሰው ቤተኛ ለፅድቄ ተገኚ፣
ከእግዜር እግር ፈሰሽ ምህረት ለምኚ።
ወትሮም በጥበቡ፤
ሞትና መሰንበት አምላክ ሲያራቅቀው፣
በውድቀቱ በኩል፤
በሔዋኑ በኩል ወንዱን አፀደቀው።

እስቲ ጉንጬን ሳሚኝ፤
ደባብሺኝ ደባብሺኝ ላመል ለነገሩ፣
በቅዱስ ከንፈርሽ፤
ግርጣቴ ሲለዝብ ይግረመው ሀገሩ።

እቱ ጉንጬን ሳሚኝ፤
ለኩሺኝ እንደ ጧፍ፤
መዛሌን ላበርታው ከል ምሽቴን ልርታው፣
የዳበስሺው ሁሉ
አንቺ የሳምሺው ሁሉ
እግዜር ቢመርቀው ቀን ሆነለት ማታው።
ብርሃን ፀዳል ልልበስ፤
ካማልክቱ መሃል እንዳንዱ ልቆጠር፣
"በከንፈርሽ አምላክ"
መኖሬ እልፍ ይሁን መሞት እድሜው ይጠር።

ወትሮ የለመንኩት የማለድኩት ረቢ፣
"ይሁን ይሁን" ብሎ
ብርሃን ሊያጠምቀኝ ልትስሚኝ ስትቀርቢ፣
ደርሶ ያለወትሮው፤
እግሬ እየከዳኝ መንፈሴ ካልነቃ፣
ጣዖታዊ ውበት፤
ልቤን ሊሰወረኝ ማርኮኝ ኖሯል በቃ።

ያዳም ዘር በሙሉ፤
በአስማተ ተፈጥሮ፤
ልቡን እየደቃው አንዳች ሲማርከው፣
የዛን ለት ለካ፤
ካምላኩ አስበልጦ ጣዖት የሚያመልከው።

ልክ ነኝ ጣዖቴ?፤
ጉንጬን የሳምሺኝ ለት፤
ተፈጭሮን ገደፍኳት።
ጨረቃዋን ናኳት ፀሃይ ቅንጣት ሆነች፣
አለም የምንላት፤
'ባሴት በደስታዋ አንቺን መች አከለች።

ልክ ነኝ ጣዖቴ ?፤
ጉንጬን ስትስሚኝ፤
ጥልቅ ማሰላሰል እሩቅ ማሰብ ጠላሁ፣
ጣዖቴ ነሽ ስልሽ፤
ከፈጠረኝ አምላክ ከእግዜሩ ተጣላሁ።
አንቺ መላዕክ ስልሽ፤
አንቺን ጣዖት ስልሽ፤
ግራ ቢገባቸው፤
መላዕክቶች ሁሉ ሸሹ ከኔ ራቁ፤
ላፈቀረሽ ልቤ፤
እግዜርና ሰይጣን ተደበላለቁ።

አየሽ የኔ መላክ፤
በዳይ አባታችን፤
አዳም ለውድቀቱ በሴት ዘር ተማረ፣
ወትሮ ለፍቅር ሲል፤
ወድቆ የተገኘው ግን በሄዋን ነበረ።
ምድረ ተዕባት ሁላ፤
ከስር መሰረቱ ከጥንትም ጀምረን፣
በውል ባናውቀውም ማን እንደመከረን።
አምላክን አስትቶ እውነት አስረስቶ፤
የሴት ልጅ ውበቷ፤
ገዳይ ደም ግባቷ፤
ለግዞት ሊቃኘን ማርኮ ስለረታን፣
ከ"አጥፊ"ያችን ጋራ አብሮ እግዜር ይፍታን።
.
.
.
"አንቺዬ........
አጥፊዬም አይደለሽ፤?
አንቺም እግዜር ይፍታሽ።"


ዓቢይ ( @abiye12 )

Join & share

@sinekal
@sinekal
@sinekal