Get Mystery Box with random crypto!

ከነገሩ ውጪ መኖር ካልቻልክ ከነገሩ ጋር መኖር አትችልም (ዶ/ር እዮብ ማሞ) ሰዎች አንድን ነገር | 15:53

ከነገሩ ውጪ መኖር ካልቻልክ ከነገሩ ጋር መኖር አትችልም
(ዶ/ር እዮብ ማሞ)
ሰዎች አንድን ነገር በእጃቸው ለማስገባት ምንም ነገር ከማድረግ የማይመለሱት፣ ማስገባት ካቃታቸው ከሰው በታች እንደሆኑ የሚያስቡትና ተሳክቶላቸው ካስገቡ በኋለ ደግሞ ያንን ነገር ላለማጣት እንደገና ምንም አይነት የጭካኔም ስራ ቢሆን ከመስራት የማይመለሱት ከዚያ ነገር ውጪ ሙሉ ሕይወት ሊኖራቸው እንደማይችል ሲያስቡ ነው፡፡
ለምሳሌ፣ አንድ ሰው ከስልጣን ውጪ መኖር እንደማይችል ካሰበ ስልጣንን በእጁ ለማስገባትም ሆነ አንዴ በእጁ የገባውን ስልጣን ላለመልቀቅ ሌላውን በጭካኔ እስከማጥፋት ድረስ ይደርሳል፡፡ ይህ እውነታ ከዝና፣ ከሃብትና ከመሳሰሉት “ውጫዊ” ሁኔታዎች አንጻር ሲታይ ተግባራዊነቱ ያው ነው፡፡
አየህ፣ ከስልጣን፣ ከዝና፣ ከሃብትና ከመሳሰሉት ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ ሊሰጣቸው ከሚገባቸውን ነገሮች ውጪ መኖር እንደምንችል ራሳችንን ስናሳምነው ብቻ እነዚህ ነገሮች በእጃችን ሲገቡ በተረጋጋና ከእኛና ከቤተሰባችን አልፈን ለሕብረተሰቡ የሚጠቅም ነገር እናደርግባቸዋለን፡፡ ምናልባት ጊዜው ተለውጦ ደግሞ ቀድሞ የነበረን ነገር በእጃችን እንደማይቆይ ስናስብ አሁንም ቀድሞ ከሁኔታው ውጪ በነበርንበት ጊዜ የነበረንን የተረጋጋ ማንነት ይዘን መቀጠል አያስቸግረንም፡፡
እቅጩን ልንገርህ፡- ከመወደድና ከተቀባይነት ውጪ አርፈህ መኖር ካልቻልክ በመወደድና በተቀባይነት ውስጥ አርፈህ መኖር አትችልም፡፡ ከሃብት ውጪ ተረጋግተህ መኖር ካልቻልክ ሃብትን ሰብስበህ ተረጋግተህ መኖር አትችልም፡፡ ከስልጣን ውጪ ሰከን ብልህ መኖር ካልቻልክ ስልጣን ብታገኝም ሰክነህ አትኖርም፡፡ ከዝና ውጪ ዘና ብለህ መኖር ካልቻልክ ዝነኛ ስትሆን ዘና ብለህ መኖር አትችልም፡፡
ቀድሞውኑ ያላረፈ ሰው ይህንና ያንን ባገኝ አርፍ ነበር የሚለውን ነገር በእጁ ለማስገባት ሲግለበለብ ኖሮ፣ እጁ ካስገባው በኋላ ደግሞ ያንን ነገር ከእጁ ላለማጣት ሲግለበለብ ለራሱና ለሌላው የረብሻ ምክንያት ይሆናል።

@lifein1553